የምትሰለጥነው ከወንዶች ጋር ነው፡፡
                   በዓለም ሻምፒዮና በ5ሺ፤ በ1500 ወይንስ በሁለቱም?
                   ከሪከርድ ይልቅ ከእንግዲህ የምጓጓው ለወርቅ ሜዳልያዎች ነው፡፡
                   ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ 4 ውድድሮች አሸንፋ 40ሺ ዶላር አግኝታለች፡፡
    የ24 አመቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ ዘመናዊ የስኬት ሞዴል ልትሆን እንደምትበቃ ሰሞኑን በመላው ዓለም የተሰራጩ ዘገባዎች ያመለክታሉ፡፡ አትሌት ገንዘቤ 2015 ከገባ በኋላ ባስመዘገበቻቸው ውጤቶች በሁሉም የውድድር መደቦች ከዓለም ሴት አትሌቶች በ1404 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ እንደሆነች በኦል አትሌቲክስ ድረገፅ የሰፈረው መረጃ ያመለክታል፡፡ በውድድር ዘመኑ ላይ በአራት የዳይመንድ ሊግ ድሎች በማስመዝገብ በ5000 ሜትር የደረጃ ሰንጠረዡን በ6 ነጥብ ልዩነት  የምትመራው ገንዘቤ እስከ 40ሺ ዶላር የተሸለመች ሲሆን ለዳይመንድ ዋንጫው ግንባር ቀደም ተፎካካሪ ሆናለች፡፡
በ2015 የውድድር ዘመን መግቢያ በዓለም አትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር የኮከብ አትሌቶች ምርጫ ከመጨረሻዎቹ ሶስት እጩዎች አንዷ የነበረችው ገንዘቤ፤ ከዚያ በኋላ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ የላውረስ አዋርድ ተሸላሚ ለመሆን በቅታለች፡፡ በከወር በኋላ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ቤጂንግ ላይ የምታስመዘግበው ውጤት በዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ያለተቀናቃኝ ተሸላሚ እንድትሆን ያበቃታል፡፡ ገንዘቤ ዲባባ ከእነ ደራርቱ፤ ጌጤ ዋሚ፤ እጅጋየሁ ዲባባ፤ ጥሩነሽ እና መሰረት ደፋር በኋላ በሚያስገርም የአትሌቲክስ ስብእና ወደ ዓለም የወጣች የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ዘመናዊ የስኬት ሞዴል ሆና መታየት ያለባት አትሌት ናት፡፡ በአሁኑ ወቅት በስፖርቱ አለም በተለይ በአትሌቲክስ ውድድሮች ሪከርዶችን ለማስመዝገብ እጅግ ወሳኝ ከሆነው ተፈጥሯዊ ክህሎት ባሻገር ሌሎች ቅድመ ዝግጅቶችን በተሟላ መንገድ በማግኘት ገንዘቤ ዲባባ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ ወቅታዊ የመነሻ ምልክት መሆን ትችላለች፡፡ በተለያዩ ውድድሮች ለሪከርድ ፍጥነት የሚመደቡ አሯሯጮችን በመጠቀም ፤ በቴክኖሎጂ የታገዙ የመሮጫ ጫማዎችና ትጥቆችን በተሟላ ሁኔታ በማግኘት፤ ዘመናዊ ህክምናዎች እና መድሃኒቶች በአጭር ጊዜ ከጉዳት ለማገገም በመቻል፤ እጅግ ዘመናዊ የስልጠና፤ የአመጋገብ እና የስነልቦና ዝግጅቶች በማድረግ ገንዘቤ ዲባባ ከሷ በፊት ከነበሩ አትሌቶች የላቀ እድገት በማሳየት ላይ ናት፡፡
በዓለም አትሌቲክስ ባለፉት 5 የውድድር ዘመናት ገንና እየወጣች ያለችው ገንዘቤ ካስመዘገባቻቸው ከፍተኛ ውጤቶች መካከል 2 የወርቅ ሜዳልያዎች በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ፤ 1 የብር ሜዳልያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ማግኘቷ ይጠቀሳል፡፡ ከዚያ ባሻገር 3 የፍፃሜ ውድድሮች በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ያደረገችበት ልምድ አላት፡፡ በዳይመንድ ሊግ በ1500 እና በ5ሺ ሜትር ዋንኛ ተቀናቃኝ የሆነችው ገንዘቤ በአጠቃላይ በ8 ከተሞች ስምንት አስደናቂ ድሎች በዳይመንድ ሊግ ውድድሮችም አስመዝግባለች፡፡
ቤጂንግ ላይ በ5ሺ ፤1500 ሜትር ወይንስ በሁለቱም?
እንደአይኤኤኤፍ ዘገባ በመካከለኛ ርቀት የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ውድድሮች በልዩ ብቃት ፍፁም የበላይነት ያሳየ አትሌት ብዙም አጋጥሞ አያውቅም፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ግን የ24 ዓመቷ ገንዘቤ ዲባባ በቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሁለት የዓለም ሻምፒዮናነት የወርቅ ሜዳልያዎችን ከመጎናፀፏም በላይ፤ በያዝነው የውድድር ዘመን በ1500 እና በ3000 ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ውድድሮች ከአንድ ጊዜ በላይ የዓለም ሪከርድ በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡
‹‹ከቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ውድድር ተሳታፊነት ወደ ትራክ ለመዞር አስቸጋሪነቱ የተለመደ ነው፡፡ በርግጥ የትራክ ውድድር ለእኔ የሚቀለኝ ይመስለኛል፡፡ ግን መሮጥ የምፈልገው በቤት ውስጥ አትሌቲክስ መወዳደርን ነው፡፡ የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ውድድርን የምመርጠው ባለው ሞቅ ያለ ድባብ እና በመሮጫ መሙ ማጠር ነው›› በማለት ገንዘቤ ተናግራለች፡፡ የገንዘቤ ዲባባ አሰልጣኝ ጃማ አደን ይባላል፡፡ ዘንድሮ በልምምድ ፕሮግራማቸው ከአሰልጣኟ ጋር ለትራክ ውድድሮች ውጤታማነት በመስራት ላይ ማዘንበላቸውን ለአይኤኤኤፍ ዘጋቢ የገለፀችው ገንዘቤ ዲባባ፤ ‹‹ብዙውን ግዜ ልምምድ የምሰራው ከወንዶች አትሌት ጋር በመሆኑ ብቃቴን አንዳጎለብት ጥሩ ግፊት ተፈጥሮልኛል›› ብላለች፡፡ ከአሰልጣኝ ጃማ አደን ጋር ከገንዘቤ ዲባባ ጋር  የሚሰለጥኑት ሌሎቹ ወንድ አትሌቶች በ800 ሜትር የዓለም ሻምፒዮና የነሐስ ሜዳልያ ባለቤት የሆነው የጅቡቲው አይናለህ ሱሌይማንና እና የኳታሩ አትሌት ሙሴባ ባላ ይጠቀሳሉ፡፡ጃማ ሞሃመድ አደን በትውልዱ ሶማሊያዊ ሲሆን አገሩን ወክሎ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች በመካከከለኛ ርቀት ይሮጥ የነበረ ነው፡፡ በ እኤአ በተደረገ የዓለም ሻምፒዮና እና በ ኦሎምፒክ ሶማሊያን በመወከል የተሳተፈም አትሌት ነው፡፡ በ800 እና በ1500 ሜትር የተዋጣለት አትሌት ነበር፡፡
በአትሌቲክስ መወዳደር ካቆመ በኋላ ወደ ስልጠናው የገባው ጃማ በኤክሰርሳይስ ፊዝዮሎጂ ከጆርጅ ሜሰን ዩኒቨርስቲ ማስትሬት ዲግሪ የተቀበለ ሲሆን፤ በ1987 እኤአ ላይ በዓለም ሻምፒዮና ለሶማሊያ የወቅር ሜዳልያ ያስገኘው የመካከለኛ ርቀት ሯጭ አብዲ ቢዬሌ አሰልጣኝ በመሆን ያገኘው ስኬት ታዋቂ አድርጎታል፡፡ አሁን ከኢትዮጵያዊቷ ገንዘቤ ዲባባ ጋር በመስራት በስልጠና ሙያው በከፍተኛ ደረጃ ስሙ እየገነነ መጥቷል፡፡
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ባለፈው ሳምንት ባወጣው በ15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ የሚሳተፈው ጊዜያዊ የቡድን ስም ዝርዝር ላይ ገንዘቤ ዲባባ በ5000 እና በ1500 ሜትር እንድትሮጥ መርጧታል፡፡ ይህንኑ አስመልክቶ ግን የተረጋገጠ ነገር ከወዲሁ የለም፡፡ በዓለም ሻምፒዮናው ላይ በየትኛው ርቀት እንደምትወዳደር የምትወስነው በቅርብ ጊዜ ከአሰልጣኟ ጋር በመማከር እንደሆነ የገለፀችው ገንዘቤ፤ በአንድ ውድድር ለመሳተፍ ከወሰንን ምርጫዬ በ5000 ሜትር መሮጥ ነው ብላለች፡፡ ባለፉት የውድድር ዘመናት በሁለት የዓለም ሻምፒዮናዎች እንዲሁም በኦሎምፒክ በ1500 ሜትር ተሳትፋ ገንዘቤ ዲባባ ማጣርያዎቹን እያለፈች ለፍፃሜ ብትወዳደርም ከ8ኛ የተሻለ ደረጃ አላስመዘገበችም፡፡ በ2015 እኤአ ላይ እያስመዘገበች ካለችው ስኬት አንፃር አሁን ዋንኛው ጉጉቷ ከሪከርዶች ይልቅ በዓለም ሻምፒዮና ወይንም በኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳልያዎች ማግኘት እንደሆነ ገልፃለች፡፡
‹‹ሁሉም ከእኔ የሚጠብቀው የወርቅ ሜዳልያ ነው፡፡ እናም ይህን ማሳካት አለብኝ፡፡ በተለይ ታላቅ እህቴ ያገኘችውን ስኬት መድገም ወይም ማሻሻል  አለብኝ፡፡›› ስትል ተናግራለች፡፡ ‹‹ህልም አለኝ፡፡ በርግጥ ህልሜ ሪከርዶችን መስበር ብቻ አይደለም፡፡ ወደፊት ግን የ1500 ሜትር ብቻ ሳይሆን የ5000 ሜትር እና የ800 ሜትር ክብረወሰን መስበር እፈልጋለሁ›› በማለትም ስለወደፊት እቅዷ አስተያየት ሰጥታለች፡፡
ከወር በኋላ ቤጂንግ ላይ በሚካሄደው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ1500 እና በ5000 ሜትር ደርባ ስለመወዳደሯ ወይንም በአንዱ ርቀት ስለመወሰኗ የመጨረሻ ውሳኔዋ በጉጉት ከገንዘቤ ዲባባ ይጠበቃል፡፡ ከሞናኮው የ1500 ሜትር የዓለም ሪከርድ ሩጫዋ በኋላ በሰጠችው አስተያየት ከአሰልጣኟ ጋር በመመካከር የምትወስነው እንደሆነ የገለፀችው ገንዘቤ በዓለም ሻምፒዮና ላይ ዋናው ትኩረቷ 5000 ሺ ሜትር ላይ ለመወዳደር መሆኑን ጠቁማለች፡፡ በአካል በቃት፤ በዝግጅት ትኩረት እና በስነልቦናም ዝግጅቷ ለ5000 ሜትር መሆኑንም አስገንዝባለች፡፡ ሌትስራን ድረገፅ በሰራው ትንተና ገንዘቤ ቤጂንግ በምታስተናግደው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በሁለቱም ርቀቶች መሮጥ ትችላለች፡፡ የ1500 ሜትር ሁለት የማጣርያ ውድድሮች በዓለም ሻምፒዮናው አንደኛና ሁለተኛ ቀኖች እንዲሁም ፍፃሜው በአራተኛ ቀን ከተደረጉ በኋላ 5000 ሜትር ማጣርያው በስድስተኛው ቀን እንዲሁም ፍፃሜው በሻምፒዮናው 9ኛ ቀን ስለሚደረግ ለገንዘቤ የተመቸ መርሃ ግብር ነው ብሏል ሌትስ ራን ድረገፅ፡፡
ከሞናኮው የሪከርድ ገድል በኋላ ገንዘቤ ዲባባ በሰጠችው አስተያየት ክብረወሰኑን በማሳካቷ ታላቅ እህቷ ጥሩነሽ ዲባባ እና የኢትዮጵያ ህዝብም በተመሳሳይ ደስተኛ የሆናሉ ካለች በኋላ ወደፊት የርቀቱን ሪከርድ እንደምታሻሽል እና በ5 ሺህ ሜትርም ክብረ ወሰን ለመስበር መስራት ሌላው ትኩረቷ እንደሆነ ተናግራለች፡፡ የ5ሺ ሜትር ሪከርድ ለመስበር የሚኖራትን እቅድ ከዓለም ሻምፒዮናው በኋላ ለመተግበር እቅድም እንዳላት አስታውቃለች፡፡
ሪከርዶቿን  ከሷ በቀር የሚሰብር ላይኖር ይችላል
የ24 ዓመቷ አትሌት ገንዘቤ ዲባባ ከሳምንት በፊት በሞናኮ በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር በ1500 ሜትር አዲስ የዓለም ሪከርድ ማስመዝገቧ በከፍተኛ ደረጃ የምትደንቅበት ሆኗል፡፡ በ1500 ሜትር ገንዘቤ የሰበረችው አዲስ የዓለም ሪከርድ በ3 ደቂቃዎች ከ50.07 ሴኮንዶች የተመዘገበ ነው፡፡ የመካከለኛ ርቀት ሪከርድን አንዲት ኢትዮጵያዊ ሴት አትሌት በዓለም የአትሌቲክስ መድረክ ለማስመዝገብ ስትበቃ ገንዘቤ ዲባባ በታሪክ የመጀመርያዋ ሆናለች፡፡ ገንዘቤ የሰበረችው የ1500 ሜትር ሬከርድ ለ22 ዓመታት በቻይናዊቷ ኩ ዩንሺያ የተያዘ እና ሰዓቱን ለማሻሻል የማይቻል ደረጃ ተደርሷል ተብሎ የነበረ ነው፡፡ ቻይናዊቷ አትሌት የ1500 ሜትር የዓለምን ክብረወሰን በ1993 እኤአ ላይ ቤጂንግ ውስጥ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ 50 ሰክንድ ከ 46 ማይክሮ ሰከንድ በመግባት ይዛው ነበር፡፡ ከ22 ዓመታት በኋላ ገንዘቤ ስትሰብረው በ39 ሰከንዶች ፈጥና በመግባት ነው፡፡ በ1500 ሜትር ገንዘቤ ያስመዘገበችው ክብረወሰንን ራሷ ካልሆነች በቀር በሌላ አትሌት ለማሻሻል ብዙ ዓመታት ሊወስድ ይችላል እየተባለ ነው፡፡
የገንዘቤ 4 የዓለምና 6 የአፍሪካ ሪከርዶች
ገንዘቤ ዲባባ በሞናኮ ካስመዘገበችው የ1500 ሜትር አዲስ የዓለም ሪከርድ በኋላ በሩጫ ዘመኗ ያስመዘገበቻቸው የዓለም ሪከርዶች ብዛት 4 ሆነዋል፡፡
ከእነዚህ ሪከርዶች አራቱ የዓለም ሪከርድ ስድስቱ ደግሞ የአፍሪካ ሪከርድ ናቸው፡፡ ገንዘቤ ዲባባ በ1500ሜና በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች እንዲሁም በ2 ማይል ሩጫ የተመዘገቡት ሶስት የዓለም ሪከርዶችን ሌላ አትሌት በድጋሚ ሊሰብር የሚችለው ቢያንስ ከ5 አመታት በኋላ እንደሚሆን በባለሙያዎች ይገለፃል፡፡በሴቶች 5ሺ ሜትር ውድድር ጥሩነሽ ዲባባ የያዘችው ክብረወሰን ከተመዘገበ 6 ዓመታት አልፈዋል፡፡
 ይህን ክብረወሰን ለመስበር ገንዘቤ ዘንድሮ ካስመዘገበችው ፈጣን ሰዓት በ8 ሰከንዶች ፈጥና ርቀቱን መጨረስ ይጠበቅባታል፡፡
የገንዘቤ 4 የዓለም ሪከርዶች
1. በ1500 ሜትር ትራክ 3:50.07
2. በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 3:50.07
3. በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 8:16.60
4. በ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 14:18.86
የገንዘቤ 6 የአፍሪካ ሬከርዶች
1. በ1500 ሜትር በትራክ 3:50.07
2. በ1500 ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 3:50.07
3. በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 8:16.60
4. በ5ሺ ሜትር የቤት ውስጥ አትሌቲክስ 14:18.86
5. በ2000 ሜትር ትራክ 5:27.50
6. በ3ሺ ሜትር ትራክ 8:26.21

 ምርጫው አገሪቱ በዴሞክራሲ መራመዷን ያሳያል ብለዋል
               - የዋነኛው ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ ሌላ ምርጫ እንዲካሄድ ጠይቀዋል
   አወዛጋቢውና ደም አፋሳሹ የብሩንዲ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ባለፈው ማክሰኞ የተካሄደ ሲሆን ለመምረጥ ከተመዘገቡት 3.8 ሚሊዮን የአገሪቱ ዜጎች መካከል 74 በመቶው ድምጻቸውን እንደሰጡ የብሩንዲ የምርጫ ኮሚሽን ፕሬዚደንት ፔሪ ካልቬር ዳይካሬ ባለፈው ረቡዕ መናገራቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
ህገ መንግስቱ ከሚፈቅድላቸው ውጪ ለሶስተኛ ዙር የስልጣን ዘመን በምርጫ ለመወዳደር መወሰናቸው ከፍተኛ ተቃውሞ ያስነሳባቸው የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ፣ ሃሳባቸውን እንዲቀይሩ ጫና ቢደረግባቸውም በእምቢተኝነት በተወዳደሩበት ምርጫ ድምጽ የሰጡ ሲሆን ምርጫው ብሩንዲ በዲሞክራሲ አንድ እርምጃ ወደፊት መራመዷን የሚያሳይ ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡
የአገሪቱ ቀንደኛ ተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት አጋቶን ርዋሳ በበኩላቸው፣ አገሪቱ እንደ አገር እንድትቀጥልና የከፋ ደም መፋሰስ እንዳይከሰት ከተፈለገ፣ የምርጫው ውጤት ይፋ በተደረገ በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ ብሄራዊ የአንድነት መንግስት ሊያቋቁሙ ይገባል ሲሉ ለፕሬዚዳንት ንኩሩንዚዛ ጥሪያቸውን እንዳቀረቡ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ምርጫው የአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ባገለሉበት ሁኔታ የተከናወነ በመሆኑ አሳታፊ አይደለም ያሉት ርዋሳ፣ የሚቋቋመው ጊዜያዊ የብሄራዊ አንድነት መንግስት በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ሌላ ምርጫ እንዲያካሂድም ጠይቀዋል፡፡
አሜሪካ የመንግስት ሃይሎች ተቃዋሚዎችንና የሲቪክ ማህበራትን በሚያዋክቡበት፣ መገናኛ ብዙኃን በተዘጉበትና መራጮች በሚገደዱበት ሁኔታ የተደረገው የብሩንዲ ምርጫ ተዓማኒነት የለውም ማለቷን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ካለፈው ሚያዝያ ወር ጀምሮ ምርጫው ባስነሳው ብጥብጥ ከ100 በላይ ዜጎች መሞታቸውንና ከ170 ሺህ በላይ የሚሆኑትም አገር ጥለው እንደተሰደዱ አስታውቋል፡፡
የተመድ ዋና ጸሃፊ ባንኪ ሙን በበኩላቸው፤የብሩንዲ የፖለቲካ ሃይሎች አገሪቱንና ህዝቧን ወደ ከፋ ጥፋት የሚያስገቡና በአካባቢው አለመረጋጋትን የሚያስከትሉ ተግባራትን ከመፈጸም እንዲታቀቡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በመዲናዋ ቡጁምቡራና በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች በተቃዋሚዎችና በመንግስት ወታደሮች መካከል ግጭት በቀጠለበት ሁኔታ ማክሰኞ ዕለት የተከናወነው ምርጫ የድምጽ ቆጠራ ረቡዕ መጠናቀቁን የዘገበው አልጀዚራ፣ ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በሰፊ ልዩነት ያሸንፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

  እ.ኤ.አ በ2050 ሮቦቶችንና ሰዎችን ኳስ ለማጋጠም ታቅዷል
    በቻይና በተከናወነውና 40 የአለማችን አገራት ቡድኖች በተካፈሉበት የዘንድሮው የአለም ሮቦቶች የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ጃፓን ማሸነፏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በጃፓኑ ቺባ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ የተሰሩ ሮቦቶችን የያዘው ዘ ብሬንስ ኪድስ የተባለው የጃፓን የሮቦቶች ቡድን፣ የቻይናውን ዚጁዳንሰር አቻውን አንድ ለባዶ በማሸነፍ ነው ዋንጫውን ለመሳም የበቃው፡፡
የአለማችን ሮቦቶች የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር እ.ኤ.አ ከ1997 ጀምሮ በየአመቱ ሲከናወን እንደቆየ ያስታወሰው ዘገባው፣ በውድድሩ የሚሳተፉ አገራት ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱንም ጠቁሟል፡፡
የአለማችን ሮቦቶች የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር በሮቦቲክስ ዘርፍ የተሻለ ፈጠራን የማበረታታትና የማስፋፋት አላማ እንዳለው የጠቀሰው ዘገባው፣ እ.ኤ.አ በ2050 በሮቦቶችና በሰዎች መካከል የእግር ኳስ ውድድር የማካሄድ  እቅድ መያዙንም አክሎ ገልጧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

 የአንበሳ ጀግንነት ከአዳኝ ቀስት አያድነውም።
የአፍሪካውያን አባባል
ደስተኛ ህዝብ ታሪክ የለውም፡፡
የቤልጂየሞች አባባል
ጦርነት ላልቀመሱት ጣፋጭ ነው፡፡
የላቲኖች አባባል
ሽንፈት የሚመረው ስትውጠው ብቻ ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል
እውነት የያዘን ሆድ በበላ እንኳን አይበሱትም፡፡
የሃውሳ አባባል
እሳት ያቃጠለው ሰው ሁልጊዜ አመድ ያስፈራዋል፡፡
የሶማሌያውያን አባባል
መጥበሻው ካልጋለ ማሽላው አይፈነዳም፡፡
የዮሩባ አባባል
ዝሆን ላይ የሚጮህ ሞኝ ውሻ ብቻ ነው፡፡
የአንጎላውያን አባባል
በግድ ድስት ውስጥ የገባ አጥንት ድስቱን መስመሩ አይቀርም፡፡
የቼዋ አባባል
አይጥ የገደለ ዝሆን ጀግና አይባልም፡፡
የካሜሩያውያን አባባል
ትዕግስት የገነት ቁልፍ ነው፡፡
የአልባንያውያን አባባል
ቤትህን ከመምረጥህ በፊት ጎረቤትህን ምረጥ፡፡
የሶሪያውያን አባባል
ፈረሱ ከሚጠፋ ኮርቻው ይጥፋ፡፡
የጣልያኖች አባባል
ምንም ዓይነት ምስጢርህን ከራስህ አትደብቅ፡፡
የግሪካውያን አባባል
የሥራ ፈት ምላስ ፈፅሞ ሥራ አይፈታም፡፡
የአፍሪካውያን አባባል

Published in ከአለም ዙሪያ

 መስራቹ ዙክበርግ የዓለማችን 9ኛው ባለጸጋ ሆኗል
    ታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ትርፍ እያገኙ ካሉ 10 የዓለማችን እጅግ ትርፋማ ኩባንያዎች አንዱ መሆኑንና የኩባንያው መስራች ማርክ ዙክበርግም ከዓለማችን ቀዳሚ ቢሊየነሮች 9ኛውን ደረጃ መያዙን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ኤስ ኤንድ ፒ በተባለው የአክሲዮን ገበያን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ 274 ነጥብ 95 ቢሊዮን ዶላር ሃብት ያካበተው ፌስቡክ፣ ከሰሞኑ የአክሲዮን ገበያ ትርፋማነቱ መጨመሩን ተከትሎ፣ ከአለማችን 10 እጅግ ትርፋማ ኩባንያዎች የስምንተኛ ደረጃን ይዟል፡
የኩባንያው ትርፋማነት መጨመሩን ተከትሎ፣ የኩባንያው መስራች የማርክ ዙክበርግ አጠቃላይ ሃብትም 42 ነጥብ 9 ቢሊዮን መድረሱን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
ከሳምንታት በፊት ይፋ የተደረገው የብሉምበርግ የአለማችን ቀዳሚ ባለጸጎች ዝርዝር ማርክ ዙክበርግን የዓለማችን 11ኛው ባለጸጋ ብሎት እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣አራት ቢሊየነሮችን ቀድሞ በ9ኛነት ደረጃ ላይ መቀመጡን ገልጧል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

 አሸባሪ ቡድኖችን ሊቀላቀሉ ይችላሉ በሚል ሰግታለች
  የሞሮኮ መንግስት የአገሪቱ ወጣቶች ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር ሊቀላቀሉ ይችላሉ በሚል ስጋት ለመዝናናት ወደ ቱኒዝያ የሚያደርጉትን ጉዞ መከልከሉን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ወቅቱ የሞሮኮ ወጣቶች ለመዝናናት በብዛት ወደ ቱኒዝያ የሚጓዙበት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ የአገሪቱ መንግስትም የተወሰኑ ወጣቶች አጋጣሚውን ተጠቅመው ወደ ሊቢያ በማምራት ከአሸባሪና ጽንፈኛ ቡድኖች ጋር ሊቀላቀሉና የሽብርተኝነት ስልጠና ሊወስዱ ይችላሉ በሚል ስጋት፣ ሁሉንም የአገሪቱ ወጣቶች ወደ ቱኒዝያ እንዳይሄዱ መከልከሉን ገልጧል፡፡ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከጽንፈኛ ቡድኖች ጋር የሚቀላቀሉ የአገሪቱ ወጣቶች ቁጥር እያደገ መምጣቱ ስጋት የፈጠረበት የሞሮኮ የወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ ወጣቶቹን ከጥፋት ተግባር ለመታደግ ውሳኔውን አስተላልፏል ብሏል ዘገባው፡፡በቅርብ ጊዜ ውስጥ ብቻ 1 ሺህ 600 ያህል ሞሮኳውያን ወደ ሶርያ በማቅናት ጽንፈኛ ቡድኖችን መቀላቀላቸውንና ስልጠና መውሰዳቸውን የገለጸው ዘገባው፣ የአገሪቱ መንግስትም የችግሩን አሳሳቢነት በማጤን የጉዞ እገዳ ውሳኔውን ማስተላለፉን አስታውቋል፡፡
የእንግሊዝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤አሸባሪውን አይሲስ የሚቀላቀሉ ሞሮኳውያን ቁጥር እያደገ መምጣቱን በመግለጽ፣ ለመዝናናት ወደ ሞሮኮ የሚሄዱ ዜጎቹን የሽብር ጥቃት ሰለባ ሊሆኑ እንደሚችሉ በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ማስጠንቀቁንም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡በቱኒዝያ የመዝናኛ ስፍራ በተከሰተው የሽብር ጥቃት 38 የተለያዩ አገራት ዜጎች ለሞት መዳረጋቸውን ተከትሎ፣ እንግሊዝን ጨምሮ በርካታ የአለማችን አገራት ዜጎቻቸው ወደ ቱኒዝያ እንዳይሄዱ መከልከላቸውንም ዘ ኢንዲፔንደንት አስታውሷል፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

 አንጋፋው የሆሊውድ የፊልም ተዋናይ ጆርጅ ክሉኒ፤ የአፍሪካን አስከፊ ግጭቶች በገንዘብ የሚደግፉና ከጦርነቱ የሚጠቀሙ ወገኖችን በመከታተል ለፍርድ ለማቅረብ የሚያስችል አዲሰ ፕሮጀክት ባለፈው ሰኞ መጀመሩን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡ ክሉኒ ከአሜሪካዊው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ጆን ፕሬንደርጋስት ጋር “The Sentry” በተባለ ፕሮጀክት ላይ በጋራ ለመስራት የተቀላቀለ ሲሆን ፕሮጀክቱ በግጭት ቀጠናዎቹ ውስጥና ውጭ ያለውን የገንዘብ ፍሰት በመመርመር፣ ለፖሊሲ አውጭዎች ውጤታማ እርምጃ መውሰድ የሚያስችላቸውን ግብአቶች ለመስጠት ያለመ ነው ተብሏል፡፡
ፕሮጀክቱ መረጃ በማሰባሰብ፣ የመስክ ጥናት በማካሄድና የትንተና ቴክኖሎጂን በመጠቀም ጦርነቶች እንዴት በገንዘብ እንደሚደገፉና ትርፍ እንደሚገኝባቸው ለማጋለጥ ያቀደ ሲሆን ሰዎች በድረገፅ የሚያውቋቸውን መረጃዎችና ምስጢሮች ስማቸውን ሳይገልፁ እንዲጠቁሙ ያበረታታል፡፡  የ54 ዓመቱ ክሉኒ እና ፕሬንደርጋስት ለሮይተርስ እንደገለፁት፤ የዚህ ፕሮጀክት ዓላማ፤ “የጦርነት አትራፊዎች ከወንጀላቸው ያገኙት የነበረውን ጥቅም መንፈግ ነው” ብለዋል፡፡ “ከጦርነቱ የሚጠቀሙ ሰዎች ላደረሱት ጉዳት ዋጋ ሲከፍሉ ሰላም ለማስፈንና ሰብዓዊ መብት ለማስከበር አቅም ይፈጠራል” ብሏል የሁለት ጊዜ ኦስካር አሸናፊው ክሉኒ በሰጠው መግለጫ፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ የአፍሪካ ጉብኝታቸውን ከመጀመራቸው ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ የተጀመረው ፕሮጀክት፣ የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ፣ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳንና ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ ከሰሜን ምስራቅ እስከ ማዕከላዊ አፍሪካ ያሉ ግጭቶችን በገንዘብ የመደገፍ እንቅስቃሴ ምን እንደሚመስል ይመረምራል ብሏል ሮይተርስ፡፡
አዲሱ ፕሮጀክት ክሉኒ ከእነብራድ ፒትና ማት ዴመን የመሳሰሉ ተዋናዮች ጋር በመሰረተው “Not on our watch” የተሰኘ ድርጅትም ድጋፍ እንደሚደረግለት ታውቋል፡፡ የቀድሞው የአሜሪካ ፀጥታ ም/ቤት የአፍሪካ ዳይሬክተር የነበሩት ፕሬንደርጋስት እና ክሉኒ በሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ላይ ሲሰሩ የአሁኑ የመጀመሪያቸው አይደለም፡፡    

Published in ከአለም ዙሪያ

   የአንጋፋው ሰዓሊ ለማ ጉያ እና የሴት ልጁ የሰዓሊ ነፃነት ለማ የስዕል ስራዎች በጋራ የሚቀርቡበት የስዕል ኤግዚቢሽን ዛሬ ከጠዋቱ 5 ሰዓት ጀምሮ ይከፈታል፡፡
የልጅና የአባት የስዕል ኤግዚቢሽኑ የሚከፈተውና ለእይታ የሚቀርበው በአዲስ አበባ በሚገኘው የኦሮሚያ የባህል አዳራሽ ሲሆን፤ ኤግዚቢሽኑን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር አቶ አሚን አብዱልቃድር እንደሚከፍቱት ታውቋል፡፡

 የአንጋፋው ደራሲ አበራ ለማ “ቅንጣት - የኔዎቹ ኖቭሌቶች” የተሰኘ አዲስ የልብወለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለገበያ ቀረበ፡፡ በ264 ገፆች የተመጠነው መፅሃፉ፤ በ70 ብር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡
ነዋሪነቱን በኖርዌይ ያደረገው ደራሲው፤ በበርካታ የአጫጭር ልቦለድና የግጥም መድበሎቹ የሚታወቅ ሲሆን ከቀደምት ሥራዎቹ መካከል፡- “ኩል ወይም ጥላሸት” (የግጥም መድበል)፣ “ሸበቶ” (የግጥም መድበል)፣ “ሕይወትና ሞት” (የአጫጭር ልቦለዶች መድበል)፣ “ሞገደኛው ነውጤ” (ኖቭሌት) እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
በ1980ዎቹ የኢትዮጵያ ደራስያን ማህበር ዋና ፀሃፊ ሆኖ ያገለገለው አበራ ለማ፤ በአሁኑ ሰዓት በኖርዌይ ደራስያን ማህበር የመጀመርያውና ብቸኛው ጥቁር እንዲሁም በአፍ መፍቻው ቋንቋ የሚፅፍ አባል ደራሲ ነው ተብሏል፡፡

“የቤት ሥራ” የቴሌቪዥን ድራማ በቅርቡ መታየት ይጀምራል
   በጋዜጠኛና ፀሐፌ ተውኔት ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ ተደርሶ፣ በካሌብ ዋለልኝ የተዘጋጀው “ከትዳር በላይ” የተሰኘ ዘመናዊ ኮሜዲ ቲያትር የፊታችን ረቡዕ  ከ11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር ይመረቃል፡፡ ቲያትሩ በየሳምንቱ ዘወትር ረቡዕ በተመሳሳይ ሰዓት በዚሁ ቴአትር ቤት እንደሚታይ ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል በቴዎድሮስ ተ/አረጋይ እና በሰዓዳ መሃመድ ተደርሶ፣ በኢሳያስ ግዛው የሚዘጋጀው “የቤት ሥራ” የቴሌቪዥን ድራማ፣በያዝነው ወር መጨረሻ ላይ በኢቲቪ-1 መታየት እንደሚጀምር ተገለፀ፡፡ በቴዎድሮስ የትያትር ኢንተርፕራይዝ ፕሮዱዩሰርነት የሚቀርበው የቲቪ  ድራማ፤ በትዳርና በቤተሰብ ግንኙነት ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው ተብሏል፡፡ በድራማው ላይ አርቲስት ሽመልስ አበራ፣ ሰላም ተፈሪ፣ ስዩም ተፈራ፣ ቶማስ ቶራ፣ ጀምበር አሰፋ፣ ሳምሶን ታደሰ (ቤቢ) እንደሚተውኑበት ለማወቅ ተችሏል፡፡

Page 1 of 17