የ2013 የዳይመንድ ሊግ ፉክክር ባለፈው ሐሙስ ዙሪክ ላይ ሲካሄድ በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮኗ መሰረት ደፋር የቅርብ ተቃናቃኟን ጥሩነሽ ዲባባ በመቅደም አሸናፊ ሆነች፡፡ በዙሪኩ የዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ መሰረት ደፋር እና ጥሩነሽ ዲባባ በሩጫ ዘመናቸው ለ33ኛ ጊዜ መገናኘታቸው ሲሆን ከሃሙሱ ውጤት በኋላ ፉክራቸው በጥሩነሽ ዲባባ 19 ለ14 ድል አድራጊነት ቀጥሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጥሩነሽ ዲባባ እና መሰረት ደፋር በታሪካቸው ለ34ኛ ጊዜ ከሁለት ሳምንት በኋላ በቡፓ ግሬት ኖርዝ ናን ግማሽ ማራቶን መፋጠጣቸውም ተጠብቋል፡፡ ከሁለት ሳምንት በኋላ በቡፓ ግሬት ኖርዝ ራን የግማሽ ማራቶን ሞ ፋራህ፤ ኃይሌ ገብረስላሴ እና ቀነኒሳ በቀለ መወዳደራቸው ሲያነጋግር ቆይቶ ነበር፡፡ በሴቶች ምድብ የጥሩነሽ ዲባባ እና የመሰረት ደፋር በግማሽ ማራቶን መገናኘት ከሰሞኑ መሰማቱ ማን በይበልጥ ከፍተኛ ትኩረት ሊስብ እንደቻለ ታውቋል፡፡ በሞስኮ ተካሂዶ በነበረው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የጥሩነሽ ዲባባ እና የመሰር ደፋር ተቀናቃኝነት በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ትኩረት ተሰጥቶ ነበር፡፡ የሚታወስ ይሁንና ለወጣት እና አዳዲስ አትሌቶች እድል እንዲሰጥ በፌደሬሽን ተጠይቆ ሁለቱ አትሌቶች በየምርጥ የውድድር መደባቸው ገብተው የዓለም ሻምፒዮኖች ሆነዋል፡፡ ጥሩነሽ ዲባባ በ10ሺ ሜትር እንዲሁም መሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን መውሰዳቸው አይዘነጋም፡፡ የዳይመንድ ሊጉ የአንድ ከተማ ፉክክር እየቀረው መሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር ማሸነፍ የቻለችው በ18 ነጥብ አንደኛ መሆኗን አረጋግጣ ሲሆን የዳይመንድ ቀለበት እና የ50ሺ ዶላር ሽልማት ተጎናፅፋለች፡፡ ጥሩነሽ ዲባባ በ12 ነጥብ ሁለተኛ ሆና የዳይመንድ ሊጉን ፉክክር አጠናቅቃለች፡፡ በተያያዘ በዘንድሮው የዳይመንድ ሊግ ውድድር ሌሎች ሁለት የኢትዮጵያ አትሌቶችም በየውድድር መደባቸው የመሪነት ደረጃውን በመያዝ ለአሸናፊነት እየገሰገሱ ሲሆን ከሁለት ሳምንት በኋላ በቤልጅዬም ብራሰልስ የሚደረገው ውድድር ይጠብቃቸዋል፡፡ በ800 ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው መሃመድ አማን የዳይመንድ ሊግ ፉክክሩን በ14 ነጥብ አንደኛ ሆኖ እየመራ ሲሆን የኬንያው ዴቪድ ሩዲሻ በ8 ነጥብ እንዲሁም የፈረንሳዩ ፒዬሬ አምብሮሴ ፒርስ በ6 ነጥብ በ2ኛ እና በሶስተኛ ደረጃ ይከተሉታል፡፡በ5ሺ ሜትር በዓለም ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ የወሰደው አትሌት ሃጎስ ገብረህይወት እና የኔው አላምረው በዳይመንድ ሊጉ ፉክክር ተያይዘዋል፡፡ ሃጎስ ገብረህይወት በዳይመንድ ሊጉ በ5ሺ ሜትር መሪነቱን የያዘው በ13 ነጥብ ሲሆን የኔው አላምረው በ11 ነጥብ ይከተለዋል፡፡ የእንግሊዙ ሞፋራህ እና የኬንያው ኤድዊን ሶይ እያንዳንዳቸው አራት ነጥብ ይዘው 3ኛ ደረጃን ተጋርተዋል፡፡
የውድድር ዘመኑን በ3ሺ ሜትር በማሸነፍ በጥሩ ብቃት የጀመረችው አትሌት መሰረት ደፋር በኒውኦርሊዬንስ ግማሽ ማራቶን ከወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ በመወዳደር ርቀቱን በ67 ደቂቃ ከ25 ሴኮንዶች በመሸፈን የቦታውን ሪከርድ አስመዝግባ አሸንፋለች፡፡ በሴቶች 5ሺ ሜትር የዓለም ሪከርድ በምንግዜም የዓለማችን ምርጥ ሴት አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ የተያዘ ቢሆንም በትልልቅ ዓለምአቀፍ ውድድሮች በርቀቱ ባስመዘገበችው ውጤት መሰረት ደፋርን የሚስተካከላት አልተገኘም፡፡ በ5ሺ ሜትር ሴት አትሌቶች የዘንድሮ ዓለም አቀፍ ደረጃን መሰረት ደፋር፤ በ1389 ነጥብ በአንደኝነት እየመራች ነው፡፡ በኦሎምፒክ መድረክ በ5ሺ ሜትር በ2004 እኤአ በአቴንስ እና በ2012 እኤአ በለንደን ኦሎምፒክ ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችና በ2008 እኤ በቤጂንግ ኦሎምፒክ የነሐስ ሜዳልያ የሰበሰበችው መሰረት ደፋር በዓለም ሻምፒዮና በ5ሺ ሜትር ሁለት ወርቅ ሜዳልያዎች በ2007 እኤአ ኦሰካና በ2013 እኤአ ሞስኮ ላይ፤ የብር ሜዳልያ በ2005 እኤአ ሄልሲንኪ ላይ እንዲሁም ሁለት የነሐስ ሜዳልያዎች በ2009 እኤአ በርሊንና በ2011 እኤአ ዳጉ ላይ በማግኘት ተሳክቶላታል፡፡መሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድር፤ በ3ሺ ሜትር እና በ2 ማይል ውድድሮች ሶስት ክብረወሰኖችንም የያዘች ናት፡፡ በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ወድድር ከ2004 እስከ 2010 እኤአ ለአራት ተከታታይ የውድድር ዘመናት አራት የወርቅ ሜዳልያዎችን ከመሰብሰቧም በላይ፤ በኦሎአፍሪካን ጌምስ ለሁለት ጊዜ ሻምፒዮን፤ በአፍሪካ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና አራት ሜዳልያዎች እንዲሁም በዓለም ወጣቶች ሻምፒዮና ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች በ5ሺ ሜትር በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡

 

             በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከሞላ ጎደል ስኬታማ የሆነው የኢትዮጵያ አትሌቶች ቡድን በመንግስት እና በተለያዩ ባለድርሻ አካላት በኩል መቼ እንደሚሸለም አልታወቀም፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን የልዑካን ቡድኑን ወጤታማነት እና ድክመት በመገምገም በቅርቡ ይፋዊ መግለጫ እንደሚሰጥ የሚጠበቅ ሲሆን ለተገኘው ስኬት አስፈላጊውን የማበረታቻ ሽልማት ለማከናወን በዝግጅት ላይ እንደሆነ ምንጮች ገልፀዋል፡፡ በዓለም ሻምፒዮናው የሜዳልያ ደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ በሰበሰበቻቸው 10 ሜዳልያዎች ከዓለም 6ኛ እንዲሁም ከአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃን ማግኘቷ ይታወሳል፡፡ ሞስኮ ላይ የኢትዮጵያ ቡድን በድምሩ 10 (3 የወርቅ፤ 3 የብርና 4 የነሐስ ) ሜዳልያዎች መሰብሰቡ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ ከፍተኛው የሜዳልያ ብዛት ሲሆን አስሩ ሜዳልያዎች በ10 የተለያዩ አትሌቶች መገኘታቸው፤ በአዳዲስ የውድድር መደቦች ለመጀመርያ ጊዜ የተገኙ ሜዳልያዎች መኖርና ወጣት እና ተተኪ አትሌቶች በውጤታማነት መውጣታቸው የስኬቱን ታሪካዊነት አጉልቶታል፡፡ የኢትዮጵያን 3 የወርቅ ሜዳልያዎች በ10ሺ ሜትር ሴቶች ጥሩነሽ ዲባባ፤ በ800 ሜትር ወንዶች መሃመድ አማን እንዲሁም በ5ሺ ሜትር ሴቶች መሰረት ደፋር አስመዝግበዋል፡፡ ሶስቱን የብር ሜዳልያዎች ኢብራሂም ጄይላን በወንዶች 10ሺ ሜትር፤ ሃጎስ ገብረህይወት በወንዶች 5ሺ ሜትር እንዲሁም ሌሊሳ ዴሲሳ በወንዶች ማራቶን ሲጎናፀፉ አራቱን የነሐስ ሜዳልያዎች ደግሞ በ10ሺ ሜትር ሴቶች በላይነሽ ኦልጅራ፤ በ3ሺ መሰናክል ሶፍያ አሰፋ፤ በ5ሺ ሜትር ሴቶች አልማዝ አያና እንዲሁም በወንዶች ማራቶን ታደሰ ቶላ አግኝተዋቸዋል፡፡ ብዙውን ጊዜ በዓለም ሻምፒዮና እና በኦሎምፒክ ውድድሮች ማግስት ውጤታማ ለሚሆኑ የአትሌቶች ቡድን አባላት እና ለአጠቃላይ ልዑካኑ በመንግስት እና በሌሎች ባለድርሻ አካላት በኩል የገንዘብ፤ የማዕረግ እና ልዩ ልዩ የክብ ሽልማት ይሰጥ የነበረ ሲሆን ለአሁኑ ቡድን የሚደረገው ርብርብ ያነሰ መስሏል፡፡ ኒያላ ኢንሹራንስ በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሜዳልያ ላገኙ አትሌቶች የህይወት ዋስትና በመግባት ማበረታቱን ጀምሯል፡፡
በተያያዘ ዜና በዓለም ሻምፒዮናው ለሜዳልያ አሸናፊዎች እና እስከ ስምንተኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች ከቀረበው እስከ 7 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የሽልማት ገንዘብ በ10 ሜዳልያዎች እና በወንዶች ማራቶን በቡድን ውጤት በተገኘው ተጨማሪ የወርቅ ሜዳልያ ኢትዮጵያ 330ሺ ዶላር ስታገኝ በአጠቃላይ 12 ሜዳልያ የሰበሰበችው ኬንያ ድርሻዋ 640ሺ ዶላር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከሜዳልያ ተሸላሚዎች ከሰበሰበችው 330ሺ ዶላር ባሻገር እስከ ስምንት ባለው ደረጃ አራተኛ የወጡ 2 ፤ 5ኛ የወጡ 3፤ ሰባተኛ የወጡ 2 እና 8ኛ የወጡ 2 አትሌቶች በማስመዝገቧ በአጠቃላይ ከቀረበው የሽልማት ገንዘብ 408ሺ ዶላር ስታገኝ የኬንያ ድርሻ 891ሺ ዶላር ሆኗል፡፡
በሌላ በኩል የኬንያ ቡድን በሞስኮው የዓለም ሻምፒዮና አመርቂ ውጤት አላመጣም በሚል ከፍተተኛ ትችት ከሚዲያው እና ከአንዳንድ ባለሙያዎች እየደረሰበት ሰንብቷል፡፡ በወንዶች ማራቶን የኬንያ አትሌቶች በኡጋንዳ፤ በኢትዮጵያ፤ በጃፓንና በብራዚል ማራቶኒስቶች መበለጣቸው፤ በ3ሺ መሰናክል ከ1 እስከ 3 ደረጃ አለመገኘቱን የጠቀሱት ተቺዎቹ ሞስኮ ላይ የኬንያ ቡድን በቡድን ስራ እና በሚማርክ ቅንጅት አልሰራም በማለት ተቃውመዋል፡፡ የኬንያ ምክትል ፕሬዝዳንት በዓለም ሻምፒዮናው ሜዳልያ ላመጡ አትሌቶች የገንዘብ ሽልማት ሰሞኑን ያበረከቱ ሲሆን፤ ለወርቅ ሜዳልያ አሸናፊዎች 11495 ዶላር ፤ ለብር ሜዳልያ 8621 ዶላር እንዲሁም ለነሐስ ሜዳልያ 5748 ዶላር ተሰጥቷቸዋል፡፡
በአጠቃላይ በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው የሜዳልያ ስብስብ ደረጃ ሰንጠረዥ ላይ 1ኛ ሆና የጨረሰችው ራሽያ በ7 የወርቅ፤ 4 የብርና 6 የነሐስ ሜዳልያዎች ሲሆን የደረጃ ሰንጠረዡን መሪነት ከአሜሪካ ስትነጥቅ ከ12 ዓመታት በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ነው፡፡ አሜሪካ በ6 የወርቅ፤ 14 የብርና 5 የነሐስ ሜዳሊያዎች ሁለተኛ ደረጃን አግኝታለች፡፡ ጃማይካ በ5 የወርቅ፤ በ2 የብርና በ1 የነሐስ ሜዳልያ ሶስተኛ ፤ ኬንያ በ5 የወርቅ፤ በ4 የብርና በ3 የነሐስ ሜዳልያዎች 4ኛ እንዲሁም ጀርመን በ4 የወርቅ፤ በ2 የብርና በ1 የነሐስ ሜዳልያ አምስተኛ ሆነዋል፡፡ በሻምፒዮናው የአፍሪካ አገራት በነበራቸው ተሳትፎ 8 አገራት ብቻ የሜዳልያ ስኬት አግኝተዋል፡፡ ከአፍሪካ አህጉር ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ አንደኛ ደረጃ የያዘችው ኬንያ ስትሆን ኢትዮጵያ ሁለተኛ ሆናለች፡፡ ሌሎች አፍሪካን የወከሉ አገራት ኡጋንዳ በወንዶች ማራቶን ባገኘችው ብቸኛ የወርቅ ሜዳልያ ሶስተኛ፤ አይቬሪኮስት በ2 የብር ሜዳልያዎች አራተኛ፤ ናይጄርያ በ1 የብርና በ1 የነሐስ ሜዳልያዎች አምስተኛ፤ ቦትስዋና በ1 የብር ሜዳልያ ስድስተኛ እንዲሁም ደቡብ አፍሪካ እና ጅቡቲ በእያንዳንዳቸው በወሰዷቸው አንድ ነሐስ ሜዳልያዎች ሰባተኛ ደረጃን ለማግኘት ችለዋል፡፡ በዓለም ሻምፒዮና በተሳተፉባቸው የውድድር መደቦች ከ1 እስከ ስምንት ባለው ደረጃ ባስመዘገቡት ውጤት በመመስረት በተሰራው ደረጃ ኬንያ 3ኛ ስትሆን ኢትዮጵያ ደግሞ ስድስተኛ ነች፡፡ በሜዳልያ ስብስብ እና በአጠቃላይ ውጤት በወጣው ደረጃ አሜሪካ በ282 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ስታገኝ፤ ራሽያ በ83 ነጥብ ሁለተኛ፤ ኬንያ በ139 ነጥብ ሶስተኛ፤ ጀርመን በ102 ነጥብ አራተኛ፤ ጃማይካ በ100 ነጥብ አምስተኛ፤ ኢትዮጵያ በ97 ነጥብ ስድስተኛ፤ እንግሊዝ በ79 ነጥብ ሰባተኛ እንዲሁም ዩክሬን በ51 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ከ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በኋላ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የምንጊዜም የሜዳልያ ስብስብ የደረጃ ሰንጠረዥም ለውጦች ታይተዋል፡፡ በ14 የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የሰበሰበቻቸውን ሜዳልያዎች 300 (138 የወርቅ፤ 88 የብርና 74 የነሐስ) ያደረሰችው አሜሪካ አንደኛነቷን እንዳስጠበቀች ናት፡፡ ራሽያ 168 ሜዳልያዎች (53 የወርቅ ፤ 60 የብርና 55 የነሐስ)፤ ኬንያ 112 ሜዳልያዎች (43 የወርቅ፤ 37 የብርና 32 የነሐስ) ፤ ጀርመን 101 ሜዳልያዎች (35 የወርቅ፤ 28 የብርና 38 የነሐስ)፤ ጃማይካ 98 ሜዳልያዎች (24 የወርቅ፤ 42 የብርና 32 የነሐስ)፤ ሶቭዬት ህበረት 75 ሜዳልያዎች (22 የወርቅ፤ 25 የብርና 28 የነሐስ) እንዲሁም ኢትዮጵያ 64 ሜዳልያዎች (22 የወርቅ፤ 19 የብርና 23 የነሐስ) በ14 የዓለም ሻምፒዮናዎች የተሳትፎ ታሪካቸው በማስመዝገብ እስከ 7 ያለውን ደረጃ አከታትለው ይዘዋል፡፡

Saturday, 31 August 2013 12:49

“...ይለይልኝ ብዬ...”

ኤችአይቪ ቫይረስ በሰዎች ላይ መከሰት ከጀመረ ጀምሮ ተፈጥሮ የነበረው አድሎና መገለል በራሱ ብዙዎችን ለሞት ያበቃ መሆኑ እሙን ነው፡፡ ሰዎች ከቫይረሱ ጋር እየኖሩ መሆኑን ልባቸው እያወቀ ነገር ግን ወደ ሕክምና ተቋም በመሄድ በቫይረሱ መያዝ አለመያ ዛቸውን ማረጋገጥ ከማይፈልጉበት ደረጃ ላይ እንደነበሩና በድብቅ ከተኙበት እየሞቱ እንደነበረ የቅርብ አመታት ትውስታ ነው፡፡ ነገር ግን እየዋለ እያደረ በጉዳዩ ላይ ሰፊ ውይይቶች በመደ ረጋቸው እንዲሁም በመገናኛ ብዙሀን ትምህርት በመሰጠቱ ፣የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት ወደ ሀገር በመግ ባቱና በስፋት እንዲሁም በነጻ መታደል በመጀመሩ ከፍተኛ የንቃተ ህሊና ማዳበር ስራ ተሰርቶ ሁኔታዎች ተለውጠዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሰዎች በተለያዩ ማህበራት በመደራጀት ማንኛውም ሰው ከቫይረሱ ጋር መኖር ያለመኖሩን ምርመራ በማድረግ እራሱን እንዲያውቅ እና አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ የተቻላቸውን ያህል ምክር በመስጠት ላይ ናቸው፡፡ ከቫይረሱ ጋር በሚኖሩ ሰዎች ተቋቁመው ስራ በመስራት ላይ ከሚገኙት ማህበራት አንዱ ጥላ የተሰኘው በአዋሳ የተቋቋመው ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር ሲሆን ከእነሱ ጋር ያደረግነውን ውይይት እነሆ ለንባብ ብለናል፡፡
አንድ የጥላ ማህበር አባል እራስዋን ከቫይረሱ ጋር መኖርዋን እንዴት እንዳወቀች እንድትገልጽ በዚህ አምድ አዘጋጅ ተጋበዘች፡፡ እሱዋም እንደሚከተለው ገልጻለች፡፡
“እኔ እራሴን ያወቅሁት በሰው አማካኝነት ነው። በመጀመሪያ ከገጠር ስመጣ በሰው ቤት እየሰራሁ እማራለሁ ብዬ ነበር፡፡ ነገር ግን ተቀጥሬ ከምሰራበት ቤት ፊት ለፊት የጥበቃ ስራ የሚሰራ ሰው ...ለምን ሰው ቤት ትሰሪያለሽ...ከእኔ ጋር ቤት ተከራይተን አብረን እየኖርን የቻልነውን ነገር እየሰራን እንኑር ብሎ ሲያግባባኝ እሺ ብዬ አብሬ መኖር ጀመርኩኝ፡፡ ብዙም ሳይቆይ ወደስምንተኛው ወራችን ገደማ ሰውየው በከፍተኛ ሁኔታ ታመመ፡፡
ጥ/ ከመታመም ባለፈስ ?
መ/ .....በጊዜው ምንም አልተከሰተም፡፡ ነገር ግን ክፉኛ በመታመሙ ወደገጠር ወደቤተሰቦቹ ተወሰደ እና ብቻዬን መኖር ጀመርኩኝ፡፡ ...ለነገሩማ...ትንሽ ቆይቶ ሞተ፡፡
ጥ/ የአንቺ ቀጣይ ሕይወት ምን ይመስል ነበር?
መ/ ...ትንሽ ቆይቶ እኔም ታመምኩኝ፡፡ በጣም ትከታተለኝ የነበረች ጉዋደኛዬ ...ምን ሆነሽ ነው? አለችኝ፡፡ እኔም ምክንያቱ ምን እንደሆነ ያልገባኝ ሕመም እያመመኝ መሆኑን ገለጽኩላት፡፡ ጉዋደኛዬ ወደሆስፒታል እንሂድ ብላ ስታስመረምረኝ ቫይረሱ በደሜ ውስጥ እንደሚገኝ ተገለጸልኝ፡፡
ጥ/ በምን ሁኔታ ተቀበልሽው?
መ/ በጊዜው በምንም ሁኔታ አልተቀበልኩትም፡፡ እንደ እብድ ወደሐይቅ እሮጥኩ፡፡ ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር አብሮ መኖር ማለት ሕይወት ያበቃለት የመጨረሻው አለም ነው ብዬ ነበር ያሰብኩት፡፡ ወደሐኪም ወስዳ ያስመረመረችኝ ልጅ አብራኝ ባትኖር ኖሮ ሐይቅ ገብቼ ነበር፡፡ ነገር ግን በእሱዋ ብርታት ከአደጋ ተርፌ...ከብዙ ትግል በሁዋላ አሁን ኑሮዬን አስተካክዬ በመኖር ላይ እገኛለሁ፡፡
ጥ/ ለወደፊት በምን ሁኔታ ሕይወትን መቀጠል አስበሻል?
መ/ አሁንማ እድሜ ለጥላ ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር...ስራም እየሰራሁ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜም ትዳር እመሰርታለሁ...ልጅም እወልዳለሁ ብዬ አስባለሁ...እንግዲህ እግዚ ሀር እንደፈቀደ እኖራለሁ፡፡ አሁንማ ጊዜውም ተለውጦአል፡፡ እራሱን የሚያታልል ካልሆነ በስተቀር በኤችአይቪ ቫይረስ ምክንያት መሞት ቀርቶአል፡፡ ሁሉም ሰው በትክክል ከሐኪም ጋር በመመካከር ሕይወቱ እንዲቀጥል ማድረግ ይችላል፡፡
---------////---------
ከላይ ያነበባችሁት የአንዲት የጥላ ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር አባል ምስክርነት ሲሆን በተከታይነት የማህበሩ አመሰራረትና እንቅስቃሴን በሚመለከት ከሌላ የማህበሩ አባል ያገኘነውን እናስነብባችሁ፡፡
ጥ/ ጥላ ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር መቼ ተቋቋመ?
መ/ ጥላ ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር የተመሰረተው በህዳር ወር 1995/አመተ ምህረት ነው። ማህበሩ የተመሰረተው በ5/ ሴቶች አማካኝነት ሲሆን በጊዜው የመጀ መሪያው ስራው ያደረገውም ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ወደ መድረክ እንዲወጡ በማድረግ ህብረተሰቡን እንዲያስተምሩ እና እራሳቸውንም በምን መንገድ ጤንነታቸውን መጠበቅ እንደሚችሉ ማስተማር ነበር፡፡ ቀስ በቀስ የማህበርተኛው ቁጥር ከፍ እያለ ወደ 30/ የደረሰ ሲሆን የስራ ድርሻውም እያደገ በመምጣቱ እርጉዝ ሴቶች ወደጥላ እንዲመ ጡና አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እንዲሁም ባሎቻቸው የሞቱባቸውን ሴቶች ወደ ማህበሩ በማምጣት አንዳንድ ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግ በተጨማሪም በተለያዩ ወረዳዎች በመግባት ስለኤችአይቪ ትምህርት መስጠትና ህብረተሰቡ እራሱን እንዲያውቅ የሚያ ስችሉ ቅስቀሳዎችን ያካተተ ነበር። በተለይም በህብረተሰቡ ዘንድ በጊዜው ይታይ የነ በረውን የአድሎና መገለል ሁኔታ ለመቀየር ማህበሩ የቻለውን ስራ ተሰርቶአል፡፡
ጥ/ አድሎና መገለል ምን ያህል እንደነበር ማሳያ የሚሆን ...የምታስታውሱት ነገር አለ?
መ/ ለማስታወስ ያህል፡-
..... አንዲት በእድሜያቸወ ትልቅ የሆኑ ሴት ለጉዋደኛቸው ሲያወሩ እንዲህ አሉ፡፡ ... ዛሬ ይለይልኝ ብዬ ...እከሊትን... ግጥም አድርጌ ጨበጥኩዋት...ይላሉ፡፡ ....ጉዋደኝየ ውም...ውይ.. ውይ.. ውይ..እንዴት ደፈሩ? ይሉዋቸዋል፡፡ እንዴ...ምን ላድርግ ...አብሬ ኖሬያለሁ...እንዲያው ዝም ብሎ ማለፍ ልክ አይደለም ብዬ...አስቀድሜ እጄን በነጠላዬ ጥቅልል አድርጌ የራሱ ጉዳይ ብዬ ጨበጥኩዋታ... .. ብለው መልሰዋል፡፡
የአድሎና መገለል ሁኔታ እጅግ አስከፊ ስለነበር ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሰዎች በተቻለ መጠን እራሳቸውን በመደበቅ እስከሞት የሚደርሱበት እጅግ ፈታኝ ሁኔታዎች አልፈ ዋል፡፡ ዛሬ ግን ሁኔታው ሙሉ በሙሉ ተለውጦአል ባይባልም እንኩዋን ተሸሽሎአል፡፡
ጥ/ የማህበሩ የስራ እንቅስቃሴ ከምን ደርሶአል?
መ/ ጥላ በአሁኑ ሰአት 400/አራት መቶ አባላት አሉት፡፡ እነዚህ አባላት የገቢ ማሰባሰብን በሚመለከት፣ እራሳቸው የሚሰሩት ስራን መፍጠር እንዲሁም የማስተማር ስራን በሚያከናውኑበት ወቅት ትንሽ ክፍያ ይሰጣቸዋል ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በቫይረሱ ምክንያት ወላጆቻቸውን ያጡ ልጆች በምግብ እና አልባሳት በኩል የሚደገፉበት ሁኔታ ተመቻችቶአል፡፡ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ እናቶችም የተለያዩ ስልጠናዎችን እየወሰዱ በስራ ላይ የሚሰማሩ ስለሆነ ኤችአይቪ ማለት የህይወት ማብቂያ እንዳልሆነ እንዲያስቡ የሚያስችል አሰራር ተዘርግቶአል፡፡
ጥ/ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ወደትዳር አለም ለመግባትና ልጅ ለመውለድ ሲያስቡ ማህበሩ ምን ያማክራል?
መ/ አንዲት ትዳር የሌላት አባል ይህንን ሰው ማግባት እፈልጋለሁ ስትል ሰውየውን ይዛ ወደማህበር ትቀርባለች፡፡ ማህበሩም ባል ስታገባ ተያይዞ ሊመጣ የሚችለውን ተዛማጅ ችግር እንዲሁም ወሲብ በሚፈጽሙበት ጊዜ ከኮንዶም ውጭ መሆን እንደሌለበት እና ልጅ በመውለድ እና በማጥባት በኩል ምን ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባት እና በፍጹም ከሐኪምዋ መራቅ እንደሌለባት ምክር እንሰጣለን፡፡
ጥ/ የማህበሩ አባላት ማህበሩን የሚደግፉ ናቸው ወይንስ ከማህበሩ ድጋፍ የሚፈልጉ ናቸው?
መ/ በአብዛኛው ወደማህበሩ የሚመጡት ተቸግረው ነው፡፡ ከፊሉ መጠለያ እንኩዋን የለ ውም። ግማሹ በማህበረሰቡ መገለል ደርሶበት ይመጣል። ሌሎቹ ደግሞ ልጆቻቸውን ማሳደግ ይሳናቸዋል፡፡ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሴቶች በተለይም ቤተሰብ እንኩዋን አው ጥቶ ሲጥላቸው መጥተው ማህበሩ ዘንድ ይወድቃሉ። ወደማህበሩ የሚመጡትን ሁሉ እንደችግራቸው እየተመለከተ እንዲያገግሙ ሁኔታዎችን ያመቻችላቸዋል። በእርግጥ እየ ተለወጡ ሲመጡ እነርሱም በተራቸው ሌሎች ሰዎችን መርዳትና መደገፍ ይጀምራሉ፡፡
ጥ/ ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ልጅ ሲወልዱ ለልጁ የሚደረገውን የህክምና ክትትል እንዳይቋረጥ ማህበሩ ምን አስተዋጽኦ ያደርጋል?
መ/ ማንኛዋም ከቫይረሱ ጋር የምትኖር ሴት በማህበሩ መዝገብ ትመዘገባለች፡፡ ልጅ ከወለዱ በሁዋላ ደግሞ ማህበሩ ለተወለዱት ልጆች የሚያደርገው ድጋፍ ስላለ እናቶቹ በምንም ምክንያት አይጠፉም። የህክምና ክትትሉን ማድረግ አለማድረጉዋን እግረ መንገድ ስለምንከታተል በእኛ ዘንድ እንደችግር የሚታይ አይደለም፡፡
ማንኛዋም የማህበሩ አባል ልጅዋ ከቫይረሱ ጋር እንዲኖር አትፈቅድም...በፍጹም አትፈልግም፡፡
ጥ/ ማህበሩ በቀጣይነት እንዲዘልቅ ድጋፍ ከማግኘት ባሻገር ምን በማድረግ ላይ ይገኛል?
መ/ ጥላ ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር የሚኖሩ ሴቶች ማህበር እስከአሁን ባደረገው እንቅስቃሴ ባገኘው ድጋፍ ብዙ ነገር ሰርቶአል፡፡ አባላቱ በማህበር እየተደራጁ የራሳቸውን ስራ እንዲሰሩ አስችሎአል፡፡ ማህበሩ እራሱ ትልልቅ ማሽኖችን በመግዛት ብዙ አባላትን ባሳተፈ መልኩ የራሱን ገቢ የሚያገኝበት ስራ በመስራት ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ድጋፍ ከማግኘት ጎን ለጎን የራሱንም ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

              የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የዛሬ ሳምንት በኮንጎ ብራዛቪል ከሴንተራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር የሚያደርገው ወሳኝ ጨዋታ እንደዘበት ደረሰ፡፡ ዋልያዎቹ በዚሁ ወሳኝ ፍልሚያ አድራጊነት ብቸኛው አማራጫቸው ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በበቂ የዝግጅት ግዜ እና የተጨዋቾች ስብስብ ሳይሰራ መቆየቱና የወዳጅነት ጨዋታ አለማድረጉ ያለውን እድል አስጨናቂ አድርጎታል፡፡ ዋልያዎቹ በኮንጎ ብራዛቪል መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን ካሸነፉ ብራዚል በ2014 እኤአ ላይ ለምታዘጋጀው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ በአፍሪካ ዞን ለሚደረገው የ10 ብሄራዊ ቡድኖች የመጨረሻ ጥሎ ማለፍ ማጣርያ ይበቃሉ፡፡ በምድብ 1 ሌላ ጨዋታ በደርባን በሚገኘው የሞሰስ ማዲባ ስታድዬም ደቡበ አፍሪካ ቦትስዋናን ታስተናግዳለች፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ከምድባቸው የማለፍ እድል የሚኖራቸው ኢትዮጵያ ከተሸነፈች ብቻ ነው፡፡ በምድቡ ሁለተኛ ደረጃ ይዛ የምትገኘው ደቡብ አፍሪካ የማለፍ እድል የሚኖራት ቦትስዋናን ካሸነፈች በኋላ ኢትዮጵያ ከሴንተራል አፍሪካ ሪፐብሊክ ጋር አቻ ከወጣች ወይንም ከተሸነፈች ብቻ ይሆናል፡፡ በምድቡ በሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ቦትስዋና በበኩሏ ማለፍ የምትችለው ደቡብ አፍሪካን ማሸነፍ ከቻለች እና ኢትዮጵያ በሴንተራል አፍሪካ ከተረታች ይሆናል፡፡
የቦትስዋናው ጋዜጣ ሜሜጌ በድረገፁ እንደፃፈው ዜብራዎቹ በደቡብ አፍሪካ በሚኖራቸው ጨዋታ በቀላሉ 3 ነጥብ እንደማይጥሉ እና እጅ እንደማይሰጡ አትቷል፡፡ ደቡብ አፍሪካ ለወሳኙ ጨዋታ በጣም ጠንካራ የቡድን ስብስብ ለማዋቀር ደፋ ቀና ስትል መሰንበቷን ሲያወሳም፤ ከ23 የባፋና ባፋና አባላት ከ8 በላይ በአውሮፓ ፕሮፌሽናል ደረጃ የሚጫወቱ መሆናቸውን ጠቁሟል፡፡ ቦትስዋና ለሳምንቱ ጨዋታ በአብሳ ፕሪሚዬር ሊግ የሚጫወቱ ተጨዋቾችን እንዳሰባሰበች የሚገልፀው ጋዜጣው እነዚህ ልጆች በደቡብ አፍሪካ ሊግ ባላቸው ከፍተኛ ልምድ ጨዋታው የካይዘር ቺፍ እና የኦርላንዶ ፓይሬትስ ደርቢ ይመስላል ብሏል፡፡የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እያደረገ ባለው ዝግጅት አንድም የወዳጅነት ጨዋታ አለማሳቡ የሳምንቱን ግጥሚያ አቋሙን ሳይፈትሽ የሚደርስበት ሆኗል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በተለያዩ አገራት ለፕሮፌሽናል ቅጥራቸው የተሰማሩ ምርጥ ተጨዋቾችን በቶሎ ማሰባሰብ ባይችሉም፤ 32 ተጨዋቾችን በመጥራት እየተዘጋጁ ነው፡፡ በብሄራዊ ቡድኑ ስብስብ በደቡብ አፍሪካ ሊግ የሚጫወተው ጌታነህ ከበደ፤ በሱዳን ሊግ ያለው አዲስ ህንፃ፤ በእስራኤል ያለው አስራት መገርሳ እንዲሁም በስዊድን ያለው ሳላዲን ሰኢድ በቶሎ አለመካተታቸው በቡድኑ መቀናጀት የተወሰነ ተፅእኖ ሊፈጥር ይችላል፡፡ በዝግጅት ቡድኑ ጊዮርጊስ 11፤ ኢትዮጵያ ቡና 4፤ ደደቢት 3፤ መከላከያ 2 ፤ መብራት ሃይል 2 ተጨዋቾች ሲያስመለምሉ በ2006 የውድድር ዘመን ፕሪሚዬር ሊጉን የሚቀላቀለው የዳሸን ቢራ ክለብ 3 ተጨዋቾች በማስመረጥ ብሄራዊ ቡድኑን ማጠናከሩ አስደንቋል፡፡ከደቡብ አፍሪካ ጋር ተደርጎ በነበረ ጨዋታ እያንዳንዳቸው ሁለተኛ የቢጫ ካርዳቸውን ያዩት የኋላው ደጀን አይናለም ሃይሉና ግብጠባቂው ጀማል ጣሰው በሳምንቱ ጨዋታ በቅጣት አይሰለፉም፡፡

ጆን ማን “The On’s Share” በሚል ርዕስ የፃፈው መፅሃፍ “የጃንሆይ ወርቅ መዘዝ” በሚል ርዕስ በሙሉቀን ታሪኩ ተተርጉሞ ለንባብ በቃ፡፡
መፅሃፉ የአገሪቱ የቀድሞ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማርያም፣ ከምዕራባውያን በተለይ ከአሜሪካ ድጋፍ በማግኘት የተራቡ ወገኖችን ለማበራከት የነደፉት እቅድ ባለመሳካቱ ወደ ሩሲያ መዞራቸውን፣ ከአንድ ባንክ የተበደሩትን 200 ሚሊዮን ዶላር ከሩሲያ የጦር መሳሪያ ለመግዛት ማዋላቸውንና ሌሎች ጉዳዮችን ይገልፃል፡፡ በኤችዋይ ኢንተርናሽናል አታሚዎች የታተመው ባለ 173 ገፅ መፅሃፍ፣ በ40.50 ብር እየተሸጠ ነው።

ኩኑዝ ኮሌጅ ከደረጃ ሁለት እስከ አራት በአካውንቲንግ ያስተማራቸውን 81 ተማሪዎችና ሁለት መፅሃፍት ዛሬ ከጠዋቱ 3 ሰዓት በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት ትያትርና ባህል አዳራሽ እንዲያስመርቅ አስታወቀ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ረዳት ፕሮፌሰር በድሉ ዋቅጅራ በክብር እንግድነት ይገኙበታል ተብሎ በሚጠበቀው የምረቃ ሥነስርዓት ላይ “የኢትዮጵያ የትምህርት ችግሮች ያስከተለው ኪሳራና መፍትሄዎች” የሚለውና “ወርቃማ ቁልፍ” የተሰኘ የእንግሊዘኛ ማስተማሪያ መፅሃፍ ይመረቃሉ ተብሏል፡፡ መፅሃፎቹን ያዘጋጁት የኩኑዝ ኮሌጅ እና የሜሪት የቋንቋ ትምህት ቤት ባለቤትና ፕሬዝዳንት አቶ ተስፋዬ ለጋ ናቸው፡፡
በተያያዘ ዜና ቅድስት ልደታ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ በነርሲንግ፣በፋርማሲና በህክምና ላብራቶሪ የሰለጠኑ 169 ተማሪዎችን ነገ ከጠዋቱ 2 ሰአት፣ አምስት ኪሎ በሚገኘው የጠቅላይ ቤተክህነት አዳራሽ ያስመርቃል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በሌላም በኩል ኒው ጄኔሬሽን ዩኒቨርስቲ ኮሌጅ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 250 ተማሪዎች ዛሬ ያስመርቃል። ተማሪዎቹ የሚመረቁት ሜክሲኮ አደባባይ በሚገኘው የአፍሪካ ህብረት አዳራሽ ነው፡፡

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የትያትር ጥበባት መምህር የሆኑት አቶ ኤፍሬም ለማ ያዘጋጁት “መሰረታዊ የፊልም ድርሰት አፃፃፍ ዘዴ” መፅሃፍ ነገ ይመረቃል፡፡ መፅሃፉ በቀኑ 8ሰዓት የሚመረቀው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ስድስት ኪሎ ግቢ፣ ኔልሰን ማንዴላ አዳራሽ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ትያትር በኢትዮጵያ ኪነጥበብ ጉልህ ድርሻ ያላቸውን ከያንያን ዛሬ እንደሚዘክር አስታወቀ፡፡ የትያትር ቤቱ ባልደረቦች “የኢትዮጵያ ብሄራዊ ትያትርን በአዲስ ራዕይ” በሚል መርህ በሚያቀርቡት ዝግጅት ላይ በትያትር ቤቱ የሰሩ እና ሌሎች አንጋፋ ባለሙያዎች ልምዳቸውን የሚያካፍሉ ሲሆን የቀይ ምንጣፍ አቀባበልና የምሳ ግብዣ እንደሚደረግላቸው ትያትር ቤቱ ጨምሮ ገልጿል፡፡

Saturday, 31 August 2013 12:40

ላ-ቦረና ሰኞ ይመረቃል

በኢንጂል አይስ ፊልም ፕሮዳክሽን የተዘጋጀውና በደራሲ ዮናታን ወርቁ የተደረሰው ላ-ቦረና ፊልም፣ የፊታችን  ሰኞ በ11 ሰዓት በብሄራዊ ትያትር ቤት ይመረቃል፡፡ በላይ ጌታነህ ዳሬክት ያደረገው ፊልሙ፣ በአንዲት ፈረንሳዊት አንትሮፖሎጂስት ጥናት ላይ ያተኮረ ሲሆን የቦረናን ባህልና ወግ ያንፀባርቃል  ተብሏል፡፡ በፊልሙ ላይ አለም ሰገድ ተስፋዬ፣ ማርያኔ ቤለርሰን፣ አንተነህ ተስፋዬና ሌሎችም ተውነውበታል፡፡ ፊልሙ የ1፡40 ርዝማኔ እንዳለውም ተገልጿል፡፡

Saturday, 31 August 2013 12:38

“ላማ ሰበቅታኒ”

የውድነህ ክፍሌ ፋንታዚ
በፀሐፌ ተውኔትነቱ የምናውቀው ውድነህ ክፍሌ ሰሞኑን “ላማ ሰበቅታኒ” በሚል ርእስ 174 ገፅ ያለው መፅሐፍ እነሆ ብሎናል እንድናነብ፡፡ የመፅሐፉ ደራሲ በመግቢያው ላይ “ይህ መፅሐፍ በአብዛኛው ገደብ የለሹን የስነ-ፅሁፍ ዘውግ በእንግሊዝኛው fantasy የተሰኘውን የአፃፃፍ ቅርፅ ተከትሏል” ይላል፡፡ የስብሐት ገ/እግዚአብሔርን “ስምንተኛው ጋጋታ” ልብ ይሏል፡፡ ነገሩን ካነሳሁት አይቀር አለማየሁ ገላጋይ ባሳተመው “መልክአ ስብሃት” የተሰኘ መፅሐፍ ውስጥ፣ ፀደይ ወንድሙ የተባለች ፀሐፊ፤ “እውን አከል- ህልም፣ አለማዊነትና ህይወት በስምንተኛው ጋጋታ ውስጥ” በሚል ርእስ እንዲህ ስትል ፅፋለች፡- “ይህ አጭር ፅሁፍ የስምንተኛው ጋጋታን የድርሰት ዓለም በመፈተሽ ፋንጣዚ (fantasy) ብቻ ሳይሆን ህልመ-አለማዊ (surrealist) ነው፣ እንዲሁም ከእውን አከል (Virtual reality) አንፃር ሊታይ ይችላል የሚል አቋም ይዞ ተዘጋጅቷል፡፡”
ይህ የፀደይ ወንድሙ የፅሁፍ መግቢያ ለውድነህ ክፍሌ “ላማ ሰበቅታኒ”ም ተስማሚ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ፋንጣዚ (አንዳንዶች እንደሚሉት ፈንጠዝያ) ብቻ አይደለም፤ ህልመ-ዓለማዊ ብቻም አይደለም፡፡ እውን አከል የሆነን ምስል እንድናይ የሚያደርግም ነው፡፡
በምዕራፍ አንድ በወዶ ዘማችነት “እናት ሀገር ወይም ሞት” ብሎ ጦር ሜዳ የዘመተና አንድ እግሩን፣ አንድ እጁንና አንድ ዐይኑን አጥቶ የመጣ ስም የለሽ ሰው… ወደ ቀዬው ሲመለስ ሚስቱ ሌላ አግብታ የጠበቀችው ሰው፤ ከራሱ ጋር የሚያደርገውን መብሰልሰል ምሬቱን ያስደምጠናል።
“አይ እግሬ? በእግሬ ስላሰብኩኝ እንጂ መቼም በጭንቀላቴ ባስብ ከገባሁበት ቤት “አልወጣም” ብዬ መከራከር እችል ነበር፡፡ ግን እኔ ለመሆኔ ደግሞ ምን ምስክር አለኝ? ሞተ ተብዬ ብቀበር አይደለም እንዴ ጡረታዬ እየተበላ ያለው፡፡ ለነገሩስ አሁንስ ላለመሞቴ ምን ማረጋገጫ አለኝ? ከአካሌ ሦስቱ ቀድመውኝ ተቀብረዋል፡፡ በመቶኛ ቢሰላኮ ግማሽ ሊሞላ ምን ይቀረዋል?”
(ምዕራፍ ሁለት፤ ገፅ 9) እያለ ይነግረንና ገፅ 14 “ሰው መሆን መረረኝ! መረረኝ! ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ እልሃለሁ፤ ስትፈልግ ድመት አድርገኝ! ድመት! እደግመዋለሁ ድመት!”
በምዕራፍ ሶስት ድመት ሆኖ በድመትኛ ያወጋናል፡፡ ልክ እንደ ስብሃት ኮምቡጡር፡፡
“እህ! አንተ ኮምቡጡር አይደለህም እንዴ?”
“ነኝ”
“እኮ ኮምቡጡር የኛ ውሻ?”
“አዎን”
“ታዲያ ከመቼ ወዲህ ነወ የሰው ቋንቋ የተማርከው ባክህ?”
“እርስዎ እንጂ የእንስሳት ቋንቋ መቼ ነው የተገለፀልዎት?”
በዚህ የፋንጣዚ አፃፃፍ ገደብ የለሽነት እንደፈለጉ መሆን፣ የፈለጉትን ማለም ይቻላል፡፡ በዚህ ሁሉ መሃከል ግን የሚነግረን እውን አከል ወግ ደግሞ አለ፡፡ በምዕራፍ ሶስት ድመቱ በድመትኛ እንዲህ ያወጋናል፡-
“ድመት ድመትን አትሸውድም… ድመት ቁጣዋም ፍቅሯም ለድመት ፊት ለፊት ነው። ‘አይጤን አትንኩብኝ፡፡’ የሚል ድመት አይጡ እንዲነካበት አይፈልግም፡፡ ድመት ለድመት ድብብቆሽ አይወድም፡፡ የኛ ድብብቆሽ ከአይጥና ከሰው ጋር ብቻ ነው፡፡ ሰው ግን ድብብቆሽ ነው ህይወቱ፡፡ በዚህ ግቢ እንኳን የማየው ድብብቆሽ ያስገርመኛል፡፡ ያውም ትንሽ ሰው በሚኖርበት ቤት፡፡”
እያለ በዚያ ግቢ ወስጥ የሚመለከተውን የሰው ስራ በትዝብት ያወጋናል - ጆሮው ላይ ሎቲ ያንጠለጠለውና ቴሌቪዥን ሲመለከት የሚውለው ድመት፡፡
ከምቾት ኑሮው ባለቤት ነኝ የሚሉ አሮጊት መጥተው፣ ሎቲውን አውልቀው ድጋሚ እንዳይጠፋ ጭራውን ቆርጠው በር ዘግተውበት ይሄዳሉ፡፡ ቁንጫዎች ሰውነቱን ሲወሩት ድመት መሆን በቃኝ! በ…ቃ…ኝ!” ይላል፡፡ በምዕራፍ ስድስት ውሻ ሆኖ ብቅ ይላል - እንዲህ ሊያወጋን፡-
“ሰምቶ መቻል ምንድን ነው?” አባወራው ጠየቀኝ፡፡ ቋንቋዬ አይገባውም፤ ሃሳቤም አይረዳውም፡፡ ብዙ ጊዜ እኛ ውሾች ሰዎች የሚሉንን እንረዳ ይሆናል እንጂ ሰዎች እኛ የምንለውን ሊረዱን አይችሉም፡፡ የሚረዱት ነገር ቢኖር ውሻ ታማኝ ወዳጅ መሆኑን ብቻ ነው። ታማኝ ስለሆንን ከአጥቂ ይከላከሉናል ብለው ልባቸውን ይሰጡናል። ስላልተግባባንም የማየው አይታያቸውም፡፡ የማዳምጠውን አይሰሙም፡፡ እነሱ የሰሙትና ያዩት ብቻ ትክክል እንዲሆን ይፈልጋሉ፤ የኔን ማየት ካላስተዋሉ፣ ስህተቱ የኔ ሆኖ ጀርባዬ ላይ ቆመጥ ያርፍብኛል፡፡
“በተኛሁበት እሪ ብዬ ስጮህ አሳልፈው የሰጡኝ ወዳጆቼ በአስገራሚው አመታቱ አጨበጨቡለት። ሲያጨበጭቡለት እሱና ከስክስ ጫማው ባሰባቸው። እየደጋገመ ሰውነቴ ላይ ዘለለበት፡፡
በቃ…በቃኝ! ስትፈልግ አህያ ወይንም በረሮ አድርገኝ! በረሮ ብሆን ይሻለኛል፡፡
በረሮ!...
(ከምዕራፍ አስራ ሶስት እስከ መጨረሻው) ከበረሮው ጋር እያወጋን እናዘግማለን… ምዕራፍ አስራ ሶስት፤ ገፅ 111 ላይ)
“እኔ ብልጥ ነኝ… አራዳ በረሮ! እንደዚህ ያለ አደጋ ከመድረሱ በፊት በቤቴ ወስጥ ሁለት ውድ ንብረቶች አሉ፡፡ አንዱ ባይሰራም ጥቁርና ነጭ ቲቪ ነው፡፡ ሌላኛው አሮጌ ፊሊፕስ ሬዲዮ! እኔ ለብዙ ጓደኞቼ በችግር ጊዜ ከነዚህ ምሽጐች አትራቁ እላቸዋለሁ፡፡ እነሱ ግን አይሰሙም፡፡ ባለመስማታቸው ስፍር ቁጥር የሌላቸው በረሮዎች ተበልተዋል፡፡
“እኔ ቅፍፍ ካለኝ ለሊትም ቢሆን ከነዚህ ምሽጐች መራቅ አልፈልግም፡፡ በተለይ ቲቪው ይመቸኛል፤ ሰፊ ነው፤ ጭለማው ውጡ ውጡ አይልም፡፡ አቧራና ጥቀርሻው ተፍ ተፍ ይላል፡፡ የሚተነፍገው ሽታ በሀሴት ይሞላል፡፡ እዚህ ቲቪ ውስጥ የሚበላ አይጠፋም… ካሉት ስፍር ቁጥር በረሮዎች ውስጥ በእያንዳንዱ ለሊት በእርጅና፣ በረሃብ፣ በፀብና በህመም የሚሞቱ አሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ለኛ በስጋ ላለነው መኖ ይባላሉ፡፡
በዚህ መፅሐፍ ውስጥ በወዶ ዘማቹ ሰው፣ በድመቷ፣ በውሻውና በበረሮው በኩል የተነገሩን እውነታዎች ብዙ ናቸው፡፡ በረሮዎቹ በአሮጌው ቲቪ ውስጥ ያደረጉት ድንገተኛ ስብሰባ የሚያስተላልፍው መልእክት እንዲሁ ስለ በረሮ ብቻ የሚተርክ ትረካ አይደለም፡፡ ለእያንዳንዳችን ልብ የሚደርስ አንዳች ሹክ የሚለን ነገር አለ፡፡ በረሮው በመጨረሻ ገፅ 174 “በቃኝ!.. ሰለቸኝ!… ቀፈፈኝ! በረሮ መሆን መረረኝ!… ሰው መሆን ይሻለኛል… በቃ… ሰው! ….” ይለናል፡፡
ሰው መሆን ሸጋ ነገር ነው፡፡ እንደኔ ከሆነ የውድነህ ክፍሌ “ላማ ሰበቅታኒ” ሸጋ ፅሁፍ ነው። ሸጋ ነው ስል የአለማየሁ ሞገስን አንድ ቅኔ በማስታወስ ነው፡፡
ጓዒ… ጓዒ ጉባዔ ቃና ድመት
አምጣነ ተክወ ለኪ ልበ ተማሪ ወተት
ትርጉም - አንቺ ድመት የሆንሺው ጉባዔ ቃና
ነይና ወተት የሆነውን የተማሪ ልብ ላሺው
አንባቢዎችስ… እንደ ተማሪ መሆናችን አይደል? የነገ ሰው ይበለን!

 

Published in ጥበብ
Page 1 of 17