የደደቢት የእግር ኳስ ክለብ የ2005 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ‹መለስ ዋንጫ› አሸናፊ መሆኑን አረጋገጠ፡፡ የውድድር ዘመኑ ሊጠናቀቅ የሁለት ሳምንት ጨዋታ እየቀረው ደደቢት ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች 17 አሸንፎ፤ በአራቱ አቻ ተለያይቶ እና በ3 ተሸንፎ 55 ነጥብ እና 35 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ነው፡፡ ደደቢት በአንድ ጨዋታ በአማካይ የሚያገባው 2.39 ጎሎች ሲሆን ይህም በሜዳው 2.91 ጎሎች ከሜዳው ውጭ ደግሞ በ1.92 ጎሎች የሚመነዘር ነው፡፡ ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች በተጋጣሚዎቹ ላይ 59 ጎሎች አስቆጥሮ 24 ጎሎችን ያስተናገደው ክለቡ ጎል ማግባት ያቃተው በ1 ጨዋታ ብቻ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮንነቱም በ2014 በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፍ ይሆናል፡፡

የደደቢት እግር ኳስ ክለብ መሥራችና ፕሬዚዳንት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም ለስፖርት አድማስ እንደገለፁት ክለቡ የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን የሆነው ዕቅዱና አላማውን መሠረት አድርጐ በመንቀሳቀሱ ነው ብለው፤ በተገኘው ውጤት የትኩረት አቅጣጫው ለአገሪቱ እግር ኳስ ሙሉ አስተዋጽኦ ማበርከት መሆኑን አስመስክሮበታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ክለቡ በ2002 ዓ.ም ፕሪምየር ሊጉን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀላቀል ለብሔራዊ ቡድን አንድ ተጨዋች ብቻ ማስመረጡን ያስታወሱት ፕሬዝዳንቱ፤ ከአራት የውድድር ዘመን በኋላ ግን በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተሳተፈው ብሔራዊ ቡድን 8 ቋሚ ተሰላፊዎችን ከማስመረጡ በላይ ከአፍሪካ ዋንጫውም በኋላ ከክለቡ 11 ተጨዋቾች ተመልምለው 9ቱ በቋሚነት ተሰላፊነት ማስመረጥ መቻሉ ዓለማውን ያንፀባረቀ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ደደቢት ፕሪሚዬር ሊግን መሳተፍ በጀመረ በ4ኛ የውድድር ዘመኑ ላይ የመጀመሪያውን የሻምፒዮንነት ክብር መጐናፀፉ በክለቡ ታሪክ አበይት ምዕራፍ የሚከፍት ነው ያሉት የክለቡ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል አብዱራሂም፤ዘንድሮ ውድድሩ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያነት ተዘጋጅቶ ደደቢት ዋንጫውን መውሰዱ ልዩ ታሪክ እና ትርጉም ሰጥቶታል ብለዋል፡፡ ለዚህ ውጤት መገኘት ከክለቡ ባለድርሻ አካላት ባሻገር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት ሞተር ሆነው ወሳኝ ሚና በመጫወት፤ የክለቡን ሞራል በመገንባትና የሚሰራን በማነሳሳት መመስገን ያለባቸው እግር ኳስ አፍቃሪያን ናቸው፤ በማለትም ኮሎኔል አወል ለስፖርት ቤተሰቡ ያላቸውን አድናቆት ገልፀዋል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማኅበር ለደደቢት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮናነት የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት ወዲያውኑ በማድረስ የፈፀመው ተግባር በጣም እንደማረካቸው የሚናገሩት ኮሎኔል አብዱራሂም ከከፍተኛ ፉክክር በኋላ ለአሸናፊው ወገን አድናቆት መስጠት በአርአያነት ሊታይ የሚገባው ነው፤ ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከአመት ወደ አመት የፉክክር ደረጃው እያደገ መጥቷል የሚሉት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም፤ ክለቦች ለመሸናነፍ በጥሩ ፉክክር መወዳደራቸው፣ በደረጃ ሰንጠረዥ ላይ ተቀራራቢ ነጥቦች መስተዋላቸው እንደሚበረታታ አስገንዝበው በየመካከሉ ኢንተርናሽናል ውድድሮች በዝተው በውድድር ፕሮግራሞች ላይ በሚፈጠሩ መዛባቶች ከሚያመጡት የመቀዛቀዝ ችግር በስተቀር ጠንካራና ፈታኝ የውድድር ዘመን አሳልፈናል ብለዋል፡፡ ከ4 የውድድር ዘመን በፊት ደደቢት ፕሪሚዬር ሊጉን ለመጀመርያ ጊዜ ሲቀላቀል ባልተጠበቀ ሁኔታ ከባድ ፉክክር በማሳየት የፕሪሚዬር ሊጉን የመጀመርያ ዙር በመሪነት ቢያጠናቅቅም የውድድር ዘመኑን በ2ኛ ደረጃ ነበር የጨረሰው፡፡ በዚሁ የውድድር ዘመን ግን ክለቡ በኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር ከፍተኛ ደረጃ ባለው የጥሎ ማለፍ ውድድር ሻምፒዮን ለመሆን በቅቷል፡፡ ካች አምና በኮንፌደሬሽን ካፕ እየተወዳደረ በመጀመርያ ዙር ማጣርያ ከውድድር የተሰናበተው ክለቡ በፕሪሚዬር ሊጉ ደግሞ ከቡና እና ጊዮርጊስ በመቀጠል በሶስተኛ ደረጃ አጠናቅቋል፡፡ አምና በፕሪሚዬር ሊጉ ለ3ኛ ጊዜ ተሳትፎ በሁለተኛ ደረጃ ያጠናቀቀው ደደቢት በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ የመሳተፍ እድል አግኝቶ እስከ ሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ በመጓዝ ተስፋ ሰጭ ውጤት አሳይቷል፡፡

የብሔራዊ ባንክ ክበብ ሠራተኞች በደል እንደሚፈፀምባቸው ተናገሩ የብሔራዊ ባንክ ክበብ አስተዳደር፣ በሠራተኞቹ ላይ በደል እንደሚፈፅምና ያለ ህግና ማስጠንቀቂያ ከሥራ እንደሚያባርር በደል ደረሰብን ያሉ የክበቡ ሠራተኞች ገለፁ፡፡ የባንኩ የሠራተኞች ክበብ ከባንኩ ሠራተኞች በተጨማሪ ለውጭ ተጠቃሚዎች አገልግሎት በመስጠት እንዲሁም የሠርግ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት ላለፉት 20 ዓመታት ሲሠራ የቆየ ሲሆን በክበቡ ውስጥ በተለያዩ ሙያዎች ተቀጥረው በቋሚነት ሲያገለግሉ የቆዩ 92 ሠራተኞች ለረዥም ዓመታት ዕድገትና የደሞዝ ጭማሪ አግኝተው እንደማያውቁ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ የአመት እረፍት፣ የህመም ወይም የወሊድ ፈቃድ የሚባል ነገር ያልተለመደና እንደ መብትም እንደማይቆጠር ነው በቅርቡ ከስራቸው የተባረሩ የክበቡ ነባር ሠራተኞች የገለፁት፡፡

ሠራተኞቹ በህመምና በሐዘን ምክንያት ከሥራቸው ሲቀሩ በጥበቃ ሠራተኞች ወደ ውስጥ እንዳይገቡ እንደሚከለከሉና በሥራ ላይ እያሉ ለሚደርስባቸው አደጋና የአካል ጉዳት ምንም ዓይነት ህክምና እንደማያገኙ ተናግረዋል፡፡ በሥራ ላይ እያለች እግሯ ላይ ቢላ ወድቆ በደረሰባት ጉዳት ለከፍተኛ ህመም የተዳረገችው የክበቡ ሠራተኛ፤ ከጉዳቷ ጋር በተገናኘ የሥራ ገበታዋ ላይ ባለመገኘቷ ደሞዟ እንደተቆረጠባት ሠራተኞቹ ይናገራሉ፡፡ ሌለው የክበቡ ሠራተኛም ፔርሙዝ ይዞ ደረጃ ላይ ሲወጣ ተንሸራቶ በመውደቁ እግሩ ቢሰበርም የሰበረውን ፔርሙዝ ሂሣብ እንዲከፍል ተደርጐ ከሥራ መሰናበቱን እነዚህ ሠራተኞች ይገልፃሉ፡፡ በክበቡ ውስጥ ለ15 ዓመታት በወጥ ቤት ኃላፊነት የሰሩትና ከህግና ስርዓት ውጭ ያለ ማስጠንቀቂያ የተባረሩት አቶ ቀፀላ ተሾመ፤ የበዓላት ቀናትን ጨምሮ የተለያዩ የትርፍ ጊዜ ሥራዎችን ቢሠሩም የሚያገኙት የትርፍ ሰዓት ክፍያ በሰዓት 3 ብር ብቻ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

ያለ አንዳች ማስጠንቀቂያ ከሥራ ገበታቸው ላይ እንዲታገዱ ከተደረጉ በኋላም ወደ ውስጥ ገብተው ዕቃቸውን ለማውጣት እንኳን መከልከላቸውን የገለፁት አቶ ቀፀላ፤ ቀሪ ደመወዛቸውን ለመውሰድ ወደ መ/ቤታቸው ቢሔዱም ወደ ውስጥ መግባት እንደማይችሉ ተነግሮዋቸዉ፣ ገንዘብ ከፋይዋ ውጪ ድረስ ወጥታ እንደከፈለቻቸው ተናግረዋል፡፡ ከአቶ ቀፀላ ተሾመ ጋር ከሥራ ከታገዱት ሠራተኞች መካከል ወ/ሮ ሰላም አማኑኤል እና ወ/ሮ መሠረት ደምሴ በበኩላቸው፤ የክበቡ አስተዳደር ለሠራተኛው ደንታ የሌለውና የሠራተኛውን መብት ለማክበር ፈፅሞ የማይፈልግ መሆኑን ጠቁመው፤ መብቱን የጠየቀ ሠራተኛ እጣ ፋንታው ከሥራ መታገድ ብቻ እንደሆነ ተናግረዋል። በክበቡ ውስጥ ለሃያ ዓመት የሠሩ ሠራተኞች ቢኖሩም ሁሉም ሠራተኛ ቋሚ አይደለም እየተባለ ኃላፊዎች በፈለጉት ጊዜና ሰዓት ከሥራው ሊያፈቅናሉት እንደሚችሉ ስለሚያስፈራሩ መብታቸውን ለማክበር ወደ ፍርድ ቤት የሚሄዱ ሠራተኞች አለመኖራቸው፣ ለሃላፊዎቹ የልብ ልብ ሰጥቶ እንደፈለጉ እንዲገዙን አድርጓቸዋል ብለዋል - ተበዳዮቹ፡፡ የሠራተኞቹን ቅሬታ አስመልክቶ ምላሽ እንዲሰጡን የክበቡን የሥራ ኃላፊዎች ለማግኘት ባደረግነው ጥረት ከብዙ እንግልት በኋላ የክበቡ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታደሰ መሰረትን ብናገኝም ጥያቄዎችን ማቅረብ ከመጀመራችን “ሥራችንን እያወካችሁ ነው” በማለት በጥበቃ ሠራተኞች ከቢሮአቸው ተገደን እንድንወጣ አድርገዋል፡፡

Saturday, 29 June 2013 11:08

አዘኔታ!

ምሽቱ ገፍቷል፤ ለኮሌጁ ዘበኞች ደግሞ በጣም ገፍቷል፤ አንድ ተማሪ የግቢውን በር ማንኳኳት የሚፈቀድለት እስከ ምሽቱ 4፡30 ድረስ ነው፤ አሁን 4፡40 ሆኗል፤ በጣም መሽቷል፤ በዚህ ሰዓት ደፍሮም የሚያንኳኳ ተማሪ የለም፤ ዘበኞቹም አዝነው አይከፍቱም፡፡ አሁን ወደ ግቢው ለመግባት ሁለት አማራጮች ናቸው ያሉት፡፡ አንድ፣ በአጥር መዝለል ሌላም፣ዘበኞቹን በጥቂት ብሮች መደለል፡፡ ሁለቱም የየራሳቸው አደጋ አላቸው፡፡ በአጥር ሲዘል የተገኘ ተማሪ ቢያንስ ለአንድ ሴሚስተር ከኮሌጁ ይታገዳል። ዘበኞቹ ደግሞ እንደ ጉስቁልናቸው አይደሉም፤ በብር አይታለሉም፤ በዚህ ላይ ሁለት እና ሶስት ስለሚሆኑ እርስ በርስ ይጠባበቃሉ፤ብቻ ደረቆች ናቸው፤ በሰላም ጊዜ እንኳ ተማሪዎችን የሻይ ግብዣ አይቀበሉም፡፡ ሌላኛው የተሻለ እና ብቸኛ አማራጭ ሊሆን የሚችለው ቤርጎ ማደር ነው፡፡ ክፋቱ ግን እርሱ ሁሉንም መፈፀም አይችልም፡፡

“አምላኬ! ምን አይነት ጣጣ ውስጥ ነው የከተትከኝ!” አባቱ ደግሞ ደውለው ነበር፡፡ አደራቸውን ለማደስ፡፡ እሺ ታዲያ አሁን የት ሄዶ ነው? ይህን ያህል ከቶም አምሽቶ አያውቅም፡፡ 4፡53 እንደ አለመታደል ሆኖ ጊዜውም የፈተና ወቅት ነው፡፡ ደብተርና መፅሃፎቼን ለአመል ያህል ልግለጣቸው እንጂ አንዲት ዐረፍተ ነገር እንኳ መረዳት አልቻልኩም፡፡ የስሜት ህዋሳቶቼ በሙሉ ውጭ ነው ያሉት፡፡ ጆሮዎቼ የበሩን መንኳኳት ይጠብቃሉ፡፡ ሲራመድ ዱቄት ላይ ይሄድ ይመስል ኮቴው ባይሰማም መተላለፊያው ላይ ኮቴ ባዳመጥኩ ቁጥር አይኖቼን በር ላይ እሰካለሁ፡፡ አንድ፣ ሁለት፣ ሶስት፣ አራት፣ ከዚያ ድምጹ እየራቀ ይሄዳል፡፡ ጸጥታ፡፡ ነፋስ፡፡ ኃይለኛ ነፋስ፡፡ በመኝታ ክፍላችን ውስጥም ከባድ ጸጥታ ሆኗል። ቀና ብዬ ሌሎች ሶስት የመኝታ ክፍል ጓደኞቼን ቃኘኋቸው፡፡ ሁሉም አንገታቸውን ወረቀት ላይ ደፍተዋል፡፡ ጭንቅላታቸውን መጽሐፍት ውስጥ ደብቀዋል፡፡

እስቲፋኖስ በመሰላቸት ደጋግሞ ፀጉርን ያካል፤ ይፎክታል፤ የዘወትር ልምዱ ነው፡፡ አትክልቲ ጉንጮቹን እጆቹ መዳፎች ውስጥ ቀብሮ ደብተሩ ላይ አድፍጧል፡፡ መኩሪያ አንዳች ነገር ይጫጭራል፣ ሲያጠና እጁ አያርፍም፤ ካልጻፈ አይገባውም ወይም የገባው አይመስለውም፡፡ ክፍላችንንም ቃኘሁት፡፡ ያልተጠረገ ቤት፣ ያልተነጠፈ አልጋ፣ የተዘበራረቁ መጻህፍት፣ ያልተከደነ ደብተር፣ በአልጋው ስር የወደቁ ካልሲዎች፣ ያለቁ እስኪርቢቶዎች… ዐይኔን ወደ ጓደኞቼ መለስኩት። ያልተበጠረ ፀጉር፣ የደፈረሱ አይኖች፣ የጎበጠ ትከሻ፣ መረጋጋት የማይታይበት ፊት… ጥናቴን ትቼ አይኔን ሳንከራትት ጭንቀቴ ገብቷቸው ሶስቱም ካቀረቀሩበት ቀና ቀና እያሉ በቦዙ ዓይኖቻቸው ሲያፈጡብኝ የባሰ ጨነቀኝ፡፡ ሰዓቴን አየሁ፡፡ 5፡10፡፡ ማድረግ የምችለው ነገር ስላልነበር ወጥቼ ቀጥታ ወደ ግቢው በር አመራሁ፡፡ የእስጢፋኖስ የመሰላቸት እና የንጭንጭ ድምጽ ተከተለኝ፡፡ ነፋሻ ምሽት ነው፡፡

እንደምትሀት ይወረወራል ነፋሱ፡፡ ባሕር ዛፎቹን ገንድሶ ሊጥል የፈለገ ይመስላል፡፡ ያ ባይቻለውም ጎንበስ ቀና እያደረጋቸው ነው፡፡ ዛፎቹ መቅኔያቸው እንደተንጠፈጠፈ የሽማግሌ ጉልበቶች እየተንቋቁ አጎንብሰው ይመለሳሉ፡፡ ወደ ግቢው በር እየቀረብኩ በመጣሁ ቁጥር የሰዎች አጀብ ቢጤ ታየኝ፡፡ እርምጃዬን አፈጠንኩ፡፡ ረጃጅም ቅልጥሞቼን አወናጨፍኳቸው፡፡ የክርስቶስ ያለህ! ይህ ተዓምረኛ ልጅ ከወገቡ በላይ ራቁቱን ሆኖ ዘበኞቹ መኻል ቆሟል፤ ቀጫጫ ሰውነቱ በብርድ ይንዘፈዘፋል፤ ረዥም ሉጫ ጸጉሩ ተንጨባሯል፤ ጥቋቁር አይኖቹ ወዲያ ወዲህ ይንከባለላሉ፤ ግትር አፍንጫውን ቅዝቃዜ አርጥቦታል፡፡ ተንደርድሬ መሀላቸው ገባሁ፡፡ አዟዙሬ አየሁት፡፡ ደህና ነው። ቆዳው ብቻ በብርዱ ሳቢያ ተጉረብርቦ ፎጣ መስሏል። የምለውን አጣሁ፡፡ ምላሴ እንኳን በእንዲህ አይነት ቀውጢ ሰዓት ይቅርና በደህናው ጊዜም አይታዘዝልኝም፡፡ በጥያቄ ዐይን አየሁት። ወተት ጥርሶቹ ስስ ከንፈሮቹን ሸርተት አድርጎ አሳየኝ። አሁን የሆነውን ለማወቅ ጊዜ አልፈጀብኝም። ድሮውንም ሳየሁ ጠርጥሬያለሁ፤ እስከ አሁንም መሳቀቄ ራሱ ከንቱ ነበር፡፡ ቶማስን እንኳንስ የመቀሌ ኮሌጅ ማህበረሰብ፣ የመቀሌ ህዝብ ሳያውቀው አይቀርም፡፡

ዘበኞቹ በዚህ መኻል አዝነው ከህግ ውጭ እንዲገባ ፈቀዱለት፡፡ ይህን ጊዜ በእፎይታ ተነፈስኩ፡፡ እንዲያውም ትህትናቸዉ ለጉድ ነበር፤ ይግረምህ ብለው ነው መሰለኝ አንደኛው ዘብ እራሳቸውን ለብርድ አጋልጠው ጋቢያቸውን ከላያቸው ገፈው አለበሱት፡፡ ፊታቸው ላይ ያየሁት ርህራሄ ልቤን ዘልቆ ተሰማኝ፡፡ “የት ነበርክ?!” አልኩት፡፡ ፈገግታ - የእሱ ምላሽ፡፡ ቶማስ፣ “የት ነበርክ?!” ደግሜ ጠየቅሁት፡፡ ንጻታቸው የሚያስፈራ ጥርሶቹን በሰፊው ገለጻቸው፡፡ “የት ነ-በ-ር-ክ?!” አሁንም ፈገግታ፡፡ ትከሻውን ይዤ እንደ ጆንያ አራገፍኩት፡፡ “ለምጠይቅህ ጥያቄዎች መልስ እንድትሰጠኝ እፈልጋለሁ፡፡ የት ነበርክ?! ደግሞስ ልብሶችህስ?! ትከሻውን አማታብኝ፡፡ ይዤው መንገድ ጀመርን፡፡ ትዕግስቴ ተሟጦ ቢያልቅም ምን እንደምለው ግራ ገብቶኛል፡፡ የመጨረሻ ልናገር የምችለው ክፉ ነገር ቢኖር፡- “ከእንግዲህ ስለ አንተ አያገባኝም፡፡ ገደል ግባ!” ይሆናል፡፡ በቃ፡፡ “ጃኬቱን ዛሬም አውልቀህ ሰጠህ አይደል?!” ከግድ-የለሽነት በተቀላቀለ አዎንታ ትከሻውን ነቀነቀ። በወዲያኛው ሳምንት የተገዛ ጃኬት ነበር፡፡

እሱንም አውልቆ በሰጠው ጃኬት ምትክ ነበር የገዛነው። ምናልባት የዋጋው ውድነት አሸንፎት አይሰጥ እንደሁ ብዬ ለአንድ ጃኬት 500 ብር ስንከፍል ቅር አላለኝም ነበር፡፡ ይኸው ጉድ ሰራኝ፡፡ ያለ ወትሮዬ የማደርገውን መቆጣጠር ተሳነኝ፡፡ በድጋሚ ይዤ ወዘወዝኩት፡፡ “ለምስኪኑ አባትህ እንኳን አታዝንላቸውም?! እኔንስ ያለ ዕዳዬ ለምን ታሰቃየኛለህ?! ለምን ነብሴን ታስጨንቃለህ?! ለሰው ማዘን፣ የተቸገረን መርዳት፣ መጥፎ አይደለም፡፡ ግን እንዲህ ቅጥ ሲያጣ ደግሞ በምንም መልኩ ቢሆን ጥሩ ሊሆን አይችልም፡፡ እንዴት ያን ያህል ብር አውጥተን የገዛነውን ጃኬት አውልቀህ ትሰጣለህ?! ለዚያውም በዚህ ብርድ …” አቋረጠኝ፡፡ “ምንተስኖት፣ ሰውየውን ብታያቸው እንዲህ አትልም ነበር፡፡ በዚህ ብርድ በብጣሽ ሸሚዝ ግንብ ስር ኩርምት ብለው ሳያቸው ልተባበራቸው ይገባኝ ነበር፤ ተባበርኳቸው፡፡ እስከ አሁን የቆየሁትም ሳጫውታቸው ነው፡፡ አየህ እናቴ “የተቸገሩ ሰዎች ከምንም በላይ ሰው ይናፍቃቸዋል” ትል ነበር፤ እና ከአንዱ የኔ-ቢጤ ጋር ማውራት ከጀመረች ቀኑ ይመሽ፣ ምሽቱ ይነጋ ነበር…” ጆሮዎቼ በሁለት እጆቼ ደፈንኳቸው፡፡ ሁሌም የሚነግረኝ ይህንኑ ነው፡- እናቴ፣ እናቴ፣ እናቴ … ኪሱ ውስጥ ያለውን ገንዘብ በሙሉ አራግፎ “የኔ-ቢጤ” ለሚላቸው ያከፋፍላል፡፡

“ለምን?” ስል፡- “አየህ እናቴ ድሆችን መርዳት ያለብን ከተረፈን ላይ ቆንጥረን ሳይሆን ከሚያስፈልገን ጭምር ላይ መሆን አለበት፤ ትለኝ ነበር” ነው መልሱ፡፡ የራሱን ትቶ የሌሎች ተማሪዎችን አሳይመንት ይሰራል፡፡ “ተው” ስል እየፈገገ፡- “አየህ እናቴ ከራሷ በፊት ሌሎችን ታስቀድም ነበር” ይላል፡፡ እንዲህ እንደዛሬ ጃኬቱን አውልቆ የሰጠ ጊዜም፡- “ለምን?” ብዬ ስሞግተው፡- “እናቴ ሁለት ነጠላ ካላት አንዱን ለታረዘ ታለብስ ነበር’ ነው ያለኝ፡፡ ምን ዓይነት ልክፍት እንደሆነ አላውቅም፡፡ ለተቸገሩ የሚቸረው ንብረቱን፣ ገንዘቡን እና ጊዜውን ብቻ አይደለም፤ እንባውንም ጭምር ነው፡፡ ሳንቲም አጥቶ ኪሱ ሲራቆት (ያው ሰጥቶ ሲጨርስ) እንባው ይጎርፋል፡፡ ደውሎ አባቱ ላይ ይጮህባቸዋል፤ እንደመታደል ሆኖ ደህና ኑሮ አላቸው አባቱ፤ እናም ገንዘብ ይልኩለታል፡፡ ለአራት ወራት መከርኩት፤ ተቆጣሁት፤ አብሬው ላይ ታች አልኩ፤ አሁን ግን ሰለቸኝ፤ መረረኝ፡፡ እዚህ ሁሉ ጣጣ ውስጥ የገባሁበት ቀን ብላሽ ቀን ነው። አባቱ ናቸው እዚህ ጣጣ ውስጥ የነከሩኝ፡፡ እናም ደግሞ የኮሌጁ ዲን፡፡

ብቻ መጀመሪያ አደራውን ስቀበል ይህን ያህል እቸገራለሁ ብዬ ፈጽሞ አላሰብኩም ነበር፡፡ … ከአምስት ወራት በፊት፣ እዚህ ኮሌጅ በገባሁ ማግስት አንድ አባት ልጃቸውን አስከትለው ወደ ዶርማችን መጡ፡፡ የኮሌጁ የተማሪዎች ዲን አብሮአቸው አለ፡፡ ካሉት አምስት አልጋዎች አራቱ በእኔ፣ በእስጢፋኖስ፣ በመኩሪያ እና በአትክልቲ ተይዘው አንድ አልጋ ብቻ ነው ያልተያዘው፡፡ እንግዳው ሰውዬ እና ዲኑ ጎርደድ እያሉ ክፍሉን ቃኙት፡፡ እንደ አጋጣሚ አራታችንም የዚያ መኝታ ክፍል ተጋሪዎች እዚያው ነበርን፡፡ ዲኑ ሲቀሩ አባትና ልጅ በየተራ ተዋወቁን፡፡ ልጅ ቶማስ፣ አባት ሙሉ ወርቅ ይባላሉ፡፡ ቶማስ በቅጽበት ተዋሀደን፡፡ አራታችን መኻል ሆኖ ሲያወራን ለረዥም ጊዜ የምንተዋወቅ እንመስል ነበር፡፡ ሁኔታው ገርሞኛል፡፡ የመጣንበትን ቦታ፣ የተማርንበትን ትምህርት ቤት፣ ሌላው ቀርቶ ውጤታችንን በየተራ አስለፈለፈን፡፡ እርሱም እንደ እኔ የአዲስ አበባ ልጅ ነው፤ መኩሪያ የሲዳሞ፣ እስጢፋኖስ የጅማ፣ አትክልቲ ደግሞ የዚሁ የመቀሌ ልጅ ነው፡፡ ቀልቤ ቶማስ የጫረው ጨዋታ ላይ እንደሆነ፣ ድንገት ቀና ስል የቶማስ አባት እና ዲኑ ባይናቸው መልዕክት ሲለዋወጡ አየኋቸው፡፡ አፈጠጡብኝ።

ዐይኔን ሰበርሁ፡፡ ተሰናብተውን ሊወጡ በር ጋ ከደረሱ በኋላ ከጓደኞቼ ነጥለው ጠሩኝ፡፡ ከተቀመጥኩበት ተነስቼ ሄድኩ፡፡ አቶ ሙሉ ወርቅ ባንድ እጃቸው እኔን፣ በሌላ እጃቸው ቶማስን ይዘው መንገድ ጀመሩ፡፡ ዲኑ ከጎኔ ሆኖ ተከተለን፡፡ ወደ እርሱ ቢሮ ነበር የሄድነው፡፡ ቶማስን የፊተኛው ክፍል ውስጥ አቁመው እኔን ይዘውኝ ወደ ዋናው ቢሮ ዘለቁ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን አንዳችም አልተናገርኩም። ቀጣዩ ነገር ምን እንደሚሆን በጉጉት ሳይሆን በአግራሞት እየጠበቅሁ ነበር፡፡ ሁለቱ ጎን ለጎን፣ እኔ ከፊት ለፊታቸው ተቀመጥን፡፡ አቶ ሙሉወርቅ “ልጄ…” አሉኝ ንግግራቸውን ሲጀምሩ፡፡ ልክ እንደ ልጃቸው ቶማስ ብስል ቀይ ይሁኑ እንጂ የሱን ያህል ዐይን አይስቡም፡፡ ቀጭን ናቸው፤ ጆሮአቸው ትልልቅ፣ ጥርሶቻቸውና ዐይኖቻቸው ትንንሽ፣ አፍንጫቸው ደግሞ አጠር አጠር ብሎ ወደ ግንባራቸው ሰቀል ያለ ነው፤ ጸጉራቸው ሉጫ ነው፤ ጥቁር ሉጫ፡፡

ጅምር ንግግራቸውን አቋርጠው ኪሳቸውን መዳበስ ጀመሩ፡፡ ከኪስ ቦርሳቸው ጉርድ ፎቶ አውጥተው አቀበሉኝ፤ ያለችበትን የዕድሜ ክልል መገመት የሚያስቸግር ሴት ምስል አለበት፤ በምንም በምንም ቶማስን የምትመስል ሴት ፎቶ፤ ጸጉር፣ ግንባር፣ ዓይን፣ አገጭ፣ አፍንጫ … ሁሉ ነገራቸው ይመሳሰላል ሳይሆን አንድ ነው፤ እህቱ ወይ እናቱ መሆን አለባት፡፡ “ልጄ” ቀጠሉ የቶማስ አባት፡፡ “ልጄ እርሷ የምታያት ሴት የቶማስ እናት ናት፤ አምና ነው በድንገተኛ ሕመም ያረፈችው፡፡ ቶማስ፣ የኔም የሷም ብቸኛ ልጃችን ነው፤ እና ለእርሱ የነበራት ፍቅር ፍፁም ልዩ ነበር፡፡ እኔን ከነመኖሬም አያስታውሱኝም፡፡ ሁለቱ አብረው ይበላሉ፤ አብረው ይጠጣሉ፤ በአንድነት ይጫወታሉ፤ አንድ ላይ ይተኛሉ … አሁን እንግዲህ አስራ ዘጠኝ ዓመቱ ነው፡፡ እስከ አስራ ስምንተኛው ዓመት ማብቂያው ድረስ … ማለትም በሞት እስክትለየው ድረስ ግን ጡቷን ይጠባ ነበር፤ ደረቅ ጡቷን ይመጠምጥ ነበር። በዚህ ሁሉ ጊዜ ውስጥ ለመኻላ እንኳን አንድም ቀን ተለያይተው ተኝተው አያውቁም፤ እና ይህን ሁሉ ያነሳሁት ለምንድነው? …እ… ዲኑ እንደነገሩኝ በኮሌጁ ውስጥ አንድ አልጋ ለሁለት መጋራት አይፈቀድም፡፡ የኔ ልጅ ደግሞ በዚህ በኩል ከፍተኛ ችግር አለበት። በምንም ዓይነት ብቻውን መተኛት አይችልም።

እና አብሮት የሚተኛ ሰው ከተገኘ ያን ማድረግ እንደሚችል ተነግሮኛል፡፡ ማለት፣ ፍቃደኛ ከሆነ ከአንድ ሌላ ሰው ጋር አልጋ እንዲጋራ ተፈቅዶለታል፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ደግሞ እናንተ መኝታ ክፍል ውስጥ ተመድቧል …” ንግግራቸውን ገታ አድርገው አዩኝ፡፡ ስሜቴን ለማንበብ ሳይሆን አይቀርም፡፡ የዲኑ ዓይኖችም እንዲሁ ላዬ ላይ ይተራመሳሉ፡፡ አንገቴን ደፋሁ፡፡ አካሄዳቸው ገብቶኛል፡፡ ቀጠሉ፡- “…እ…ምን ነበር ያልኩት? …እ…አዎ እናም ደግሞ ያች እናቱ፣ ፍጹም ደግ ነበረች፤ ካፏ ነጥቃ ታጎርሳለች፤ ተጠምታ ታጠጣለች፤ ተርባ ታበላለች፤ እሷ መሬት ወርዳ እንግዳን አልጋ ላይ ታስተኛለች፡፡ የብቻ ነበር የሷስ ደግነት፡፡ እንደኔ ልፋት ቢሆን ይሄኔ ስንት ጥሪት ባየቆየን ነበር፡፡ እርሷ ግን ያመጣሁትን ሁሉ አንዳንዴ ለቤት እንኳ እስኪቸግረን ድረስ ታከፋፍለው ነበር፡፡ ቶማስ ታዲያ ከርሷ ብሶ ቁጭ አለ፡፡ ምኑም አይቀረው፡፡ ልብሱ፣ ጫማው፣ ለኪሱ የሚሰጠው ገንዘብ፣ ሁሉንም እናቱ ታደርግ እንደነበረው ተቸግሮ ላያቸው ያከፋፍላል … ታዲያ አሁን እኔ ብዙ ነገር ያስፈልጋልና ከአዲስ አበባ ገንዘብ ብልክለት አንዳችም አይጠቀምበትም፡፡ ይረጨዋል፡፡ ለዚህም ከጎኑ ሆኖ የሚረዳው ሰው ያስፈልገዋል፡፡

በዚህም በኩል ዲኑ ሊተባበሩኝ ፈቃደኛ ናቸው፡፡ ገንዘቡን በሳቸው ስም እልካለሁ …እ… ለትምህርት የሚያስፈልጉ መገልገያ መሳሪያዎች ሆኑ ሌሎች አላቂ የየዕለት መገልገያ ቁሳቁሶች የሚያጋዛው ሰው ያስፈልገዋል፡፡ ይህን ማድረግ የሚችለው ደግሞ እንደ አንተ ተማሪ የሆነ፣ ለተማሪ የሚያስፈልጉትን እቃዎች የሚያውቅ ሰው መሆን አለበት፤ እና በእነዚሀ ሁለት ጉዳዮች ላይ ብትተባበረኝ …እ” ብለው ድንገት ሳግ አፈናቸው፡፡ እንባቸውም ተከተለ፡፡ ነገሮች ግራ አጋቡኝ፡፡ መናገር አልቻልኩም፡፡ ፀጥታ፡፡ የለቅሶ ድምጽ፡፡ ፀጥታ፡፡ የመናገር ተራ ዲኑ ወሰዱ፡፡ የችግሩን ሁኔታ በገባቸው አቅጣጫ ነገሩኝ፡፡ ብተባበራቸው በትምህርቴም ሆነ በሌላ ልጎዳ እንደማልችል ሊያሳምኑኝ ሞከሩ፡፡ ካልፈለግሁ እና የማልችል ከመሰለኝ ግን አለመተባበር ሙሉ መብቴ እንደሆነ አስረዱኝ፡፡ ዝምታ ሰፈነ፡፡ በዚህ ቅጽበት አስቤ ፍቃደኛ ብሆን የሚከተለውን መዘዝ ወይም ፈቃደኛ ባልሆን የሚሰማኝን ፀፀት ማመዛዘን አልቻልኩም።

ፊት ካለው ክፍል የዲኑ ፀሐፊ ታይፕ ስትቀጠቅጥ ይሰማል፡፡ “ላግዝሽ? ታይፕ መምታት እችላለሁ፡፡” የቶማስ ድምጽ፡፡ ማሰብ አላስፈለገኝም፡፡ “እሺ፤ ልተባበራችሁ ዝግጁ ነኝ፡፡” አልኩ፡፡ አቶ ሙሉወርቅ ተንደርድረው በመምጣት አቀፉኝ፡፡ “እንግዲህ እኔም አንተን ቶማስን በማይበት ዐይኔ ነው የማይህ፤ ቃል ኪዳን ፈፀምን ማለት ነው፡፡” አሉኝ፡፡ እኚህ መከረኛ አባት ታዲያ ዛሬም ደውለው ነበር፡፡ ከአሳቤ ስመለስ ጐንበስ ብዬ አየሁት ቶማስን፡፡ አሻቅቦ ያየኛል፡፡ “እሺ አባትህም በሰቀቀን እንዲሞቱ ትሻለህ?!” የሞት ነገር ሲነሳ ስሜቱ በጣም እንደሚነካ አውቃለሁ፡፡ ያለሁበት ሁኔታ ግን ስሜቱን እንድጠብቅለት የሚያደርግ አልነበረም፡፡ የተደበላለቀ ስሜት ሰፍኖብኛል፡፡ ሐዘን፡፡ መታከት፡፡ ንዴት፡፡ ተስፋ መቁረጥ፡፡ ወደ ዶርም ስናመራ መንገድ ላይ እነ እስጢፋኖስን አገኘናቸው፡፡ እኛን ፍለጋ መውጣታቸው ነበር። ቶማስ በወፍራም አዲስ ጃኬት ፈንታ አዳፋ ጋቢ ለብሶ ሲያዩት ምን እንደተከሰተ ለመገመት ጊዜ አልወሰደባቸውም። ሁላቸውም ቃል እንኳን ሳይናገሩ ተያይዘን ወደ ዶርም ገባን፡፡ ብርድ ልብሳችንን ከአልጋችን ላይ አንስቼ አለበስኩት። መቼስ የኔ የምለው ነገር የለኝም፤ ሁሉ ነገር የኛ ሆኗል፤ ጊዜዬ እንኳን የኔ አይደለም፡፡

መኩሪያ እና አታክልቲ ቀኑን ሙሉ ከመጽሐፍ ጋር ሲታገሉ ስለዋሉ በተቀመጡት ማንቀላፋት ጀመሩ፡፡ እስጢፋኖስም ወፍራም ጉንጮቹ ተንጠልጥለዋል። ዐይኖቹ ደክመዋል፡፡ እየተነጫነጨ ራሱን ያካል፡፡ መኩሪያና አታክሊቲ ገፍቶ የመጣ እንቅልፋቸውን መቋቋም ስላልቻሉ ተኙ፡፡ ቶማስ፣ እስጢፋኖስ እና እኔ ብቻ ቀረን፡፡ ብዙም ሳይቆይ እስጢፋኖስ ማላዘን ጀመረ። እስካሁን ባለው ህይወቴ ውስጥ ካጋጠሙኝ ሰዎች ከቶማስ እኩል የሚገርመኝ ሰው ቢኖር እስጢፋኖስ ነው፤ ምንም ነገር አያስደስተውም፤ ሁሌ ይነጫነጫል፡፡ በትምህርቱ ከማንም አያንስም፤ በኑሮውም ብዙ አይጐድለውም፤ ቤተሰቦቹ ከጅማ በየወሩ በቂ ብር ይልኩለታል፤ ግን ሁሌ እንዳላዘነ፣ እንደተነጫነጨ ነው የሚኖረው፡፡ ሲለው የኮሌጁ ምግብ አልተስማማኝም፤ የአገሩ አየር ፀባይ ጥሩ አይደለም፣ እከሌ የሚባል መምህራችን ደካማ ነው፣ ሴቶች አፍጠው ያዩኛል፣ የቤተሰብ ደብዳቤ ዘገየብኝ፣ እያለ እዬዬ ይላል፡፡ ሁሉም ነገር ሞትን ያስመኘዋል፡፡ “ሕይወት ዋጋ ቢስ ናት፣ ከመኖር አስር ጊዜ መሞት ይሻላል፡፡” የሚለው የዘወትር መነባንቡ ነው፡፡

በእርሱ የተነሳ ዶርማችን ውስጥ ሰላም ጠፍቷል። እርሱ መነጫነጭ ሲጀምር ቶማስ እያባበለው ያለቅሳል፡፡ እስጢፋኖስ ግን አይጽናናም፡፡ ቶማስ ሊረዳቸው ያልቻለ ሰዎች ቢኖሩ እስጢፋኖስ ዋነኛው ይሆናል፡፡ አሁንም መነጫነጭ ሲጀምር ቶማስ ማባበሉን ያዘ፡፡ “እስጢፍ ለምን አትረጋጋም? ሁሌ ለምን እንዲህ ትሆናለህ?!” “በዚህች ዓለም ውስጥ ምን መረጋጋት አለ? ይታይህ ቀን ከሌት ማጥናት ነው፤ ለአስራ ስንት ዓመት ፍዳ ማየት፤ መሰቃየት፤ ከዚህ ሁሉ ታድያ ሞቶ መገላገል አይሻልም?!” ጠረጴዛውን በቡጢ ደለቀው፤ እና የሚወደውን የመጽሐፈ መክበብ ጥቅሶች አዥጐደጐዳቸው፤ መጽሐፈ መክበብን በቀን ቢያንስ አንዴ ሳያነብ አይውልም፤ ሙሉ መጽሐፉን በቃሉ ሸምድዷል፡፡ “….ከፀሐይም በታች የተሰራው ሥራ ሁሉ ከብዶኛልና ህይወትን ጠላሁ፤ ሁሉም ከንቱ ንፋስንም እንደመከተል ነው…ከፀሐይ በታች በደከመበት ድካም ሁሉና በልቡ ሃሳብ የሰው ጥቅም ምንድነው? ዘመኑ ሁሉ ሀዘንና ጥረትም ትካዜ ነው፤ ልቡም በሌሊት አይተኛም፤ ይህም ደግሞ ከንቱ ነው…አሁንም ቢሆን ከኛ ይልቅ የሞቱት ከነሱም ደግሞ ገና ያልተፈጠሩት ይሻላሉ…ፈተና፣ እንቅልፍ ማጣት፣ መባዘን፣…ከንቱ ነው፤ ሁሉ ነገር…” ቀባጠረ የራሱንም እያከለ፡፡ በቃ እንዲህ እንዲህ ዓይነት ነገር ነው የሚያስመርረው፤ ሞት የሚያስመኘው፡፡ ቶማስ ብዙም አልገፋም፡፡ የእስጢፋኖስ ጭንቀት አስጨነቀው፡፡ ሊያለቃቅስ ጀመረ፡፡ እስጢፋኖስ ደግሞ ካለ ነገሩ ለሰው ግድ የለውም፡፡ ቶማስ ሰውን መርዳት ሲያቅተው ምን ያህል እንደሚጨነቅ፣ ምን ያህል መንፈሱ እንደሚረበሽ አውቃለሁ፡፡ ደግነቱ እስጢፋኖስ ወዲያውኑ ተነስቶ ተኛ፡፡ እኔም አካሌ ዝሎ ስለነበር ጋደም አልኩ፡፡

እንቅልፍ ሊወስደኝ አካባቢ ቶማስ ነቅነቅ አድርጐ ቀሰቀሰኝና ጠጋ ብሎ በጆሮዬ “እስጢፎን የምረዳበትን ዘዴ ሳስብ ነበር፤ አሁን አገኘሁ፡፡” አለኝ፡፡ አየት አድርጌው ፊቴን አዙሬ ተኛሁ፡፡ ጠጋ ብሎ አቀፈኝ፡፡ ጠዋት አንድ ሰዓት ግድም ዶርማችን ውስጥ ትርምስ ሰምቼ ነቃሁ። ቶማስ አጠገቤ የለም፡፡ አትክልቲና መኩሪያ ዶርማችንን ያምሱታል፡፡ ዘልዬ ተነሳሁ፡፡ ምን እንደሆኑ ብጠይቅ የሚመልስልኝ ጠፋ፡፡ ኋላ መኩሪያ በጣቱ ወደ እስጢፋኖስ አልጋ ጠቆመኝ፡፡ ተንደርድሬ ሄድኩ፡፡ እስጢፋኖስ ዓይኖቹ ተገለባብጠው አልጋው ላይ ተዘርሯል፡፡ “ምን?!” ብዬ ጮህኩ፡፡ ለጥንቃቄው ደንታ አልነበረኝም፡፡ አቅፌ ነቀነቅሁት፡፡ ዝም፡፡ ሰውነቱን ዳበስኩት፤ ይቀዘቅዛል፡፡ ደረቱ ላይ እጄን ጫንኩ፤ ምንም፡፡ ሰውነቴ መንዘፍዘፍ ያዘ፡፡ ቀድሞ የነቃ ሌላውን የመቀስቀስ ልማድ ስለአለ ከእንቅልፉ ሊቀሰቅሱት ሲሉ ነበር እንዲያ ሆኖ ያገኙት፤ ሞቶ። አትክልቲ ፊቱ ገርጥቶ ባለበት ሐውልት መስሎ ተገትሯል፡፡ ከንፈሮቹ ደርቀዋል፡፡ መኩሪያም ምንም አይናገርም፡፡ ጭንቅላቱን በሁለት እጆቹ ይዞ፣ አፉን በሰፊው ከፍቶ ቆሟል፡፡

“ሰዎች እርዳታ እንጥራ እንጂ፡፡ ተንቀሳቀሱ።” እያልኩ በባዶ እግሬ ወጥቼ ሮጥኩ፡፡ ወዴት እንደምሄድ ግን አላውቅም፤ኋላ ነው መንገድ ቀይሬ ወደ ዲኑ ቢሮ ያመራሁት፡፡ እዚያ ስደርስ ቶማስ በር ላይ ቆሞ አገኘሁት፡፡ እርሱም እንደኔው ሁኔታውን ሊነግር እንደመጣ ገባኝ፡፡ “ዲኑ አልገቡም?” አልኩት፡፡ ጥያቄዬን ችላ ብሎ “አየህ ምንተስኖት እስጢፋኖስ በጣም ነበር የሚያሳዝነኝ፤ ልረዳው ባለመቻሌ ዘወትር እንደተጨነቅሁ ነበር፡፡ የተቸገረ ጓደኛን መርዳት አለመቻል በጣም አሳፋሪ ነው፡፡ አስቤ እንደደረስኩበት ደግሞ ከዚህ የተሻለ እስጢፋኖስን የምንረዳበት መንገድ የለም፤ እና…” አላስጨረስኩትም፡፡ እጄ ቡጢ ሆኖ ሲወናጨፍ ይታወቀኛል፡፡ አጓርቶ ወደ ኋላ ተዘረረ፡፡ ደነዘዝኩኝ፡፡ ባለሁበት ቆሜ ቀረሁኝ፡፡ እንደምንም ከወደቀበት ተነሳ፡፡ “አንተምኮ ታሳዝነኝ ነበር፡፡” አለኝ ፈገግ እንደማለት ብሎ፡፡ ሲናገር ጥርሶቹ በምላሱ እየተገፉ ወደቁ፤ ባዶ ድድ፡፡ ጭንቅላቴን ይዤ መጮህ ጀመርኩ፡፡ እንባዬ ጅረት ሆኖ ፈሰሰ፡፡ በዚህ መሃል አእምሮዬ ውስጥ አንድ ነገር ፈነዳ፡፡ “ለእናቱም ያዝንላቸው ነበር ማለት ነው?” ከዚህ በኋላ ማሰብ አልቻልኩም፡፡ ጨለማ ሆነ፡፡ ፀጥታ ሆነ፡፡ (ውድ አንባቢያን- ከዚህ በላይ የቀረበው ታሪክ በድጋሚ የወጣ ነው)

Published in ጥበብ
Saturday, 29 June 2013 11:01

ጽንስ ወደ ድንጋይነት ...

“አንድ ጥያቄ አለኝ..... በሚል ጽሁፋቸውን የጀመሩ አንድ አንባቢ የሚከተለውን ብለዋል። ..... እኔን የሚገርመኝ የተፈጥሮ ጉዳይ ነው። እርግዝና ተፈጠረ...እሰይ...ልጅ ላገኝ ነው...ብሎ ምስጋና ለፈጣሪ ሲያቀርቡ የቆዩ ባልና ሚስት...እርግዝናው በትክክለኛው ቦታ አይደለም ...ይልቁንም በሆድእቃ ውስጥ ነው ሲባሉ ...ምን ይሰማቸው ይሆን? መቼም ሁሉም ነገር እንደምንም የማይቆጠርበት አጋጣሚ ብዙ ነውና...አ.አ.ይ ...ምንም አይደለም...እንኩዋንም እሱዋን ለቀቃት ... ወደሚለው እሳቤ ይገባል። እርግጥ ነው ...ሴትየዋ ብትተርፍ እንደገናም ልጅ መውለድ ትችላለች፡፡ ሁኔታው ግን እጅግ ያሳስባል...” ከአንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ለንባብ በቀረበው ከማህጸን ውጭ እርግዝና በመነሳት ሌሎች ጥያቄዎችም ደርሰውናል፡፡ ሶስት ጥያቄዎችን ያዘለው እና በድህረገጻችን የደረሰን መልእክት እን ዲህ ይላል፡፡ “በቅድሚያ ከማህጸን ውጭ እርግዝናን በተመለከተ ላወጣችሁት ጽሁፍ በጣም አመሰግ ናለሁ፡፡ ችግሩ በእኔም ቤት ተከስቶ ስለነበር በተመስጦ አንብቤዋለሁ፡፡

የእኔ ሚስት የ27/አመት እድሜ ያላት ስትሆን የአንድ ልጅ እናት ናት፡፡ ልጃችን የ3/ አመት እድሜ ሲይዝ ሌላ ልጅ ተረገዘ፡፡ ባላሰብነው መንገድ ሚስ በድንገት ታመመች...ለካስ እርግዝናው ከማህጸን ውጭ ነበር፡፡ ወደህክምናው ስትቀርብ ሐኪሙ የነገረን ጽንሱ ያረፈው በዘር ማስተላለፊያ ቱቦ ውስጥ ስለሆነ ቱቦውም ጭምር ይወገዳል የሚል ነበር። ወደፊት ልጅ ስለመውለድ መቻልዋ ስንጠይ ቀውም መውለድ እንደምትችል ነግሮናል፡፡ ነገር ግን የእኔ ጥያቄ... የዘር ማስተላለፊያ ቱቦን ማስወገድ ሌላ የአካል ጉድለትን አያመጣምን? በአንድ የዘር ማስተላለፊያ ቱቦ ብቻ ልጅ መውለድ ይቻላልን? በስንት አመት ልዩነት ነው ማርገዝ የምትችለው?...የሚል ነው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ለዶ/ር መብራቱ ጀምበር የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በብራስ የእናቶችና ሕጻናት ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር አቅርበን የሰጡን መልስ ከማህጸን ውጪ እርግዝና የተከሰተበት የዘር ማስተላለፊያ ቱቦ መወገዱ ትክክል እንደሆነና በአንድ የዘር ማስተላለፊያ ቱቦ አማካኝነትም ልጅ ማርገዝ እንደሚቻል ነው።

የጊዜውም ጉዳይ እንደፈለጉት እንጂ በዚህ ጊዜ የሚል ገደብ እንደሌለው ነግረውናል፡፡ ነገር ግን ምናልባት አሁንም በቀረው የዘር ማስተላለፊያ ቱቦ ላይ ከማህጸን ውጭ እርግዝና ከተከሰተና እሱም ከወጣ ልጅ ማርገዝ የሚባለው ነገር የሚቋረጥ ይሆናል ብለዋል፡፡ ...በቀጣይ የምናስነብባችሁ የአንዲት ሴትን የቅርብ ቀናት ገጠመኝ ነው፡፡ ሴትየዋ ከ5-6 ወር የሚገመት እርጉዝ ነች፡፡ ሕመም እንደሚሰማት ለሐኪሞች ገልጻ ምርመራ ትጀምራለች። በመጀመሪያው ቀን ምርመራ የልጁዋ የልብ ምት እንደሚሰማ ገልጸውላት በሚቀጥለው ቀን እንድትመለስ ትደረጋለች፡፡ በቀጣዩ ቀን ግን የልጁዋ የልብ ምት አይሰማም ነበር፡፡ ስለዚህ ልጁ በሕይወት ስለሌለ ይወለድ ተብሎ የምጥ መርፌ ተሰጣት፡፡ ቢጠበቅ... ቢጠበቅ ምጥ አልመ ጣም፡፡ ከዚያ በሁዋላ ሴትየዋ ከነበረችበት ሆስፒታል በመውጣት ወደካዲስኮ አጠቃላይ ሆስፒ ታል ትሄዳለች፡፡

ታሪኩዋን በማስረዳትዋም ወደአልትራ ሳውንድ ምርመራ ስትላክ በማህጸንዋ ውስጥ ምንም ነገር የሌለ እና ባዶ መሆኑን ውጤቱ ያሳያል፡፡ በዚህ ጊዜ ጥርጣሬ በማሳደሩ እንደገና ወደ ባለሙያው ከታሪኩዋ ጋር ትላካለች፡፡ በዚህ ጊዜ እርግዝናው በሆድ እቃዋ ውስጥ የሚገኝ መሆኑን ምርመራው ግልጽ አደርጎታል፡፡ በዚህ ጉዳይ ያነጋገርናቸው ሴትየዋን በኦፕ ራሲዮን ያዋለዱዋት ዶ/ር ወንድወሰን በለጠ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር ወንድወሰን እንደሚሉት የሆድ እቃ ውስጥ እርግዝና ከማህጸን ውጭ እርግዝናዎች ውስጥ አንዱ ሲሆን ከብዙ በጥቂቱ የሚገኝ ነው፡፡ በአብዛኛው የሆድ እቃ ውስጥ እርግዝና የእን ግዴ ልጁ የሚገናኘው በሆድ ስር ወይንም በእንግሊዝኛው omentum በሚባለው ክፍል እንዲ ሁም በትንሹ ወይንም በትልቁ የአንጀት ክፍል ሊሆን ይችላል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ማህጸንን የሚመግቡ ትላልቅ የደም ስሮች ላይ ወይንም ከማህጸን የሁዋለኛው ክፍል እንዲሁም ጉበት ፣ ቆሽት የሚባሉ የሰውነት የውስጥ አካላት ላይ ሊሆን ይችላል፡፡ የእንግዴ ልጅ የሚያገኘው የደም ስርጭት ጥሩ በሆነ ቁጥር እስከ ዘጠኝ ወርም ድረስ የማደግ እድል የሚኖረው ሲሆን የደም ዝውውሩ ባነሰ ቁጥር ግን ህይወቱን የማጣት እድሉ እየሰፋ ይመጣል፡፡ ዶ/ር ወንድወሰን በመቀጠል እንደተናገሩትም ሕክምናዋን በሌላ ሆስታፒል ጀምራ በመሀከል ወደካዲስኮ የመጣችው ሴት በእድሜዋ ከሰላሳ አመት በላይ ስትሆን እሱዋ እንደ ምትናገረው ከዚህ በፊት ዘጠኝ ወር ደርሶ ከምጥ ጋር በተያያዘ ችግር የሞተ ልጅ ወልዳለች፡፡ በመቀጠልም በነበራት የእርግዝና ታሪክ ወደ ሁለት ጊዜ አስወርዶአታል፡፡ እንደ አለመታደል ሆኖ አራተኛው እርግዝና ደግሞ ከማህጸን ውጭ ሆኖአል፡፡ ሴትየዋ ቀደም ሲል በታከመችበት ሆስፒታል እርግዝናው እንዲቋረጥ ከተነገራት በሁዋላ የምጥ መርፌ ተሰጥቶአት ልጁ ሊወለድ አለመቻሉ አንዱ ለጥርጣሬያችን ምክንያት ነበር፡፡

ምክንያቱም ልጁ በህይወት እስከሌለ ድረስ የምጥ መርፌው እንዲወለድ ሊያደርገው ይገባ ነበርና ነው፡፡ ነገር ግን ልጁ በማህጸን ውስጥ ስላልነበረ የማማጫ መርፌው በምንም ምክንያት ልጁ እንዲወለድ ማድረግ አልቻለም፡፡ በአል ትራሳውንድ ምርመራው ሲደረግ የታየው በሆድእቃዋ ውስጥ ፈሳሽ መኖሩ ነው፡፡ ያ ፈሳሽ ደግሞ እየደማች እንደሆነ ከግምት የሚገባ ነበር፡፡ ስለዚህ ኦፕራሲዮን እንድትደረግ ከባለጉዳዮቹ ጋር በተደረገ ስምምነት የሆድ እቃዋ ሲከፈት ልጁን ማግኘት አስቸጋሪ አልነበረም። ሕይወት ባይኖረውም ከነሽፋኑ እንዲወጣ ተደርጎአል፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝና በሆድ እቃ ውስጥ ሲፈጠር የእንግዴ ልጁ የሚያርፍበት ውስን ቦታ እንደሌለው ከላይ ተገልጾአል፡፡ ስለዚህም የዚህችን ሴት ልጅ ካወጡ በሁዋላ ቀጣዩ ስራ የእ ንግዴ ልጁ የት እንዳለ መፈለግ ነበር፡፡ በእርግጥ እርግዝናው በሆድ እቃ ውስጥ እስከሆነ ድረስ የሚመረጠው የእንግዴ ልጁን በዚያው መተውና ጊዜውን ጠብቆ ቀስ በቀስ እንዲወገድ ማድረግ ቢሆንም አንዳንድ ጊዜ ግን የተፈጠረበት ቦታ አመቺነትም የሚወሰደውን እርምጃ ይወስነዋል፡፡

የዚህች ሴት ሆድ እቃ ውስጥ የእንግዴ ልጁ ያረፈው ከማህጸን የውጭ ግድግዳ እና ከሁዋላው እንዲሁም ትልቁን ደንዳኔ ጭምር ተጣብቆ ነው። እርግዝናው እድሜው ከአምስት ወር እስከ ስድስት ወር ድረስ ስለሆነው የእንግዴ ልጁ ሰፋ ያለ ቦታ ይዞ ነው የተገኘው፡፡ የእንግዴ ልጁን ማውጣት ግድ ስለነበር በከፍተኛ ጥንቃቄ ለማውጣት ተሞክሮአል፡፡ በእርግጥም ከፍተኛ መድማት ስለነበር ያንን ለማቆም ተገቢው ጥረት ተደርጎ ሴትየዋ በሰላም ወደቤትዋ ገብታለች፡፡ በሆድ እቃ ውስጥ በሚኖረው እርግዝና የእንግዴ ልጁን ማውጣት የሚያስቸግረው በተለይም በትላልቅ የደም ቧንቧዎች ላይ ተጣብቆ የሚገኝ ከሆነ እና ሊያስከትል የሚችለውን የደም መፍሰስ ማስቆም ስለማይቻል ነው፡፡ ስለዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ በሚገጥምበት ጊዜ መድሀኒት እየወሰደች የእንግዴ ልጁ ቀስ በቀስ እየሞተ በራሱ ጊዜ እንዲወጣ መጠበቅ ግድ ይሆናል፡፡ ግን በዚህም ወቅት የሚፈጠር ችግር የለም ማለት አይቻልም፡፡

አንዳንድ ጊዜ የእንግዴ ልጁ በሰውነት ውስጥ በመቅረቱ እዛው በስብሶ መግል የማጠራቀም ወይንም ፌስቱላ የሚባለውን ሕመም ሊፈጥር የሚችልበት አጋጣሚ ይኖራል፡፡ በተለይም አንጀት ላይ ከሆነ አንጀት ተበስቶ ሰገራንም የመቆጣጠር ችግር ሊያስከትል ይችላል፡፡ ከማህጸን ውጭ በሆድ እቃ ውስጥ የተፈጠረው እርግዝና መቀጠል ባለመቻሉ ሕይወቱ ሲያልፍ በሆድ እቃ ውስጥ በሌሎች አካላት ላይ የሚያስከትለው ችግር የለም ወይ ለሚለው ጥያቄ ዶ/ር የወንድወሰን በለጠ ሲመልሱ፡- .....የሆድ ውስጥ እርግዝና ካለ የሚመከረው በፍጥነት ማከም ወይንም በኦፕራሲዮን ማውጣት ነው፡፡ ምክንያቱም ጊዜው ደርሶ ሊወለድ የሚችለው ከብዙ በጥቂቱ ስለሆነና የመወ ለጃ ጊዜው እስኪደርስ ሳይጠብቅ ለህልፈት የሚዳረገው ግን ብዙ ስለሆነ አስቀድሞውኑ መፍ ትሔ መስጠት ሰለሚገባ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከማህጸን ውጭ የሚፈጠሩ እርግዝናዎች የአፈጣጠር ወይንም የክሮሞዞም ችግር ሊኖራቸው እንደሚችል ብዙ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ሌላው ችግር በማህጸን ውስጥ እንደተረገዘ ልጅ የሽርት ውሀ በበቂ ስለማይኖረው የሴትየዋ አንጀት ወይንም ሌሎች የሰውነት ክፍሎች የልጁን ቅርጽ ይቀይሩታል፡፡ ስለዚህ ልጁ የእግሩ ...የእጁ...ወዘተ የአስተዳደግ ቅርጽ ትክክል ላይሆን ይችላል፡፡ ጭንቅላቱ የተጣመመ ሊሆን ይችላል፡፡ ከልጁም ባሻገር እናትየውም በተለይም አንጀትዋ ላይ ከሆነ የአንጀት መዘጋት ...በዚያም ምክንያት የሆድ ማበጥ ሊያስከትልባት ይችላል።

ከዚህም በላይ መጥፎ የሚሆነው የእንግዴ ልጁ ሆዳቸው ውስጥ ተላቆ ደም በመድማት እናቶች ሾክ ውስጥ የሚገቡ መሆኑ ነው፡፡ ከማህጸን ውጭ እርግዝና በተለይም በሆድ እቃ ውስጥ ከሆነ ይደግ ተብሎ ቢተው እንኩዋን የሚያስከትለው ችግር አስከፊ ስለሆነ በጊዜ መታከም ይገባዋል ብለዋል ዶ/ር ወንድወሰን በለጠ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት፡፡ ማንኛዋም እናት የወር አበባዋ መቅረቱን ካረጋገጠችበት እለት ጀምሮ ወደሕክምና በመቅረብ የጽንሱንም ሆነ የእራስዋን ጤንነት መከታተል ይገባታል፡፡ ለዚህ ታሪክ መነሻ የሆነችው እናት ከጸነሰች ጀምሮ ምንም ክትትል ባለማድረጉዋ በስተመጨረሻ ጽንሱ ያለበትን ሁኔታ ለማወቅ ትንሽ ግራ አጋቶ ነበር፡፡ ስለዚህ ጽንሱ ከማደጉ በፊት የእናትየውን ጤንነት በተሙዋላ መልኩ እንዲቀጥል ለማድረግ ይቻላል፡፡ በጊዜው አስፈላጊው ሕክምና ሳይሰጥ በሆድ እቃ ውስጥ እያደገ ከሄደ ግን ... ሆድ ውስጥ መግል የመጠራቀም፣ አንጀት የመታጠፍ፣ አንጀት የመበሳት፣ የመድማት ...ወዘተ ችግርን ሊያስትል ይችላል፡፡ ከማህጸን ውጭ የሆድ እቃ ውስጥ እርግዝና ያለበት ቦታ በቂ ስፋት ያለው ከሆነ ጽንሱ ሕይወቱን ቢያጣም እንኩዋን ምንም ችግር ሳያመጣ ወይንም ሕመም ሳይሰማ ዝም ብሎ ሊቀመጥ ይችላል፡፡ ከአስር እና ከሀያ አመት በሁዋላ ሴቶች በሆድ እብጠት ችግር ምክንያት ለሕክምና ይመጣሉ፡፡ በምርመራ የሚገኘው ውጤት ጽንሱ ወደ ድንጋይነት ተለውጦ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ካልሽየም ከሰውነት ወደ እርግዝናው በመሄድ ስለሚጠራቀም ነው፡፡ ስለዚህም ሴቶች ከማርገዛቸው በፊት ጀምሮ የወር አበባቸው በቀረ ማግስት የእርግዝና ክትትል ሊያደርጉ ይገባል የሚል ምክር ለግሰዋል ዶ/ር የወንድወሰን በለጠ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻ ሊስት፡፡

Published in ላንተና ላንቺ

“ተቃዋሚዎች ከከባድ ቁስል የባሰ የሚያሳምሙ እከኮች ናቸው”

     የፕሬዚዳንት ሴኩቱሬን አስደናቂ የማደራጀት ችሎታ አሳንሼ አቀርባለሁ አሊያም እተቻለሁ ብሎ የሚነሳ ማንም ሰው እንኳን በምድረ ጊኒ ይቅርና በፈረንሳይ ውስጥም ቢሆን እህ ብሎ የሚያዳምጠው ሰው ማግኘት መቻሉ በጣም ያጠራጥራል፡፡ በዚህ ረገድ ሰውየው ያላቸው የማደራጀት ችሎታ እንዴት ያለ እንደሆነ በቀላሉ ለመረዳት ካስፈለገ የጊኒን ዲሞክራቲክ ፓርቲ ከተራና እዚህ ግባ ከማይባል የሰራተኛ ማህበርነት አንስተው እንዴት ወዳለ ጠንካራና መሠረተ ሰፊ ፓርቲነት እንደቀየሩት መመልከት ብቻ ከበቂ በላይ ነው፡፡ በ1957 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ ከምክር ቤቱ ስልሳ መቀመጫዎች ሀምሳ ስድስቱን ጠራርጐ የወሰደበት ዋነኛው ምስጢር፣ ያኔ የሰላሳ አምስት አመት ጐልማሳ የነበሩት አህመድ ሴኩቱሬ፣ ይህ ቀረሽ የማይባል የማደራጀትና የማንቀሳቀስ ከፍተኛ ችሎታ ነበር፡፡ ይህንን ከፍተኛ የማደራጀት ችሎታቸውን በመጠቀምም የፓርቲውን መዋቅር ከመደበኛው የመንግስት መዋቅር እኩል ከከፍተኛው አካል እስከ ዝቅተኛው የቀበሌ አካል ድረስ ወርዶ እንዲዘረጋ አደረጉ፡፡

ከመደበኛው የመንግስት የአስተዳደር አካል በበለጠ ስልጣንና ሀላፊነት ለፓርቲው በመስጠት፣ የህዝቡ የእለት ተዕለት እንቅስቃሴ ከፓርቲው ጋር በቀጥታ እንዲቆራኝ አደረጉ፡፡ መደበኛ መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማግኘት የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ አባል መሆንን በቅድሚያ ግዴታነት አስቀመጡ፡፡ ከአንድ የካቢኔ ምኒስትር ይልቅ ለምኒስትር መስሪያ ቤቱ የፓርቲው መሠረታዊ ድርጅት ፀሀፊ የበለጠ አይነት ስልጣን አጐናፀፉት፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ፓርቲያቸውን በዚህ አይነት ካዋቀሩ በኋላ ግንባር ቀደም ካድሬዎቻቸውን ሰበሰቡና እንዲህ በማለት የስራ መመሪያ ሰጧቸው፡- “ጓዶች! በጫካው ውስጥ ዝሆኖች እንደሌሉ ከታወቀ ጐሾች ዝሆን ነን ማለታቸው እንደማይቀር ምንም ጥርጥር የለውም፡፡

ስለዚህ ለፓርቲያችን ተቃዋሚዎች ወይም የፓርቲያችን አባላት ላልሆኑት ሁሉ ዝሆኖች እናንተ መሆናችሁን በሚገባና በግልጽ ማሳየት አለባችሁ፡፡ ምርጫ ያለው ሰው ምንጊዜም ቢሆን ችግር ሊፈጥር እንደሚችል መዘንጋት የለባችሁም፡፡ እናም ሰዎች ከፓርቲያችን ውጪ ሌላ ምርጫ እንዳይኖራቸው ማድረግ አለባችሁ” ቤተመንግስታቸው የሚገኝበት የሰሜን ምዕራብ ኮናክሪ አንዱ የቀበሌ መስተዳድር ለፓርቲው አባላት ባዘጋጀው የንቃተ ህሊና ማዳበሪያ ስብሰባ ላይ ድንገት ከች ያሉት ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ፤ ስለ ጊኒ አብዮትና “የምዕራቡ የአድህሮት ሀይላት የጊኒኒ አብዮት ለመቀልበስ” ስለሚያደርጉት ያላሰለሰ ጥረት ረጅም ንግግርና ሰፊ ገለጻ ካደረጉ በኋላ፣ በመጨረሻ ለተሰበሰበው ህዝብ አንድ ጥያቄ አቀረቡ፡፡

“ጓዶች! እስስት ታውቃላችሁ?” ህዝቡ በአንድ ድምጽ ጮክ ብሎ “አዎ!” በማለት መለሰላቸው፡፡ “እስስት የሚታወቅበት ተፈጥሮው ምን እንደሆነስ ታውቃላችሁ?” ህዝቡ እንደ መጀመሪያው ጥያቄ በአንድ ላይ ሳይሆን እንዲሁ እንደ መሰለው ሲመልስ፣ የቀበሌው ግንባር ቀደም ወይም ጠርናፊ የሆነው ካድሬ ከተቀመጠበት ብድግ ብሎ ሁለት እጆቹን በማንሳት፣ ህዝቡን ፀጥ ካሰኘ በኋላ “ቆራጡ መሪያችን ጓድ ሊቀመንበር! እስስት ከሌላው እንስሳት ተለይቶ የሚታወቅበት ልዩ ተፈጥሮው ከአካባቢው ጋር ለመመሳሰል ቀለሙን መለዋወጥ መቻሉ ነው! እናሸንፋለን!” በማለት ህዝቡን ወክሎ መልስ ሰጠ፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ መልሱ እንዳረካቸው ለመግለጽ ችምችም ብለው የተተከሉትንና ልዩ ንጣት ያላቸውን የሚያምሩ ጥርሶቻቸው ከዳር እስከ ዳር እስኪታዩ ድረስ ፈገግ ብለው አንድ ሶስቴ ያህል ካጨበጨቡ በኋላ “ይሄውላችሁ ጓዶች!” የጠንካራውና የመሪ ፓርቲያችን አባላት እንደመሆናችሁ መጠን ፓርቲያችንንና አብዮታችንን ከተቃዋሚዎችና ከአድሀሪያን ሀይሎች ነቅቶ መጠበቅና መከላከል ሁልጊዜም ይጠበቅባችኋል።

ይህን አብዮታዊ ሀላፊነት በድል ለመወጣት ደግሞ እስስት መሆን የግድ ይጠበቅባችኋል። በምትኖሩበት ቦታ ሁሉ እንደ እስስት እየተንቀሳቀሳችሁ፣ የፓርቲያችንንና የአብዮታችንን ጠላቶች እያጋለጣችሁ መመንጠር አለባችሁ!” አሉዋቸው፡፡ የተሰበሰበው ህዝብም የግራ እጁን ወደ ላይ በማውጣት “የፓርቲያችንና የአብዮታችን ጠላቶች ይወድማሉ! እናሽንፋለን!” በማለት መቼም ቢሆን ቸል የማይባለውን የፕሬዚዳንቱን ትዕዛዝ መቀበሉን አረጋገጠ፡፡ የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ ባለስልጣኖችና መሪ ግንባር ቀደም ካድሬዎች፣ በየካቲት ወር 1960 ዓ.ም የተላለፈውን የፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ቀጭን ትዕዛዝ በተራቸው እስከ ዝቅተኛው ቀበሌ የሚገኙ ጊኒያውያን በስራ ላይ እንዲያውሉት የመንግስትና የፓርቲውን መዋቅር በመጠቀም የቅርብ ቁጥጥር ማድረግ ጀመሩ፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በሊቀመንበርነት የሚመሩትን የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲን የህዝቡ ፓርቲ፣ ህዝቡንም የፓርቲው ለማድረግ ያደረጉት እንቅስቃሴ፣ በአንድ እጅ ጣቶች በሚቆጠሩ ወራት ብቻ ያስገኘላቸው ውጤት በእጅጉ አርክቷቸዋል፡፡

መደበኛ የሆኑ መንግስታዊ አገልግሎቶችን ይቅርና ከሰፈር ቦኖ ውሀ ለመቅዳት እንኳ ያለ ፓርቲ አባልነት የሚቻል ባለመሆኑ የፓርቲውን የአባልነት መታወቂያ ካርድ ለማግኘት ጊኒያውያን ሙሉ የወር ገቢያቸውን በየደረጃው ላሉ የፓርቲ ፀሀፊዎችና መሪ ካድሬዎች ጉቦ ከመስጠት ጀምሮ የማያደርጉት ጥረት አልነበረም፡፡ “ልክ እንደ እስስት መንቀሳቀስ አለባችሁ” የተባለውን የፕሬዚዳንቱን ቀጭን ትዕዛዝ በተግባር ለመፈፀምም የፓርቲው አባላት የስራ ባልደረቦቻቸውን፣ የትምህርት ቤት ጓደኞቻቸውን፣ ጐረቤቶቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ሳይቀር ጠቅላላ የየእለት እንቅስቃሴአቸውን እየተከታተሉ ለጠርናፊ ካድሬዎቻቸው የየእለቱን ሪፖርት ማድረግ ጀመሩ፡፡ ቀድሞውኑም አነስተኛና የተበታተኑ የነበሩት የጊኒ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ በጊኒ የፖለቲካ ምህዳር ውስጥ ይበልጡኑ ለእግር መትከያ የሚሆን ቦታ እንኳ ማግኘት አቃታቸው፡፡ ይህንን ብሶታቸውን በማሰማትም ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ የማሻሻያ እርምጃ እንዲወስዱ በይፋ ጠየቁ፡፡ ፕሬዚዳንቱ የሰጡት ምላሽም ቅልብጭ ያለና ፈጣን ነበር፡፡ “የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ በ1957 ብሔራዊ ምርጫ ማግስት ያቀረበላችሁን ታላቅ አብዮታዊ ግብዣ ንቃችሁ ትታችሁታል፡፡ ያ ትልቅ እድል መቸም እንደማይመለስ ሆኖ አልፏል፡፡

ያኔም ሆነ ዛሬ እናንተ የመረጣችሁትና የፈለጋችሁት የፀረ-አብዮተኞች በተለይ ደግሞ የምዕራብ አድህሮት ሀይላት አንጋች መሆንን ነው፡፡ ዛሬ እኛ ፍየሎች እናንተ ደግሞ ነብሮች ናችሁ፡፡ ታዲያ ፍየሎች ከነብር መንጋ ጋር ሲኖሩ ያያችሁት ከመቼ ወዲህ ነው?” በማለት ነበር ፕሬዚዳንቱ ለተቃዋሚዎች የመለሱላቸው፡፡ በ1957 ዓ.ም በተካሄደው ብሔራዊ ምርጫ፣ የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ ከስልሳ የምክር ቤት መቀመጫዎች ሀምሳ ሰባቱን ማሸነፉ በጊኒ የምርጫ ቦርድ በይፋ እንደተረጋገጠ፣ የፓርቲው ሊቀመንበር ሴኩቱሬ ሶስት መቀመጫዎችን ብቻ ላሸነፉት የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ፓርቲዎቻቸውን በመተው የእሳቸው ፓርቲ አባላት እንዲሆኑ ጠይቀዋቸውና ይፋ ግብዣ አቅርበውላቸው ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ መቸም የማይመለሰው ትልቅ እድል ያሉትም ይህን ግብዣቸውን ነበር፡፡ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ግን አንዳንዶቹ ነፃነታቸውን ጠብቀው በተቃዋሚነት ለመቀጠል በመምረጥ፣ ሌሎቹ ደግሞ ወግና ስርአት ባለው ሁኔታ ቦታችንና ሚናችን ታውቆ ባይሆን ውህደት እንፈጽም እንጂ እንዲያው ዝም ብለን ፓርቲዎቻችንን አፈራርሰን እንዴት የዲሞክራቲክ ፓርቲው ተራ አባላት እንሆናለን በማለት የፕሬዚዳንቱን ግብዣ ውድቅ አደረጉት፡፡

ከዚህ በሁዋላ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ጥቂት ጊዜ ያጠፉበት አብይ ጉዳይ ተክለ-ሰብዕናቸውን መገንባት ላይ ነበር፡፡ ይህንን እቅዳቸውን ተግባራዊ በማድረጉ ረገድ እንደ ፓርቲያቸው መዋቅርና ግንባር ቀደም ካድሬዎቻቸው በሚገባ ያገለገላቸው ፈጽሞ አልነበረም፡፡ “ቆራጡ አብዮታዊ መሪ! ታላቁ የአፍሪካ ልጅ! የኢምፔሪያሊዝ ውጋት! የቅኝ አገዛዝ መጋኛ! የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ መቅሰፍት! የአብዮታዊ ሳይንሶች ዶክተር!” የሚሉትን ስያሜዎች ተጨንቆና ተጠቦ በማውጣት ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬን የሰየማቸው ፓርቲያቸው ነበር፡፡ ስያሜዎቻቸውን በህዝቡ ዘንድ ያሰረፁትና ሌሎች ተጓዳኝ የተክለ-ሰብዕና ግንባታ ስራዎችን በከፍተኛ ብቃትና አብዮታዊ መንፈስ ቀን ከሌት ላይ ታች ብለው ያስፈጸሙት ደግሞ በየደረጃው ያሉ መሪ ካድሬዎች ነበሩ፡፡ እናም ታዲያ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በየትኛውም ቦታና አጋጣሚ ሁሉ በእርሻም ሆነ በምህንድስና፣ በፍልስፍናም ሆነ በእግር ኳስ በማንኛውም አይነት የእውቀት ዘርፍ አቻ የለሽና ታላቅ ምሁር እንደሆነ ተደርገው ይቀርቡ ነበር፡፡

አባባ ጃንሆይ በተለያየ ጊዜ ያደረጓቸውን ንግግሮች አካቶ የያዘ “ፍሬ ከናፍር ዘ ቀዳማዊ ሀይለ ስላሴ፣ ስዩመ እግዚአብሔር ንጉሰ ነገስት ዘኢትዮጵያ” የሚል ባለ ብዙ ቅፅ መጽሀፍ አሳትመዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬም በተለያየ ጊዜ ያደረጉትን ንግግርና የጊኒን አብዮትና የአፍሪካን እድገት በማስመልከት የሰጧቸውን ገለፃዎች ያካተተ ባለ ሀያ ሶስት ቅፅ መጽሀፍ አሳትመው በጥሞና እንዲያነቡት ከትዕዛዝ ጋር ለህዝባቸው እንዲሠራጭ አድርገዋል፡፡ እነዚህን የፕሬዚዳንቱን መጽሀፍት በማንበብ በኩል ከተራው ህዝብ ይልቅ ተማሪዎች ያለባቸው ሀላፊነት በእጅጉ የተለየ ነበር፡፡ በተለይ ከአንደኛ ደረጃ በላይ ያሉ ተማሪዎች ከክፍል ወደ ክፍል ለመዘዋወር የሚሠጣቸውን ፈተና ማለፍና ከሀያ ሶስቱ ቅጾች አንዱን ወይም ከአንድ በላይ መጽሀፍት በቃል ሸምድዶ መያዝ ብቻ አይበቃም፡፡ ፕሬዚዳንቱ የጊኒን የፀረ-ቅኝ አገዛዛ ትግልና የምዕራባውያን የአድህሮት ሀይሎችን ሴራ “ያጋለጡበትን” የተለያዩ እጅግ በጣም ረጃጅም አብዮታዊ ግጥሞችን ሸምድዶ በቃል ማነብነብ መቻልም የግድ ነበር፡፡

ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ይህንን የተክለ-ሰብዕና ግንባታ እንደማይፈልጉ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ “ታሪክ ሰሪው ሰፊው ህዝብ እንጂ እኔማ አንድ ተራ ግለሰብ እኮ ነኝ!” ይሉ ነበር፡፡ ይህ አባባላቸው ግን ፈጽሞ ውሸት ነበር፡፡ እንዴት ቢባል ጉዳዩን ከጀርባ ሆነው የሚያስተባብሩትና የሚመሩት እርሳቸው ስለነበሩ ነው፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ይህ የተክለ ሰብዕና ግንባታ እንቅስቃሴ ለፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ተራ ዝና ለመገንባት የሚያደርጉት እንቅስቃሴ አልነበረም። በርካቶች የሰላ ትችት ያቀርቡባቸው እንደነበረው በአፍሪካ የፀረ ቅኝ አገዛዝ ትግልና በጊኒ ድህረ-ነፃነት ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና፣ ኢኮኖሚያዊ ህይወት ውስጥ አብዛኛውን የታሪክ ምዕራፍ በዋናነት ሞልቶ ለመያዝ ከነበራቸው ይህ ነው የማይባል ፍላጐት በመነሳት ብቻ የተደረገም አልነበረም፡፡ ለእሳቸው ጉዳዩ ከዚህ ያለፈ ፋይዳ ነበረው፡፡ ራሳቸውን የፓርቲው እስትንፋስ ለማድረግ የነደፉትን ዋናውን እቅዳቸውን ለማሳካት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ፈጣንና ቀላል ለማድረግ የመረጡት ስትራተጂ ተክለ ሰብዕናቸውን መገንባት ነበር፡፡

እንዳሰቡትም ከፍ ያለ ውጤት አስገኝቶላቸዋል፡፡ “የሁሉም አብዮታዊ ሳይንሶች ዶክተር” የተባሉት ሴኩቱሬ፤ በፓርቲው የፖሊት ቢሮም ሆነ የማዕከላዊ ኮሚቴ ውስጥ እንኳን ንግግራቸው ይቅርና የአይን ጥቅሻቸውና የእጅ እንቅስቃሴአቸው ሳይቀር እንደዋና መመሪያ ተደርጐ ተቆጠረ፡፡ እሳቸው ያቀረቡትን ማናቸውም አይነት ንግግር ገለፃ ወይም አስተያየት ደግፎ ከማጨበጨብ በቀር የድጋፉም ቢሆን ተጨማሪ አስተያየት መስጠት እንደ ከባድ ወንጀል መታየት ቀጠለ፡፡ በፓርቲውም ሆነ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ለቢሮ ጽዳት የሚያገለግል መጥረጊያ እንደመግዛት ያለ እጅግ ተራ ውሳኔም ቢሆን ያለ እሳቸው እውቅናና ፈቃድ መወሰን እንደ ፀረ አብዮተኛ አስቆጥሮ በቀጥታ ወህኒ ማስወርወር ጀመረ፡፡ በፓርቲውም ሆነ በመንግስት መዋቅር ውስጥ የፈለገው አይነት ስልጣን ምንጭ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬና እሳቸው ብቻ ሆኑ፡፡ የእሳቸውን ሞገስ ያገኙት ከተራው እስከ ከፍተኛው የምኒስትርነትና የፓርቲ ፀሐፊነት ስልጣን ሲሾሙ፣ ያላገኙት ደግሞ ከስልጣናቸው ይባረራሉ፡፡

በማናቸውም አይነት የህግ ጉዳይ ውስጥ ጣልቃ በመግባት በህዝቡ ስምና ለህዝቡ ጥቅም በሚል የራሳቸውን ውሳኔ ይሰጣሉ፡፡ ለምን ብሎ ደፍሮ የሚጠይቃቸው የለም፡፡ እሳቸው በሁሉም የእውቀት ዘርፍ ከሁሉም የላቁ ምሁር ናቸዋ! በዚህ አይነት ጊኒ ከፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ ነፃ በወጣች በሁለት አመት ጊዜ ውስጥ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ የፓርቲያቸውና የመንግስታቸው እስትንፋስ ብቻ ሳይሆን የጊኒና የህዝቦቿን የእለት ተእለት ህይወት የሚወስኑ አዛዥና ናዛዥ የሌላቸው ብቸኛው ሰው ሆኑ፡፡ ጊኒም፤ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ብቸኛው ተዋናይ ሌሎች ደግሞ ለእርሳቸው ክብር አጨብጫቢ፣ በእሳቸው ሙዚቃ ብቻ ጨፋሪ የሆኑበት የአንድ ሰው ትርኢት መድረክ ሆና ራሷን አገኘችው፡፡ ተፈጥሮ ሙሉ ልግስናዋን ለጊኒ አሳይታለች። ክረምት ከበጋ የሚፈሱ ወንዞች በመስኖ ሊለማ የሚችል ሰፊ የእርሻ መሬት፣ በአለምአቀፍ ደረጃ የሚጠቀስ እጅግ ከፍተኛ የብረትና የቦክሳይት ማዕድናት ክምችት አድላታለች፡፡ በዚህ የተነሳ ጊኒ በቀላሉ ለማደግ ከፍተኛ እድል ነበራት፡፡ የፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ግን ያንን ከፍተኛ እድል “ላም አለኝ በሰማይ” ሆኖ እንዲቀር አደረገባት፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ጊኒን ከፈረንሳይ ተጽእኖ ለማላቀቅና ስራ ፈጣሪ የሆነ ልዩ ጉልሃን (elit) ቡድን እንዳይፈጠር ለመከላከል በሚል ሁሉንም የኢኮኖሚ ሴክተሮች በመንግስት ቁጥጥር ስር እንዲሆን አደረጉ፡፡

ግለሰብ ነጋዴዎችን ከሃዲ ፀረ አብዮተኛና የኢምፔሪያሊዝም ቡችሎች ብለው በአደባባይ አወገዟቸው፡፡ ይባስ ብለውም የመንግስት ፋብሪካዎችንና እርሻዎችን በፓርቲው ካድሬዎች እንዲመሩ አደረጉ፡፡ እነሱም ከፓርቲ ካድሬነት ውጪ ምንም አይነት የስራ አመራር ችሎታና እውቀት ስላልነበራቸው ውጤቱ አደገኛ ውድቀት ብቻ ሆነ፡፡ ፕሬዚዳንት ሲኩቱሬ የኢኮኖሚ ፖሊሲያቸውን ውድቀት በ”ምዕራብ አድህሮት ሃይሎች ታላቅ ሴራ” የተከሰተ እንደሆነ በድርቅና አመካኙ፡፡ ይግረማችሁ በሚል አይነትም በ1977 ዓ.ም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ጊኒያውያን የእለት ተዕለት ህይወት የተመሰረተበትን የአካባቢና የጉልት ገበያዎች እንዲነሱ፣ ገበሬዎችም ምርቶቻቸውን ለመንግስት የገበያ ድርጅት (እኛ እንደነበረን እርሻ ሰብል ገበያ ድርጅት አይነት) ብቻ እንዲሸጡ የሚያስገድድ መመሪያ አወጡ፡፡ ይህ መመሪያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ጊኒያውያንን ህይወት ከድጡ ወደ ማጡ ከተተው፡፡ በዚህ መመሪያ የተነሳ የቤታቸው ሌማት ክው ብሎ የደረቀባቸው የሰፈር ጉልት ሻጭ ሴቶች ለተቃውሞ አደባባይ በመውጣት ወደ ቤተመንግስት አመሩ። እዚያ ሲደርሱ የጠበቃቸው ግን ችግራቸውን የሚያዳምጥ ፕሬዚዳንት ሳይሆን የቤተመንግስቱ ጠባቂ የክብር ዘበኛ ጦር ጥይት ነበር፡፡

የፓርቲው ልሳን የሆነው “ሆሮያ” የተሰኘው ጋዜጣ፣ በርካታ ሰልፈኞች የተገደሉበትን ይህን የተቃውሞ እንቅስቃሴ “በአብዮትና በፀረ አብዮት መካከል የሚደረግ ትግል ነው” በማለት አስረዳ፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬም በበኩላቸው፤ አድማውን “የአምስተኛ ረድፈኞች ሴራ ነው” በማለት ካወገዙ በኋላ፣ ህዝቡ ተራራውን ሳይወጡ የተንጣለለውን የእርሻ መስክ ማየት እንደማይቻል መገንዘብ እንዳለበት ማሳሰቢያ ሰጡ፡፡ የሆነ ሆኖ ከፍተኛ አዘቅት ውስጥ በገባው ኢኮኖሚ የተነሳ ጊኒን ሙሉ በሙሉ ከመንኮታኮት በጊዜው የታደጋት በውጭ ኩባንያዎች እየተመራ እንዲቆይ ልዩ ፍቃድ በተቸረው የቦክሳይትና የብረት ማዕድን ሽያጭ ባገኘችው ገቢ ብቻ ነበር። ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በሶሻሊስት ርዕዮተአለም እየተመሩ፣ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል በጊኒ እንዲኖር ጥሬአለሁ በማለት አዘውትረው ይናገራሉ፡፡ እሳቸው ይህን ቢሉም በተግባር ያደረጉት ግን ድህነትን ለመላው ጊኒያውያን ማካፈል ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በፖለቲካውም መስክ ያሳዩት አመራር ከኢኮኖሚ አመራራቸው በእጅጉ የከፋና ለምን “ቆራጡ አብዮታዊ መሪያችን” እንደተባሉ በትክክል የሚያሳይ ነበር፡፡

ከ1957 እስከ 1959 ዓ.ም ድረስ በነበሩት ጊዜያት ተቃዋሚዎችን በተመለከተ ፕሬዚዳንቱ የነበራቸው አቋም ፓርቲዎቻቸውን እየተው የሳቸውን ፓርቲ በተራ አባልነት እንዲቀላቀሉ መጋበዝና መጐትጐት ነበር፡፡ በ1960 ዓ.ም መግቢያ ላይ ግን “እንግዲህ ሁለታችንም (ራሳቸውንና ተቃዋሚዎችን) የቤቱ አባወራ ከሆንን ግመሎችን ታዲያ ማን ሊመራቸው ነው?” ማለት አመጡ፡፡ ነገርየው በአንድ ቤት ሁለት አባወራ አይኖርም ለማለት ብቻ ሳይሆን በአንድ ሀገርም ሁለት መሪ ሊኖር አይችልም ብሎ ለመናገር ነው፡፡ ቀጠሉና ደግሞ “ከከባድ ቁስል ይልቅ ለመቋቋም የሚከብድ ሀይለኛ ህመም የሚፈጥረው እከክ ነው!” ማለት ጀመሩ፡፡ የፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ አባባል ሰምና ወርቅ ያለው ቅኔ አልነበረም፡፡ ተቃዋሚዎች ከከባድ ቁስል የባሰ የሚያሳምሙ እከኮች ናቸው ማለታቸው ነበር፡፡ በሌላም በኩል ፕሬዚዳንቱ ለተቃዋሚዎች ምን አይነት ድግስ እየደገሱላቸው እንደሆነ በግልጽ የሚያመላክት ነበር፡፡

እናም እከክ ያሏቸውን ተቃዋሚዎችንና ሌሎች “ፀረ - አብዮተኞችን” ከጊኒ የፖለቲካ መድረክ ጨርሶ ለማስወገድ ከሰው አፍ የማያስገባ ሰበብ ለመፍጠር እያሰላሰሉ በነበረበት ወቅት ድንገት አንድ “መልካም” አጋጣሚ ደጃቸው ድረስ ከች አለላቸው። በ1960 ዓ.ም አጋማሽ ላይ በምዕራብ የአድህሮት ሃይሎችና የነሱ ቡችላ በሆኑ የጊኒ አብዮት ጠላቶች የተቀነባበረ ነው የተባለ የግድያና የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተደረገባቸው፡፡ በሙከራው ተሳትፈዋል የተባሉ ሁለት የሃምሳ አለቆችን ጨምሮ ወደ አስር የሚጠጉ የክብር ዘበኛ ጦር አባላት የሆኑ ወታደሮች እዚያው ቤተመንግስቱ ውስጥ ተረሸኑ፡፡ ይህ በሆነ በማግስቱ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በኮናክሪ አደባባይ ያደረጉት ንግግር፤ ኮሎኔል መንግስቱ ሃይለማርያም በ1967 ዓ.ም የደርጉ ሊቀመንበር የነበሩትን ጀነራል ተፈሪ በንቲንና ሌሎች ተቀናቃኞቻቸውን ቤተመንግስት ውስጥ ከረሸኑ በኋላ በአብዮት አደባባይ ያደረጉትን ንግግር የሚያስታውስ ነበር፡፡

“የምዕራብ የአድህሮት ሃይሎች ወኪል በሆኑ ከሀዲ ፀረ አብዮተኞች የተቃጣው የአብዮት ቅልበሳ ሴራ በሀቀኛ የአብዮቱ ልጆች ተበጣጥሶ ከሽፏል። የጊኒ አብዮተኞች ከተከላካይነት ወደ አጥቂነት ይሸጋገራሉ፤ የኢምፔሪያሊዝም ቅጥረኛ የሆኑ ፀረ አብዮተኞችን ከገቡበት እየገቡ የእጃቸውን ይሰጧቸዋል!” በማለት ፕሬዚዳንቱ በአደባባዩ ለተሰበሰበው ህዝብ ንግግር አደረጉ፡፡ ይህ ንግግራቸውም በጊኒ የድህረ ነፃነት የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ የጨለማው ዘመን መጀመሩን የሚያበስር ንግግር ሆኖ ተመዘገበ፡፡ የዘፈቀደ እስር፣ የይስሙላ ፍርድ፣ የአደባባይ ርሸናና አሰቃቂ ግርፋት የእለት ተዕለት ክንውን ሆነ፡፡ ተቃዋሚ ፖለቲከኞችና ደጋፊዎቻቸው የዚህ አሰቃቂ እርምጃ ዋነኛ ሰለባዎች ሆኑ፡፡ የደመወዝ ጭማሪ የጠየቁ መምህራን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አቋቁመው ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ከፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ጋር እንዲፎካከሩ እጩዋቸውን ያቀረቡ ነጋዴዎች ታስረው ለሳምንታት በአስከፊ ሁኔታ በግርፋት ሲሰቃዩ ከከረሙ በኋላ በአደባባይ ተረሸኑ፡፡ በ1970 ዓ.ም ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ድንገት በቴሌቪዥን ብቅ አሉና “የኢምፔሪያሊዝምና የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ ቡችሎች የሆኑ አምስተኛ ረድፈኞች፤ በፓርቲያችንና በመንግስት መዋቅር ውስጥ ከላይ እስከታች እንደተሰገሰጉ ተደርሶባቸዋል” በማለት መግለጫ ሰጡ፡፡

ከሶስት ቀናት በኋላም በመቶ የሚቆጠሩ ምኒስትሮች፣ የገዥው የጊኒ ዲሞክራቲክ ፓርቲ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባሎችና አምባሳደሮች በቁጥጥር ስር ውለው በከፍተኛው አብዮታዊ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ በቴሌቪዥን ታዩ። አንዳቸውም ጠበቃ አቁመው ለመከራከርም ሆነ የህግ የምክር አገልግሎት ለማግኘት ይቅርና የእምነት ክህደት ቃላቸውን ለመስጠት እድል አላገኙም። በጥይት እንዲደበደቡ ከተወሰነባቸው ሌላ በስቅላት እንዲቀጡ የተበየነባቸው ሃምሳ ስምንት ባለስልጣኖች በኮናክሪ አደባባይ ሲሰቀሉ ሂደቱን በቀጥታ ሲያስተላልፍ የነበረው የቴሌቪዥን ጋዜጠኛ ሁኔታውን የገለፀው “በኮናክሪ የአብዮት አደባባይ አሁን አንድ አሪፍ የካርኒቫል ትርኢት በመካሄድ ላይ ይገኛል” በማለት ነበር፡፡ አንዳንድ ከፍተኛ ባለስልጣኖች ከፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ጋር ያላቸው ቅርበትና ወዳጅነት ዋስ ጠበቃ ይሆነናል ብለው ተማምነው ነበር፡፡ ይህ እምነታቸው ግን ባዶና ከንቱ ቀቢፀ ተስፋ ብቻ ነበር። “የአብዮታዊው መሪ አብዮታዊ ሰይፍ” ለቅርብ ወዳጅነት ቅንጣት ታክል ቁብ የሌለው ነበር፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ በጥይት አስደብድበው ወይም በስቅላት ካስገደሏቸውና የሞት ቅጣቱ ቢቀርላቸውም በወህኒ ቤት እድሜ ልካቸውን እየማቀቁ እንዲኖሩ በእስራት ከቀጧቸው ባለስልጣኖች ውስጥ ሀምሳዎቹ የቅርብ የትግል አጋርና ወዳጃቸው የነበሩ ምኒስትሮች ናቸው፡፡

ከእነዚህም ውስጥ ጊኒ ካፈራቻቸው ድንቅ ዲፕሎማቶች አንዱ የሆኑትና አቶ ክፍሌ ወዳጆን ተከትለው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ዋና ፀሐፊ የነበሩት ዲያሎ ቴሊ ይገኙበታል፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬ ስልጣን ላይ ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ ተጠናውቷቸው ሌት ተቀን ሲያባንናቸው የኖረው ክፉ መንፈስ የጊኒን አብዮት ለመቀልበስ “የምዕራባውያን አድህሮት ሃይሎችና የሀገር ውስጥ ቡችሎቻቸው ሴራ” ነው አሉ፡፡ ለምሳሌ በ1972 ዓ.ም በመላው ጊኒ የመድሀኒት እጥረት ተከሰተና ጉዳዩ ተነገራቸው፡፡ ፕሬዚዳንት ሴኩቱሬም በቴሌቪዥን ቀረቡና በጊኒ የተከሰተው የመድሃኒት እጥረት የተፈጠረው የኢምፔሪያሊዝም ቅጥረኞች የሆኑ ሃኪሞች የአብዮቱን ገጽታ ለማበላሸት ሆን ብለው በሸረቡት ሴራ መሆኑን ተናገሩ፡፡ በ1973 ዓ.ም በጊኒ አንዳንድ አካባቢዎች የኮሌራ ወረርሽኝ መከሰቱ ሲነገራቸው ወረርሽኙ የተከሰተው በፀረ - አብዮተኞች ሴራ እንደሆነና ይህንን ታላቅ የፀረ አብዮተኞች ሴራ ህዝቡ በንቃት በመከታተል እንዲያከሽፈው ጥሪያቸውን አቀረቡ፡፡ በ1976 ዓ.ም ደግሞ ለአፍሪካ የእግር ኳስ ሻምፒዮና ለፍፃሜ ደርሶ የነበረው የጊኒ ብሔራዊ ቡድን የተሸነፈው፣ ፀረ አብዮተኞች በጐነጐኑት ሴራ እንደሆነ በይፋ አስታወቁ፡፡

ይህን በመሰለው የቆራጡ አብዮታዊ መሪ አህመድ ሴኩቱሬ፤ አገዛዝ ስር የወደቁት ጊኒያውያን ቀስ በቀስ በባርነት ከሚገኝ የድሎት ኑሮ ይልቅ ነፃነታችንን ተጐናጽፈን በድህነት ብንኖር ይሻለናል ያሉበትን ጊዜ በሹክሹክታ መራገም ጀመሩ፡፡ ይህን በማለታችሁ ተሳስታችኋል ብሎ የሚፈርድባቸው የለም፡፡ ያጡት ነፃነታቸውንም ምቾታቸውንም ነበርና፡፡ ይሁን እንጂ አንሾካሹከው ብቻ ፀጥ አላሉም፡፡ ከጠቅላላ ቁጥራቸው አንድ አምስተኛ የሚሆኑት ጊኒያውያን የቆራጡ አብዮታዊ መሪን የብረት ክንድ ለማምለጥ ወደ ጐረቤት አገሮች ጨርቄን ማቄን ሳይሉ ቀያቸውን ጥለው ተሰደዱ፡፡

Published in ከአለም ዙሪያ

              በዘንድሮ የ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” አብሮ የመኖር ውድድር፣ በቀጥታ የቴሌቭዥን ስርጭት ወሲብ በመፈፀም አነጋጋሪ ሆና የሰነበተችው ኢትዮጵያዊቷ ቤቲ ከውድድሩ ተሰናበተች፡፡ ውድድሩ ከተጀመረ አራተኛ ሳምንቱን የያዘ ሲሆን እስካሁን ቤቲን ጨምሮ ስድስት ተባርረው 20 ተፎካካሪዎች ቀርተዋል፡፡ ከእነሱም መካከል ሌላው ኢትዮጵያዊ በአምላክ ተስፋዬ (ቢምፕ) ይገኝበታል፡፡ ቢምፕ ለውድድሩ የሄደው አገሩን ስለሚወድና በተገኘው አጋጣሚ ስለ ኢትዮጵያዊነቱ ለመግለፅ ነው ያሉት እናቱ ወይዘሮ ደብሪቱ ሰለሞን፤ ባለፈው አንድ ወር በነበረው ቆይታ ይህንኑ ፍላጎቱን ሲያንፀባርቅ መቆየቱን ተከታትያለሁ ብለዋል፡፡ ‹‹ልጄ የአገር ፍቅር ስላለው በቢግ ብራዘር አፍሪካ ውድድር ፍቅሩን ለመግለፅ እድል አግኝቷል፡፡ ባንዲራው አብሮት ነው፡፡ ሁልጊዜም በሚለብሰው ካኒተራ ወይ ኮፍያ አሊያም በእጁ ላይ የአገሩ ባንዲራን ትቶ አያውቅም፡፡

የሚኖርበት መኝታ ቤቱ እንኳን በባንዲራ ያጌጠ ነው›› በማለት እናቱ ወይዘሮ ደብሪቱ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ ልጃቸው በአኗኗሩ እያሳየ ያለው ባህርይ ከልጅነቱ ጀምሮ ያደገበት ስብእናው እንደሆነ የገለፁት እናቱ፤ ባለፉት አራት የውድድር ሳምንታት እንዲባረር አንድ ድምፅ ብቻ እንደተሰጠበት ገልፀው፤ የውድድሩን ውጣውረድ በመቋቋም ሳይሰላችና ለሌሎች ተወዳዳሪዎች እንክብካቤ ሳይነፍግ እስከመጨረሻው ምእራፍ ሊዘልቅና ሊያሸንፍ እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ በ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ውድድር የኢትዮጵያውያን መሳተፍ ጠቀሜታ አለው የሚሉት ወይዘሮ ደብሪቱ፤ ውድድሩ የአገርን ባህል ለማስተዋወቅ እና ገፅታ ለመገንባት ሁነኛ መድረክ መሆኑን አስረድተው፤ ልጃቸው አብረውት ከሚኖሩት ተወዳዳሪዎች ስለ ኢትዮጵያ ብዙ ጥያቄዎች እንደሚቀርቡለት እሱም ስለ ባህሏ ፤ስለ ታሪኳ፤ የሰው ዘር መገኛ ስለመሆኗ፣ ስለ ቡና፤ ስለእንጀራውና ስለሽሮው ሳይሰለች ሲያስረዳ ተመልክተነዋል ብለዋል፡፡ ከውድድሩ በወጣች ማግስት አስተያየት የሰጠችው ቤቲ ስላሳለፈችው ጊዜ ስትናገር ቤቱን ለቅቆ መውጣት ከባድ ነው፡፡

ቦልት እና እኔ ጥሩ ወዳጆች ነበርን፡፡ ከውድድሩም በኋላ በወዳጅነት እንደምንቀጥል እርግጠኛ ነኝ” ብላለች፡፡ በውድድሩ ላይ እስከ መጨረሻው እዘልቃለሁ ብዬ አስብ ነበር ያለችው ቤቲ በውድድሩ፤ ምርጥ ተሳትፎ እንደነበራት፤ በዚህም መኩራቷን እንደተናገረች “ስዌታን” የተባለው የደቡብ አፍሪካ ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ ቤቲ “ዘ ቼዝ” የሚል ልዩ ስም በተሰጠው የዘንድሮ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” አብሮ የመኖር ውድድር ገና በመጀመርያው ሳምንት ቦልት ከተባለው ሴራሊዮናዊ ተወዳዳሪ ጋር በፈፀመችው ወሲብ ትኩረት ስባ ስታወዛግብ ቆይታለች፡፡ በ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” የስምንት አመት ታሪክ በቀጥታ ስርጭት የታየ ወሲብ ሲፈፀም የቤቲ እና የቦልት የመጀመርያው ነበር፡፡ ቤቲ ለአገሯ ባህልና ወግ ክብር አልሰጠችም በሚል በማህራዊ ድረገፆች እና በብሎግ መድረኮች ላይ ስትብጠለጠል መሰንበቷም ይታወቃል፡፡ ቤቲ በ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ኢትዮጵያን አትወክልም በሚል ለተቃውሞ በተከፈተ የፌስ ቡክ ድረገፅ ላይም በአገር ውስጥ እና በዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ ትችት ተሰንዝሮባታል፡፡

የቤቲ ከውድድሩ ድንገት መባረር ፍቅረኛዋ ሆኖ ለሰነበተው ሴራሊዮናዊ ቦልት መርዶ እንደሆነበት ዘገባዎች ጠቁመዋል፡፡ ስንብቷን ባረጋገጠችበት ምሽት ሁለቱም በሃዘኔታ ተውጠው ሲተቃቀፉ እና ሲሳሳሙ መታየታቸውንም እነዚሁ ዘገባዎች አውስተዋል፡፡ ቦልት ምስጢረኛው፤ የልብ ወዳጁ እና ፍቅረኛውን ቤቲ በማጣቱ ብቸኝነት እንደሚያስቸግረውና እሱም ቢሆን በውድድሩ የማሸነፍ እድሉ የጠበበ እንደሆነ “ዘ ስታንዳርድ ዲጂታል ኒውስ” ጽፏል፡፡ ለሴራሊዮናዊው ቦልት ከዚህ በኋላ የሚኖረው የ “ቢግ ብራዘር አፍሪካ” ቆይታ ማራኪ እንደማይሆን እየተነገረ ሲሆን ፋቲማ ከተባለች ማሊያዊት ጋር የጀመረው ግንኙነት መፅናኛው ሊሆን እንደሚችልም ከወዲሁ ተተንብይዋል፡፡

ከሁለት ሳምንት በፊት 36ኛ ዓመት ልደቱን ያከበረው እና “ጄይዙስ” የተባለ አዲስ አልበሙን ከሰሞኑ ለገበያ ያቀረበው ካናዬ ዌስት፤ የዘመኑ ስቲቭ ጆብስ እኔ ነኝ ሲል ተናገረ፡፡ በሌላ በኩል ካናዬ ዌስት እና ፍቅረኛው ኪም ካርዴሽያን ከሳምንት በፊት የመጀመርያ ሴት ልጃቸውን የወለዱ ሲሆን ኖርዝ ኖሪ ዌስት የሚል ስምም አውጥተውላታል፡፡ ሁለቱ ዝነኞች ለሴት ልጃቸው ያወጡት ስም ለብራንድ አይመችም ተብሎ ቢተችም ከተወለደች ወር ያልሞላትን ህፃን የመጀመርያ ፎቶ ለማግኘት የመገናኛ ብዙሃን እሽቅድድም ላይ እንደሆኑ የጠቀሱት ዘገባዎች፤ የህፃኗ ፎቶ እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር ሊያወጣ እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ሰሞኑን ሁለት ሚዲያዎች የኖርዝ ኖሪ ዌስት የመጀመርያ ፎቶን አግኝተናል በማለት ህትመታቸውን ቢያሰራጩም ፎቶው ሃሰተኛ እንደሆነ መታወቁን ቲኤምዜድ ዘግቧል፡፡

“ፒፕል ማጋዚን” የብራድ ፒት እና አንጀሊና ጆሊ ሁለት መንታ ልጆችን የመጀመርያ ፎቶ በ14 ሚሊዮን ዶላር ገዝቶ ማተሙን ያስታወሰው ዘገባው፤ ቤተሰቡ ይህን ገንዘብ ለበጎ አድራጎት እንደለገሱ እና ካናዬ እና ፍቅረኛውም ተመሳሳይ ነገር እንደሚፈጽሙ ይገመታል ብሏል፡፡ የመጀመርያ ሴት ልጁን ባገኘ በማግስቱ “ቀጣዩ ስቲቭ ጆብስ እኔ ነኝ” ሲል የተናገረው ካናዬ ዌስት፤ “በኢንተርኔት፤ በሙዚቃ፤ በፋሽንና በባህል የምፈጥረው ተፅእኖ እንደ ስቲቭ ጆብስ አብዮተኛ ያደርገኛል” ብሏል፡፡

በራፐርነቱ የሚታወቀው ካናዬ ዌስት፤ 100 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ሲኖረው፤ በቴሌቭዥን ሪያሊቲ ሾው እና በፋሽን ኢንዱስትሪው አውራነቷን ያስመሰከረችው ፍቅረኛው ኪም ካርዴሽያን 40 ሚሊዮን ዶላር ሃብት አስመዝግባለች፡፡ ካናዬ ዌስት ከ7ኛ አልበሙ “ጄይዙስ” በፊት አስቀድሞ ባሳተማቸው ስድስት አልበሞች በመላው ዓለም 15 ሚሊዮን ቅጂዎች የተሸጡለት ሲሆን 14 የግራሚ ሽልማቶችን ጨምሮ ከ47 በላይ የተለያዩ ሽልማቶች በማግኘት ከፍተኛውን ስኬት የተቀዳጀ ራፐር ነው፡፡

“ማን ኦፍ ስቲል” በተባለው ፊልም ላይ የሱፐር ማንን ገፀባህርይ በብቃት በመተወን ሄነሪ ካቪል እንደተዋጣለት “ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር” ገለፀ፡፡ እንግሊዛዊው ተዋናይ ሄነሪ ካቪል ሱፐርማንን ለመምሰል ሲል 40 ፓውንድ ኪሎ ቀንሷል ያለው ዘገባው፤ ይህን ለማሳካትም ለ11 ወራት በሳምንት 12 ሰዓታትን የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ማድረጉን አትቷል፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ለእይታ የበቃው ፊልሙ፤ በመላው ዓለም ያስገባው ገቢ 400 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል፡፡

የሱፐር ማን ፊልሞች ተወዳጅነት በአሜሪካ ብቻ ተወስኖ ቢቆይም “ማን ኦፍ ስቲል” ከአሜሪካ ባሻገር በመላው ዓለም ተወዳጅነት በማግኘት የመጀመርያው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ዋርነር ብሮስ ለፊልሙ በጀት 225 ሚሊዮን ዶላር ያወጣ ሲሆን፤ የሱፐር ማን ገፀባህርይ በካርቱን ኮሚክ መፅሃፍ፤ በቲቪ ተከታታይ ፊልሞች እና እስካሁን በተሰሩ ፊልሞቹ ላለፉት 70 አመታት ዝናና ስኬትን ተቀዳጅቶ መቆየቱ ይታወቃል፡፡ “ማን ኦፍ ስቲል” መታየት ከጀመረ በኋላ ከሱፐር ማን ጋር የተያያዙ የንግድ እንቅስቃሴዎች መሟሟቃቸውን የዘገበው “ብሉምበርግ ኒውስ” በበኩሉ፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የሱፐር ማን ቲሸርቶች እና አሻንጉሊቶች እንደተቸበቸቡ ገልጿል፡፡

ቁምነገር የጋዜጠኞች ማሰልጠኛ ማዕከል በተለያዩ የጋዜጠኝነት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ትናንት ማታ አስመረቀ፡፡ ለአራተኛ ዙር የተመረቁት 31 ተማሪዎች በመሰረታዊ ጋዜጠኝነት፣ ዜናና ፊቸር አፃፃፍ እና በቃለምልልስ ቴክኒክ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል፡፡ ምረቃው የተካሄደው ራስ ሆቴል ጀርባ በሚገኘው የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 አዳራሽ ነው፡፡

በአንጋፋው ድምፃዊ መሐሙድ አህመድ በ“የሺ ሀረጊቱ” የተሰኘ ዘፈን መነሻነት የተፃፈው ልቦለድ መፅሐፍ ታትሞ ለንባብ ቀረበ፡፡ በዚህ ሳምንት እየተሰራጨ ያለውን መፅሐፍ የደረሰው ደጀኔ ተሰማ ነው፡፡ 235 ገፆች ያለውን መፅሐፍ ያተመው እታፍዘር ማተሚያ ቤት ሲሆን አከፋፋዩ ሊትማን ጀነራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ነው፡፡ መፅሐፉ በ40 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በሌላም በኩል በጋዜጠኛ አቤል አለማየሁ እና ኤልያስ ገብሩ የተዘጋጀው “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡

ጋዜጠኞቹ 255 ገፆች ባለው መፅሐፋቸው ከ12 ምሁራን፣ ጋዜጠኞች፣ የሐይማኖት ልሂቃን እና ፖለቲከኞች ጋር የተደረጉ ሙግቶችና ውይይቶች አካተዋል፡፡ በመፅሐፉ ያለፈው መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩትና ዘንድሮ ህይወታቸው ያለፈው ኮሎኔል ደበላ ዲንሳ የመጨረሻ ቃል፣ የሃይማኖት መቻቻል፣ ሕገመንግስት፣ የብርቱካን ሚደቅሳ ፖለቲካ የሚሉና ሌሎች ርእሰ ጉዳዮች ተካተዋል፡፡ መፅሐፉ በሀገር ውስጥ በ49.60 ብር በውጭ ሀገራት በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Page 1 of 17