አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?)

ወዳጆቼ፤ የጥምቀት በዓል እንዴት አለፈ እባካችሁ? በሸጋ ያለፈ ይመስለኛል (እኔ ከናንተ ባላውቅም) ከሁሉም ያስደመመኝ ግን ምን መሰላችሁ? በጥምቀት ይወረወር የነበረው ሎሚ ተረት ሆኖ (እንደ ድህነት? ማለት ነው) ዘንድሮ በፕሪም ተተክቷል የሚባል ነገር ሰምቻለሁ፡፡ “ወጭ ለምኔ” ያሉ የዘመኑ ወጣቶች ደግሞ (በሬ ለምኔ እንደሚባለው) የሞባይል ነምበራቸውን ቆነጃጅቱ ደረት ላይ ሲወረውሩ እንደዋሉም የአውዳመት የወሬ ምንጮቼ ሹክ ብለውኛል፡፡ በደቡብ አፍሪካው የባለፈው ሰኞ የብሄራዊ ቡድናችን ግጥምያ እለት የተባለውን ሰምታችሁልኛል? “ውበት ሲለካ የኢትዮጵያ ሴቶች ናቸው ለካ!” የሚለውን ማለቴ ነው፡፡ (ለነገሩ ሲያንሳቸው እኮ ነው!!) ነገርዬውን ዝም ብዬ ሳስበው ግን የኢትዮጵያን እንስቶች ውበት ድንገት ያጐሉት ያለፈው የአፍሪካ ዋንጫ ሻምፒዮን ከሆነችው ዛምቢያ ጋር ገጥመው (ያውም በጐደሎ ተጫዋቾች) ድንቅ የኳስ ጥበብ ያሳዩት የብሄራዊ ቡድናችን አባላት ይመስሉኛል - (ያዳኑን እነ አዳነን ማለቴ ነው!) የሴቶቻችን ውበትማ አዲስ ክስተት አይደለማ!! እኔ የምለው ግን… በኢቴቪ ቀርቦ አስተያየቱን የሰጠ አንድ

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያበደ አድናቂ፤ ቡድናችንን ከእነሜሲ ጋር ሁሉ ሲያነፃፅር እንደ ነበር ሰምታችኋል? (ቢጋነንም ከጋለ ስሜት የመነጨ ነው ብለን እንለፈው) በነገራችሁ ላይ… ይሄ ህዳሴያችን ብዙ ታሪኮቻችንን እያደሰልን አይመስላችሁም! (በእድል እኮ አይደለም በትጋት እንጂ!) ከህዳሴው ጋር ያልታደሰልን ዋናው የህይወታችን ክፍል ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ያልታደለው ፖለቲካችን ብቻ!! እንኳንስ ሊታደስ ቀርቶ ጭርሱኑ ወደ ኋላ… ወደ ጥንቱ የጨለማ ዘመን (dark age) እየጐተተን፣ የዓለም መሳቂያ መሳለቂያ ሊያደርገን ዳር ዳር እያለ እኮ ነው! ፖለቲከኞችን በማሰር፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ጋዜጠኞች ለስደት በመዳረግና ወህኒ ቤት በመከርቸም፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ነፃ እንቅስቃሴ በማፈን፣ በሙስናና በመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ወዘተ… ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ስሟ እየተነሳ መሆኑ ፀሃይ የሞቀው አደባባይ ያወቀው እውነት ነው፡፡ በእርግጥ እንዲህ ያለውን ውንጀላ ባልወለደ አንጀታቸው የሚሰነዝሩት የኢትዮጵያ በጐ ነገር የማይዋጥላቸው እንደ ሂዩማንስ ራይት ዎች ያሉ ጨለምተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሆኑ ሁሌም ገዢው ፓርቲያችን ይነግረናል (እንዳንሳሳት ብሎ እኮ ነው!) ችግሩ ግን ምን መሰላችሁ? እዚሁ ከምርጫ ቦርድ ህጋዊ ሰርተፊኬት ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱትም ህጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሟጋቹን ውንጀላ አንድም ሳያስቀሩ ይቀበሉታል፡፡

(ታዲያ ምን ተሻለ?) ምን መቀበል ብቻ… “መች ተነካና… ይታያል ገና!” ባይ ናቸው፡፡ (የገዢውን ፓርቲ ጉድ ማለታቸው እኮ ነው!) እኔ የምለው ግን… የአገር ሽማግሌዎች ቡድን መሪ የሆኑት ባለውለታችን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ ፓርቲዎችን የማስታረቅ በጐ ሚናቸውን እንዴት ዘነጉት? ለነገሩ በእሳቸውም አይፈረድም እኮ! (የአውሮፕላን ወጪ ገደላቸዋ!) እንዴ… በ97 የፖለቲካ ቀውስ ጊዜ ታስረው የነበሩትን የቅንጅት አመራሮች ከመንግስት ጋር ለማስማማት ከአሜሪካ ኢትዮጵያ የነበረውን ጉዞ የውሃ መንገድ አድርገውት ነበር እኮ! ያውም በገዛ ገንዘባቸው እየተመላለሱ፡፡ ግን ምናለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚመላለሱበትን የአየር ትኬት ስፖንሰር ቢያደርጋቸው? (የአገር ጉዳይ አይደለም እንዴ?!) ለማንኛውም ግን ፕሮፌሰሩ አንዴ እንደምንም ወደ አገራቸው ጐራ ብለው ኢህአዴግንና ተቃዋሚዎቹን “አንተም ተው! አንተም ተው!” ቢሏቸው ሳይሻል አይቀርም ባይ ነኝ፡፡

(እረስቼው! ምርጫ ቦርድም ለካ ሌላው የፓርቲዎች የኩርፊያ ሰበብ ነው) እሱ እንኳን እርቅ ሳይሆን “ማጥራት” ነው የሚሻለው፡፡ አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?) እንዴ… ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ከ15 አመት በኋላ በጐ እንቅስቃሴ የጀመረው እግር ኳሳችን እንኳ የእነቬንገርን ቀልብ ስቧል እየተባለ እኮ ነው፡፡ ፖለቲካችን ግን ይኸው 21 አመት ወደኋላ መምዘግዘግ ይዞላችኋል - ያውም ህዳሴያችንን ይዞ (ወይ ነዶ አሉ!) አያችሁ… ይሄ ክፉ ፖለቲካችን የጀመርኩትን የጥምቀት ወግ ሳልጨርስ እንዴት ጐትቶ ውስጡ እንደዶለኝ! (ፖለቲካችን እርግማንና ወቀሳ ምሱ ነው አሉ!) እኔ የምለው… በዘንድሮ የጥምቀት በዓል መዲናዋ እንዴት እንደፀዳችና እንደተዋበች በደንብ አስተውላችኋል? እንዴ… ከተማዋ 125ኛ ዓመት ልደቷን አንድ አመት ሙሉ ስታከብርም እኮ እንዲህ አላማረባትም! (አክብሮ መና ይሏል ይሄ ነው!) እውነቴን ነው የምላችሁ… የመዲናዋ ወጣት በዓሉን ያከበረው “ለጥምቀት ያልሆነ ከተማ…” በሚል አዲስ ምሳሌያዊ አባባል ይመስላል፡፡

(ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንዲሉ!) ቆይ ግን ያልፀዳና ያልተዋበ የመዲናዋ ስፍራ አለ እንዴ? (ማዘጋጃ ቤት ሲያሾፍ እንደኖረ የገባን አሁን ነው!) ለወትሮው የሽንትና የቆሻሻ ክምር የነበሩ ስፍራዎች ሁሉ ፀድተውና በተለያዩ ቀለማት ተኳኩለው “ሸገር” ተውሰን ያመጣናት ከተማ ልትመስለን ምን ቀራት? መርካቶ ሰባተኛ አካባቢ እንዴት በባንዲራና በፊኛ አሸበርቆ እንደነበር መስተዳድሩ አይቶት ይሆን? (ማን ነበር “ይደገም ቅዳሜ” ያለው…) ከምሬ ነው… መቼም አይቶት ከሆነ የመዲናዋ ልደት “በህዝብ ጥያቄ በድጋሚ ይከበራል” ማለቱ አይቀርም! እኔ ግን የልደቱን በድጋሚ መከበር ምንም ቢሆን እንደማልደግፍ ከወዲሁ አቋሜን ልገልፅ እወዳለሁ፡፡ እንደ 34ቱ ፓርቲዎችም ፒቲሽን ማሰባሰብ ከጀመርኩ አንድ ሁለት ቀናት አልፎኛል፡፡ አያችሁ… ባለፈው ተመክሮ እንደተገነዘብነው መስተዳድሩ የፓርቲና የፌሽታ ነገር አይሆንለትም፡፡ (ፍንዳታ ቢጤ ነው!) የመዲናዋን 125ኛ አመት ከአንድ አመት በላይ እኮ ነው ያከበረው፡፡ (ለመሆኑ ጊነስ ላይ ተመዘገበለት ይሆን?) እናላችሁ… ራሴ ያነሳሁትን የይደገም ጥያቄ ራሴ መቃወሜን እወቁልኝ፡፡ አንድ ጥያቄ ግን አለኝ፡፡ መስተዳድሩ የመዲናዋን ልደት ከአንድ አመት በላይ ሲያከብር (ራሱ ነው ያለን!) ምን ማስታወሻ የሚሆን ነገር ለከተማዋ ሰራላት? (ከፕሮፓጋንዳው ውጭ ማለቴ ነው!) ይኸውላችሁ… እኔ ከጥምቀቱ የወጣቶች ቡድን ምን ቁምነገር ቀሰምኩ መሰላችሁ? የመዲናዋ ወጣት ሲፈልግና ልቡ ያመነበት ጉዳይ ሲሆን እንደንብ መንጋ ነው - የያዘውን ስራ ዶግ አመድ ያደርገዋል፡፡ አድምቶ ይሰራዋል! (በኢህአዴግ ቋንቋ!) ይታያችሁ… የፅዳት ሠራዊት የለ! የህዝብ ንቅናቄ የለ! 1ለ5 አደረጃጀትማ ጭርሱኑ ትዝ ያለውም የለ!! አያችሁልኝ… ወጣት ባመነበት ጉዳይ ላይ እንዲህ አጀብ ያሰኛል - ያውም ያለ አንዳች የካድሬ ፕሮፓጋንዳና አጀብ!!

እኔማ ምን አሰብኩ መሰላችሁ? ጥምቀት ለምን ሁለቴ አይከበርም አልኩኝ (ግን ለራሴ ነው) (ከተማዋ እኮ አበባ መሰለች!) ጥምቀት እንዲህ ከሆነ ግን ለምንስ የፖለቲካ ጥምቀት፤ የዲሞክራሲ ጥምቀት፣ የልማት ጥምቀት፣ የመልካም አስተዳደር ጥምቀት፣ የጥበብ ጥምቀት፣ የፕሬስ ነፃነት ጥምቀት፣ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ጥምቀት፣ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ጥምቀት ወዘተ… ወዘተ… አያሌ የህዳሴ ጥምቀቶችን አይኖሩንም ስልም ተመኘሁ - ሁሉም በአንድ መንፈስ ከልቡ የሚያከብረው፡፡ ባይገርማችሁ… በፕሮፓጋንዳ ያልተካበደ ህዳሴ እንዴት እንዳማረኝ አልነግራችሁም (አምሮት መብቴ መሰለኝ!) ውድ አንባቢያን፡- ፕሮፓጋንዳ ያልበዛበት ፖለቲካ የት እንደሚገኝ የምታውቁ ከሆነ ብትጠቁሙኝ ወሮታውን እከፍላለሁ፡፡ እኔ የምለው ግን… እኔ ብቻ ነኝ ወይስ እናንተም ናችሁ የፖለቲካ ህዳሴ የናፈቃችሁ? ለነገሩ ባይናፍቃችሁም አይፈረድባችሁም! (ተስፋ ቆርጣችሁ እኮ ነው!) እንዴ ፖለቲካችን “ከርሞ ጥጃ”፣ “ታጥቦ ጭቃ” ሲሆንባችሁስ? እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… በጥንቱ አካሄድማ የፖለቲካ ህዳሴን መመኘት ባዶ ህልም ከመሆን ፈፅሞ አያልፍም፡፡ ለውጥ የምንሻ ከሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድናችን ላይ የምናየውና የምንሰማው አይነት አዲስ አቅጣጫና አካሄድ ልንከተል ግድ ይለናል፡፡በእርግጥ በአንድ ጀንበር ስር ነቀል ለውጥ መጠበቅ ሲበዛ የዋህነት ነው፡፡ እንኳንስ በጦቢያ ፖለቲካ ቀርቶ በየትም አገር ቢሆን ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ እያደገ ነው የሚመጣው፡፡

የአፍሪካ ተቃዋሚዎች ስልጣንም ሆነ ዲሞክራሲ ዛሬውኑ ካልተንበሸበሽን ብለው የሙጥኝ ሲሉባቸው ፈረንጆቹ ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁ? “ዲሞክራሲ ሂደት ነው!” ይሉና ይገላገሏቸዋል፡፡ እንዴ ምን ያድርጉ ታዲያ? ለነገሩ የእኛዎቹንም እኮ እናውቃቸዋለን… ምርጫን የሞት ሽረት ጉዳይ ያደርጉት የለም እንዴ! ለዚህ እኮ ነው የሥነልቦና ትምህርት የሚያስፈልጋቸው፡፡ ከምሬ ነው… ፖለቲከኞቻችን የAttitude ለውጥ ካላመጡ ፖለቲካው መቼም አይለወጥም! እኔማ የስነልቦና ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ አሰልጣኝም (coach ወይም mentor ነገር) ይፈልጋሉ ባይ ነኝ! (ኢህአዴግንም ይጨምራል!) ፖለቲካ እኮ ብስለትም ብልህነትም ይፈልጋል፡፡ አጉል ብልጣብልጥነት ብቻውን የትም አላደረሰማ!! (ካላመናችሁኝ ኢህአዴግን ተመልከቱት!) ከችኩሉ ጥላቻ ተኮር ፖለቲካችን የምንላቀቀውም በጥሩ አሰልጣኝ ድጋፍ ይመስለኛል (የፖለቲካ ሰውነት ቢሻው ቢገኝማ ሽረት ነበር!) የሚገርማችሁ ግን በፖለቲካው ውስጥ ፀጉራቸው እስኪሸብት ኖረውበትም ዘንድሮም ቅንጣት ታህል ያልተለወጡ አያሌ ፖለቲከኞች በጦቢያ ምድር ሞልተው መትረፋቸው ነው፡፡ ልብ አድርጉ! እኔ ፈፅሞ የአገሬን ፖለቲከኞች የማንኳሰስ ድብቅ አጀንዳ የለኝም፡፡ የማንም ተላላኪም አይደለሁም! (ለምሳሌ የሻዕቢያ!) ራሳቸው ፖለቲከኞቻችን እኮ ራሳቸውን ለማንኳሰስ ማንንም አያክላቸውም!! (እዳ እኮ ነው የገባነው!) ባለፈው ሰሞን የኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች የቆየ ውዝግባቸወን እንደ አዲስ ሊጀምሩ መሆኑን ሰምቼ እንዴት እንደተቃጠልኩ አልነግራችሁም፡፡

እስቲ ይታያችሁ… ከኢህአዴግ ጋር የማይቀርላቸው “ልፍያ” ሳያንሳቸው እርስ በእርስ ፍልምያ መግጠማቸው ምን የሚሉት እዳ ነው (ወይስ የወዳጅነት ግጥምያ መሆኑ ነው!) እንዲህ ያሉት እኮ ፖለቲካም፣ ፓርቲም ወደሚለው ጉዳይ ከመግባታቸው በፊት ለራሳቸው ክብር መስጠትን የግድ መማር አለባቸው (እድሜማ አላስተማራቸውም!) ፈረንጆቹ postive attitude, self esteem ምናምን የሚለውን በደንብ በውስጣቸው ካሰረፁ በኋላ በማንኛውም ፈተናና ወከባ ተከበውም ቢሆን ፅናትና ብርታት ካላቸው ስኬት እንደሚቀዳጁም መማር፣ መሰልጠን፣ መለማመድ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የምርጫ ሰሞን ወከባን ለማስቀረት ብልሃቱ ዝግጅት ብቻ ነው! ኢህአዴግ ከችግሩ (ኃጢያቱ) ነፃ ነው እያልኩ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ የችግሩ እናት ማን ሆነና! በነገራችሁ ላይ ለኢህአዴግ የሚሰጠው ስልጠና ማተኮር ያለበት… ጦቢያን ለማሳደግ፣ ለማበልፀግ፣ ከድህነት ለማውጣት፣ ዲሞክራሲን ለማስፈን ወዘተ ከላይ የተቀባሁት እኔና እኔ ብቻ ነኝ የሚለው ክፉኛ የተጣባው አመለካከቱ ላይ ነው፡፡ “ፀሃዩን ንጉስ” በመቃወም ወደ ትግል የገባ ፓርቲ እንዴት ያንኑ የተቃወመውን አመለካከት ያቀነቅናል? (ታሪክ ራሱን ይደግማል አሉ!) ይሄ ሁሉ ስጋት ከምን የመጣ እንደሆነ እንድታውቁልኝ እሻለሁ! አያችሁ… እስከዛሬ ኦክስፎርድ ዲክሽነሪ Famine የሚለውን ቃል Food Shortage, scarcity, starvation ወዘተ በማለት ከፈታ በኋላ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ምሳሌ የሚጠቅሰው ጦቢያን እንደነበር እናውቃለን አይደል! አሁን ደግሞ ሳናስበው “ኋላ ቀር ፖለቲካ” ለሚለውም ቃል ዳግም አገራችን በዲክሽነሪው ላይ እንዳትጠቀስና ዳግም ሼም በሼም እንዳንሆን ክፉኛ ሰግቻለሁ፡፡

እናላችሁ… አገሬን እወዳለሁ የሚል ዜጋ ሁሉ ጦቢያን ከኋላቀር ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማውጣት ከፍተኛ እርብርቦሽ ያደርግ ዘንድ ጥሪ ቀርቦለታል፡፡ እኔ የምለው ግን… ሰሞኑን በድራማ መልክ በኢቴቪ የሚተላለፈውን ማስታወቂያ አይታችሁልኛል - በሁለት ጫማ የሚገዙ እንስቶች የተሰራውን ማለቴ ነው፡፡ በስተመጨረሻ ላይ አንደኛዋ አዲስ የገዛችው ጫማ ተረከዟን እንደላጣትና እግሯን እንዳቃጠላት ለጓደኛዋ በምሬት ስትነግራት “በደንብ ሳትመርጪ ለምን ገዛሽ?” ትላታለች (ዋጋሽን አገኘሽ በሚል ስሜት!) ለካስ ነገርዬው ለሚያዝያው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ የተሰራ ማስታወቂያ ነው፡፡ እኔ እኮ የቻይና ጫማ ገዝታ የተቃጠለች ነበር የመሰለኝ፡፡ (ቀላል ተሸወድኩ!) ለነገሩ የማይሆን ፓርቲ መምረጥ ከቻይና ጫማም የበለጠ ሊያቃጥል ይችላል፡፡ (ፈጣሪ ይጠብቀን እንጂ!) በመጨረሻ በምርጫው ለሚሳተፉ ፓርቲዎች (ከ29ኙ ውጭ) ሁሉ የሚመች ነጠላ ዜማ እንዳገኘሁላቸው ሳበስራቸው ኩራት ይሰማኛል (ቃል በቃል መቅዳት ያኮራል ተብሎ የለ!) እንዲህ የሚል ነው የዜማው ግጥም፡- በቃ በቃ አልፈልግም ሌላ ላይመች ላይደላ… (ከጫማው ማስታወቂያም ጋር ይሄዳል አይደል? በምርጫው የምትሳተፉ ፓርቲዎች ይመቻችሁ!!) ,

“ባህል ህይወት ነው፤ ሳንሱር ግን ማጭድ ነው”

በኢትዮጵያ የዘመናዊ ቴአትር ታሪክ ውስጥ በመድረክ የቀረበ ቀዳሚ ተውኔት ሆኖ የሚቆጠረው፤ ፊታውራሪ ተክለሐዋርያት ተክለ ማርያም የደረሱት “የአውሬዎች ተረት (ፋቡላ)” ነው፡፡ ይህ በግጥም የተዘጋጀ ድርሰት በ1903 ዓ.ም ተጽፎ ለልጅ እያሱ የተበረከተ ሲሆን፤ በቴአትር መልክ የቀረበው ግን በንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ዘመነ መንግሥት አልጋ ወራሹ ራስ ተፈሪ እንዲታይ በፈቀዱ ጊዜ ነበር፡፡ ቴአትሩም ተዘጋጅቶ ንጉሣዊው ቤተሰብና መኳንንት በተገኙበት በቴሬስ ሆቴል መድረክ ላይ ቀርቦ ታይቷል፡፡ ይሁን አንጂ ተውኔቱ ለጊዜው ፖለቲካ የማይስማማ፣ መኳንንቱንና ቤተክህነትን የሚነቅፍ (ሳቲር) ነው ተብሎ እንዳይታይ ተከለከለና ታትሞ ተሸጦ የነበረው የቴአትሩ መጽሐፍም ከሕዝብ ዘንድ ተለቅሞ እንዲሰበሰብ ተፈረደበት፡፡ ይህ ቴአትር እንግዲህ በአገራችን እንዳይታይ በይፋ ክልከላ የተደረገበት የመጀመሪያው ቴአትር መሆኑ ነው፡፡

ምንም እንኳ በዚህ ጊዜ ሳንሱር ወይም ቅድመ ምርመራ በሕግ ተደንግጐ ሥራ ላይ የዋለ ባይሆንም፤ “በአውሬዎች ተረት” ቴአትር ላይ የተጣለበት ገደብ፣ በኢትዮጵያ በተውኔት ሥራ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተተገበረ ሳንሱር ተደርጐ ሊወሰድ ይችላል፡፡ በመሆኑም በኢትዮጵያ የሳንሱር ጋሬጣ በመርዛማ እሾሁ የትእይንተ ጥበብን ተክል እየወጋ ማቁሰል የጀመረው፣ ተውኔት ገና በቡቃያ ላይ እያለ ነበር ማለት ነው፡፡ የሳንሱር በትር በቴአትር ጥበብ ላይ ሲሰነዘር ተውኔት ገና በተመልካቹም ሆነ በባለሙያው ዘንድ እምብዛም ያልተለመደ እና ያልተስፋፋ አዲስ ባህል ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ሳንሱር በተደራጀ መልክ ሥራ የጀመረው በፋሺስት ኢጣሊያ አምስት የወረራ አመታት ጊዜ ውስጥ ሲሆን ተቆጣጣሪ መስሪያ ቤቱም የፖለቲካ ቢሮ (Officio Politico) ተብሎ ይታወቅ ነበር፡፡ ከነፃነት ማግስትም በኋላ ይህ መስሪያ ቤት እንደ አዲስ ተዋቅሮ ለአሰራሩም ሕግና ደንብ ወጣለት፡፡

ሚያዝያ 21 ቀን 1935 ዓ.ም “የቴአትርና የሲኒማ አደራረግን ስለመመርመር” የወጣው አዋጅ ቁጥር 37/1935 በትእይንተ ጥበባት ላይ የተጣለውን ቅድመ ምርመራ (ሳንሱር) ሕጋዊ መሰረት ሰጥቶታል፡፡ ከዚህ አዋጅ በኋላ ሳንሱር የፅልመት አደረጃጀቱን አጐልብቶ ሙሉ አካል የሚያጐድልበት ስለቱን፣ ውጦ የሚያስቀርበትን የጨለማ ቋቱን አሰናድቶና አድብቶ ከተውኔት ጀርባ ቆመ፡፡ መልከ ጥፉን በስም ይደግፉ እንደሚባለው ለዚህ እኩይ የሳንሱር ተግባር አላማ ነው ተብሎ በአዋጅ የተገለጠው ግን “የሕዝቡን ፀጥታና ንፅህና ከብልግና መጠበቅ ነው” የሚል ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በተግባር እንደታየው ሳንሱር አካለ ጐደሎ ያደረጋቸው ወይም ጭራሹኑ እንዳይታዩ የከለከላቸው ተውኔቶች፤ የሕዝብን ፀጥታ የሚያውኩ ወይም ለመልካም ጠባይ ተጣራሪ የሆኑ ናቸው ተብለው የተገመቱ ሳይሆኑ፤ ለአገዛዙ ፖለቲካ አደገኛ ናቸው የተባለ ስራዎች ነበሩ፡፡

በዘውድ መንግሥትም ሆነ በደርግ ዘመን ሳንሱር የሚከናወንበት ጥርት ያለ መመሪያ ያልተዘጋጀለት በመሆኑ፤ የተከለከለውና የተፈቀደው በውል ስለማይታወቅ ለሳንሱር ሹማምንት የግል አስተያየት ሰፊ በርን ከፍቷል፡፡ አንዳንዴ የቴአትሩ ይዘት ከመርማሪዎቹ የመረዳት አቅም በላይ ሆኖ ሲገኝ፤ ተውኔቱ ግማሽ በግማሽ እንዲቆራረጥ ወይም እንዲታገድ ይወሰንበታል፡፡ ባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ ገብረመድህን በ1978 ዓ.ም ቴአትርን እና የሳንሱር አሰራርን አስመልክቶ ለተዘጋጀ አንድ ጥናት በሰጠው አስተያየት፤ “አንድ ሕዝብ የማወቅ ደረጃውን የኪነ ጥበብ ብስለት ደረጃው ይወስነዋል፡፡ የሳንሱር ባለሙያዎች፣ የኪነጥበብ ብስለታቸው ደካማ በመሆኑ በራሳቸው ውሱንነት ነው ማንኛውንም ነገር የሚወስኑት፡፡ የቀረበላቸው የፈጠራ ሥራ ጥበቡ የበሰለ ከሆነ ጣእመ ትርጉሙ ስለማይገባቸው ይከለክሉ ነበር፡፡ አሁንም ይከለክላሉ፡፡

ምክንያቱም ሰው በተፈጥሮው የማይገባውን ይፈራል… በአሁኑ ሰዓት ደራሲያንን ወዲህ ሳንሱርን ወዲያ ማዶ ያደረገው የሳንሱር ባለሙያዎች አላማ ነው፡፡ ራሳቸውን እንደ ፖለቲካ ጠባቂዎች ያደርጋሉ፡፡ ማንኛውንም ነገር ከፖለቲካ ጋር ያያይዙታል፡፡ አእምሯቸው በዚህ ረገድ ስለተገራ ፖለቲካዊ ይዘት የሌለው ነገር ሁሉ ፖለቲካ መስሎ ይታያቸዋል” ብሎ ነበር፡፡ ባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ ከአገራችን ደራሲያን መካከል በሳንሱር የተነሳ ብዙ መከራ የተቀበለ፤ የጥበብ ትሩፋቶቹም በዚህ የጨለማ አሰራር ከፍ ያለ አደጋ የደረሰባቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ፀጋዬ ሳንሱርን የሚረዳበት እና የሚገልፅበት መንገድ እንደ አንድ ተራ ፀረ ጥበብ የጨለማ አሰራር በመመልከት ብቻ ሳይሆን፣ ይህ እኩይ አሰራር የተፈጠረበትን ጥንታዊና ታሪካዊ መሰረት በመመርመር ጭምር ነው፡፡ ፀጋዬ ይህንን ተግባር ሲያስረዳም፤ “በስልጣን ሰይፍና በብዕር (The Sword and the Pen) መካከል ያለ ትግል ጥንትም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ወደፊትም የሚኖር አሳዛኝ እውነታ ይመስለኛል… ባህል ህይወት ነው፣ ሳንሱር ግን ማጭድ ነው፡፡ አንዱ ህይወት ያበስራል፣ አንዱ ህይወት ይቆርጣል፡፡ ብዕር የዘራውን ፍቅር ስልጣን በማጭድ ይቆርጣል፡፡ ብዕር የሕዝብ እፅዋት አትክልተኛ ነው፡፡

ጠመንጃ ደግሞ የእፅዋት አራጅ ነው፡፡ አንዱ በትጋት የተከለውን ታዳጊ ተክል፣ በትጋት ያለመለመውን ፀአዳ ሌላው በፋሺስታዊ ድንፋታ ይጨፈጭፋል፡፡ የዓለም የጥበባት ማዕከሎች ሁሉ የሕዝቦች ፍቅር መዝሪያ መድረኮች ናቸው፡፡ የሀገር መውደድ ብስራቶች (manifestation) ናቸው፡፡ እነዚሀን የሚቆርጥ የየዘመኑ የስልጣን ማጭድ ደግሞ “ሳንሱር” ይባላል… በሮማ ኢምፓየር ጊዜም፣ “ታላቁ ቆራጭ ወይም ታላቁ ሳንሱር፡፡ (The Great Censor) ተብሎ የሚጠራው ኢምፔረር ኔሮ ራሱ ነው፡፡ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ጊዜም ዋናው የብዕር ቆራጭ ራሳቸው ንጉሠ ነገሥቱ ነበሩ፡፡ በደርግ ዘመን ደግሞ ምክትል ርእሰ ብሔሩ [ጠቅላይ ሚኒስትሩ] ታማኝ የብዕር ቆራጮች ነበሩ፡፡ ቀለማችን የተደፋብን፣ ብዕራችንና ልሳናችን የተቆረጠብን፣ የተፈለጠብን እናውቀዋለን” በማለት ተናግሮ ነበር፡፡. ባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን ጥበብን አስመልክቶ ያደርጋቸው በነበረው ቃለ መጠይቆችና ውይይቶች ወቅት፤ ስለ ሳንሱር ሳያነሳ ያለፈበት ጊዜ የለም ለማለት ይቻላል፡፡ ፀጋዬ ስለ ሳንሱር ሲያወሳም፤ ሳንሱር የጨቋኝ መንግሥታትን ሰይፍ ወክሎ እንደሚቆም፣ ፍልሚያውም በዚህ የጨለማ የሰይፍ ኃይልና በብርሃናማው ብዕር መካከል መሆኑን፣ የጥበብን ጥንተ ታሪክ እየጠቀሰ ያስረዳ ነበር፡፡ ፀጋዬ እንዲህ ስለ ሳንሱር የሚጮኸውና የጨለማ ስራውንም ባገኘው መድረክ የሚገላልጠው ከማንም በላይ በሳንሱር የተነሳ ስራዎቹ ፍዳቸውን በማየታቸው የተነሳ ነበር፡፡

በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቴአትር ታሪክ ውስጥ እንደ ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን በሳንሱር የተነሳ የተሰቃየ ደራሲ የለም፡፡ ሳንሱር የፀጋዬን ስራዎች እየተከታተለ ማነቅ የጀመረው ገና ከጠዋቱ ከ1950ዎቹ መግቢያ ጀምሮ ነው፡፡ ከዚህ ጊዜ አንስቶ ከሰላሳ አመታት በላይ የሳንሱር ፅልመታዊ መጋረጃ ስራዎቹን ሲጋርድበትና ሲያምቅበት ከመቆየቱም በላይ፤ የሳንሱር ጦስ ወደ ግል ህይወቱ ተሸጋግሮ ኑሮን አክብዶበታል፡፡ ሎሬት ፀጋዬ በሳንሱር ሳቢያ በጥበብ ሥራዎቹ ላይ የደረሰበትን ግፍ የዛሬ አስር አመት ግድም እንዲህ ገልጦት ነበር፡፡ “ከፃፍኳቸው 41 ቴአትሮች ውስጥ (ከተረጐምኳቸውና በእንግሊዝኛም ከፃፍኳቸው ጭምር)፣ አሥራ ሁለቱን ሳንሱር ሙሉ በሙሉ አግዶብኛል፡፡ ሃያ አንዱን ቆራርጦብኛል፡፡ ሶስቱን ግማሽ ለግማሽ ጐራርዶብኛል፡፡ አራቱ ግን ገና ለመድረክ [አልቀረቡም] ከሶስቱ የሥነ ግጥም መፃህፍቶቼ ውስጥ (ሁለቱ ገና አልታተሙም)፣ በሰላሳ ሰባት ነጠላ ዝርዝር ግጥሞቼ ምክንያት፣ የሳንሱር ቢሮ፣ የፀጥታው ክፍል ቢሮና የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቴ ቢሮ ከፍተኛ ሹማምንት ገስፀውኛል፡፡ ቀጥተውኛል፡፡ ዝተውብኛል፡፡ በአንዲት “ጆሮ ገድፍ” በምትባል ትንሽ ቴአትር ምክንያት የጃንሆይ መንግሥት ፀጥታ ቢሮ፣ ለሃያ አራት ሰዓት በቁጥጥር ስር አውሎኛል” ብሏል፡፡

የፀጋዬ ቴአትሮችን በሳንሱር መቆራረጣቸው ወይም መከልከላቸው አልበቃ ያላቸው ሹማምንት “ጆሮ ገድፍ” እና ”አቡጊዳ ቀይሶ” የተሰኙት ድርሰቶቹ እንዲታሰሩ ወስነውባቸው ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ተንሰራፍቶ ከነበረው የሳንሱር መአት ተርፈው ለመድረክ የበቁት የባለቅኔ ሎሬት ፀጋዬ የተውኔት ሥራዎች “የደም አዝመራ”፤ “የሾህ አክሊል” እንዲሁም በዘውድ መንግሥት ፍፃሜ ዋዜማ ላይ የቀረበው “ሀሁ በስድስት ወር” እና ድህረ ደርግ የታየው “ሀሁ ወይም ፐፑ” ብቻ ናቸው፡፡ ጋሼ ፀጋዬ በእንግሊዝኛ የተፃፉ ስምንት ያህል ቴአትሮች ያሉት ሲሆን በውጪ አገር የቀረቡ የጥናት ሥራዎች በመሆናቸው ከሳንሱር ምርመራ ርግማን ለመትረፍ ችለዋል፡፡ በተለይ በደርግ ዘመን ፀጋዬ ከሥራ መታገድ እስከ እስር ድረስ የዘለቀ አደጋ በህይወቱ ላይ ሊደርስበት የቻለው የሳንሱር ክፍል ለፀጥታው መስሪያ ቤት ስለ ቴአትሮቹ ባቀረበው ሪፖርት የተነሳ ነበር፡፡ ለወቅቱ የመንግሥት ፖለቲካ ተቃራኒና አደገኛ ናቸው ተብሎ ሪፖርት የቀረበባቸው ተውኔቶች ፀጋዬ “እናት ዓለም ጠኑ” ሲል ወደ አማርኛ የመለሰው (Mother Courage) የተሰኘ የብሬሽት ድርሰት፣ “አቡጊዳ ቀይሶ” በሚል ከፋንሽን (Fanshen) ወደ አማርኛ የተረጐመው ድርሰት እና ጋሞ የተባሉት ነበሩ፡፡ በዚህ የተነሳም ፀጋዬ ቴአትር ከሚያዘጋጅሪት መድረክ ላይ በድንገት ተጠልፎ ተወስዶ ወደ ወህኒ እንዲወረወር ተደርጓል፡፡ የደረሰበት አደጋ ያሳሰባቸው የሴኔጋል ፕሬዚዳንት የነበሩት ወዳጁ ሴዳር ሴንጐር፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል እንዲሁም (Pen International) ከእስር እንዲፈታ ለደርጉ በተደጋጋሚ ባቀረቡት ብርቱ ተማፅኖ የተነሳ ፀጋዬ ከነህይወቱ ከደርግ እስር ቤት ለመውጣት ችሏል፡፡ ከእሥር ከተፈታ በኋላ የነበሩት ስድስት አመታት ግን ፀጋዬ ከሥራና ከደሞዝ ታግዶ በአይነ ቁራኛ እየታየ የቆየባቸው የግዞት ዘመናት ነበሩ፡፡ በ1983 ዓ.ም የደርግ መንግሥት ከወደቀ በኋላ፣ ፀጋዬ ገብረ መድህን ሰላም ወይም አጥፍቶ መጥፋት የሚል መልዕክት ያዘለውን “ሀሁ ወይም ፐፑ” የተሰኘ ቴአትር በአማተር ተዋንያን አማካይነት ለህዝብ አሳይቶ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ይኸው ቴአትር በአዋሳ ከተማ ለሕዝብ በቀረበበት ጊዜ ታጣቂዎች ባነሱት ብጥብጥ የተነሳ የቴአትሩ ተዋንያን በቆንጨራ፣ በሰደፍና በዱላ ጉዳት ደርሶባቸው ነበር፡፡ ይህም አዲሱ መንግሥት ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላ ፀጋዬን በጥበባዊ ሥራው ላይ የገጠመው የመጀመሪያው ችግር ሆነ፡፡

ምንም እንኳ የኢህአዴግ መንግሥት ማናቸውንም ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት የሚገድብ ቅድመ ምርመራ (ሳንሱር)ን ያነሳና መዋቅሩንም ያፈራረሰ ቢሆንም፣ የፀጋዬ ሥራዎች ግን በቴአትር ቤቶች የመታየት ፈቃድ በተደጋጋሚ እየተነፈጋቸው ለመድረክ ሳይበቁ ቀርተዋል፡፡ በተለያየ ጊዜ ፈቃድ ከተነፈጋቸው የፀጋዬ የተውኔት ሥራዎቹ ውስጥ “ሀሁ በስድስት ወር”፣ “ቴዎድሮስ”፣ “አጤ ምኒልክ” እና “ቴራቲረኞች” የተሰኘ ምፀታዊ ኮሜዲ ይገኙበታል፡፡ ፀጋዬም በጣም ያሳዘነውንና ይህንን ስውር የክልከላ ድርጊት “[መንግሥታዊ] ድፍን ዝምታ ወይም የመልስ አልባ ዝምታ ሳንሱር” ነው በማለት ስም አውጥቶለት ነበር፡፡ ሳንሱር በህግ የተከለከለ ቢሆንም በተለያየ አይነት ስምና አቀራረብ የጥበብ ጋሬጣ እየሆነ መሄዱንና በሌላ አገርም ይህንን አስመልክቶ ያለውን ልማድና አሰራር ጋሼ ፀጋዬ ሲናገር፤ “ለምሳሌ ዛሬ “ግምገማ” የሚለው ቃል በሥነ ጥበባት ሥራዎች ላይ ሲከሰት የሳንሱር የክርስትና ስም ሆኗል፡፡ በእንግሊዝ አገር ደግሞ ስሙን ሳይለውጥ ዛሬ “የብሪቲሽ ሳንሱሮች ቦርድ” (British Board of Censors) ቢባልም አልፎ አልፎ አፈፃፀሙ በርካሽ ሲኒማዎች ላይ እንጂ በስነ ፅሁፍ፣ በስዕል፣ በሙዚቃና ቴአትር ላይ ከቶም አይሰራም፡፡ የሀገር መውደድ አርማን የሚያንፀባርቁ ስራዎችንም አይቃወምም” ብሏል፡፡ ፀጋዬ ከሳንሱር የጨለማ ኃይል ጋር እየተፋለመ ያሳለፋቸውን አመታት አስመልክቶ እንዲህ ብሎ ነበር፡- “በብዕር ህይወቴ ውስጥ በየዘመኑ መንግሥቶች የሥነ ልቡና ተፅእኖዎች፣ መንገላታቶች፣ የደሞዝ መቁረጫዎች፣ የዝውውር መቀጫዎች፣ ዛቻዎች፣ ዘለፋዎች፣ እስሮች ወዘተ (በግድ የለመድኳቸው ቢሆኑም) ደርሰውብኛል፡፡ ሌሎች የዓለም ደራሲያን በተለይ የብዕር ታላላቆቼ በህይወታቸው የከፈሉትን ፅዋ ስመለከተው ግን እፅናናለሁ፡፡

የኛ “ዙሩ በዛ” እንጂ በስልጣን ሰይፍና በጥበብ መካከል ያለ ትግል ጥንትም የነበረ፣ ዛሬም ያለ ወደፊትም የሚኖር አሳዛኝ እውነታ ይመስለኛል” ከአንድ ሰው አማካይ እድሜ በላይ በቆየው የፀጋዬ ጥበባዊ ህይወት ወስጥ ሽልማት፣ ሹመት፣ ሽረት፣ እስራትና ከሥራ መታገድ ተራ በተራ ተፈራርቀውበታል፡፡ ይሁን እንጂ ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው እንደታማኝ ጓደኛው ከፀጋዬ ሳይለየው የቆየው ግን የሳንሱር መሰናክል ነበር፡፡ ሳንሱር ነፃ አስተሳሰብን በማገድ የደራሲን ብዕር የማዶልዶም ተፈጥሮ ያለው ቢሆንም፤ የፀጋዬ ብርቱ የፈጠራ ኃይልን ግን ለዚህ የፅልመት አሰራር ሳይንበረከክ በርካታ ተውኔቶችን ለማፍራት ችሏል፡፡ ሳንሱር ፀጋዬ ጥበባዊ ሥራዎቹን በመድረክ እንዳያቀርብ እያፈነ እና እየቀነጣጠበ ቢያስቀርበትም፤ ተስፋ አስቆርጦ ብዕሩን እንዲጥል ስላላደረገው የአፈናው ዓላማ ተሳክቶለታል ለማለት አይቻልም፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 26 January 2013 14:46

የታገል ሰይፉ ግጥሞች!

ሰለሃገራችን ግጥም ስናነሳ ታገል ሰይፉ ፈጽሞ የማይረሳ ተዋናይ ነው፡፡እንደ ታገል በአስራስድስት አመቱ ብዕር ጨብጦ ግጥም የጻፈና በዚያ እድሜው ሰዎችን ያስደመመ ሌላ ማንም ታዳጊ አልነበረም፡፡ በተለይ “ፍቅር” በሚል ርዕስ የጻፈው መጽሃፉ፣ በዚያ እድሜ እንደዚያ ይታሰባል ለማለት የሚቸግር ነበር፡፡ ከዚያም በኋላ “ቀፎውን አትንኩት” በሚል ጥራዙ ጥሩ-ጥሩ ሃሳቦችን አንስቷል፤ሌላውና የተለየ ስራው “ኢህአዴግ ውስጥ የገባ አውሬ” (መካከለኛ ልብወለድ) ነው፡፡ ካሁኑ አዲስ መጽሃፍ ሌላ “የሰዶም ፍጻሜ”፣“የሃምሳ አለቃ ገብሩ” እና “የእድሜ ጅረት” የተሰኙ መጻህፍትን፣ እንዲሁም ምስል የለበሱ ሁለት የሲዲ ግጥሞችን አሳትሞ ለህዝብ አድርባል፡፡ ይሁንና ታገል በቴሌቪዥን በሚያቀርባቸው ምስል-ለበስ ግጥሞቹ ቢወደድም፣የግጥም ውበት፣ ጥልቀትና ግርማውን ተነጥቆ ነበር፡፡በዚህም እውነተኛ የግጥም ወዳጆቹን ቅር ያሰኘ ይመስለኛል፤እኔም የወዳጅነቴን “ወድቀሃል” ብዬ ነግሬው ነበር፡፡

ደግነቱ ታገል በፈጠራ ስራዎቹ ላይ የሚሰጠውን አስተያየት ለመስማት ከብዙዎቻችን የተሻለ ልብ አለው፡፡ይህ ደስ የሚል ልምምዱ ነው፡፡ታገል ወርዶ ያልቀረውና መልሶ መሰላሉን የጨበጠው ለዚህ ይመስለኛል፡፡አንድ ጊዜ በግጥም ምክንያት “ተበላሽተሃል” ብዬው የመረረ ንግግር ተነጋገርን፣ባንድ ታክሲ መምጣታችንን አስታውሳለሁ፡፡ያለመኮራረፋችን የታገልን ከኔ የተሻለ ታጋሽነትና ሂስ ተቀባይነት ያሳየኝ ይመስለኛል፡፡ የታገልን አዲስና ዛሬ የምቃኘውን መጽሃፍ እንዳነብበው ታገል ቀደም ብሎ ቢነግረኝም ጊዜ በማጣት ሳላነብበው ለገበያ በመቅረቡ አዝኛለሁ፤ምክንያቱም ብዙ ጊዜ ግጥማችንን ወይም ጽሁፋችንን የሚያይልን ሰው ከአልተፈለጉ ስህተቶች ሊያድነን ይችላል፤እኔ በዚህ አምናለሁ፤መጽሃፍት መግቢያ ላይ እንደዋዛ ስማቸውን የምንጽፋቸው ሰዎች ከስንት ጉድ ያዳኑን እንደሆኑ ልባችን ያውቀዋል፡፡እኔም ያዳኑኝን አልረሳም፡፡የሚያሳስቱም እንዳሉ-ሁሉ ማለቴ ነው፡፡የታገል አዲስ መጽሐፍ ርዕሱ “በሚመጣው ሰንበት” የሚል ነው፡፡

እውነት ለመናገር ይህ መጽሃፍ በታገል የግጥም ሥራዎች ታሪክ ውስጥ በውበትና በሃሳብ ልቀት ከፍ ያለ ነው፡፡ጭብጦቹ ወደ ትውልድ ያነጣጠሩ፣የሃገር ድምጽና መልክ የጠቀለሉ፤ናቸው፡፡ከዚህ ቀደምም በአብዛኛው የማይታማበት የቃላት አጠቃቀምም የተሻለ ሆኖ ቀርቧል፡፤ዜማና ምት ላይ ታገል ሁሌም አሪፍ ነው፡፡ ለምሳሌ “ልጄን ላንተ ካራ” የሚለው ግጥሙ የዘመናችን በሽታ ማሳያ ነው፡፡ትንሽ እንይ፡- “የተማረ ይግደለኝ”- የተባለ ለታ የተጣባው ደዌ -የገባው በሽታ አጎነቆለና-በኔ ላይ ግርሻቱ ልጄን ትገድሉት ዘንድ-ፈቀድኩ እኔ አባቱ …………….

ከዕውቀት የጎደለ-ከጥበብ የሌለ ህይወት አልባ ቃላት እያንበለበለ ላይበስል ያፈራ-ላያድግ የበቀለ የምናቡን ድርቀት-የቋንቋውን ኦና ያንበለብልና-ያንበለብልና…. ፍሬ የለሽ ክምር-ውሃ አልባ ደመና ላይበላ እንደራበው-ላይጠጣ እንደጠማው ማሲንቆን ሳያውቀው-በገናን ሳይሰማው በሞዛርት ፒያኖ-በነቾፐን ፍሉት ግድ የለም ግደሉት-ግድ የለም ግደሉት “መለያየት ሞት ነው!” ይባል የነበረ ፍቺው በዚህ ዘመን -እየተቀየረ ሰው ለንደን በኖረ-ሰው ዲሲ በኖረ መለያየት ህይወት መሆን ከጀመረ ግደሉልኝ ኧረ የምን ተባ ፈራ ፈቅጄ በሰጠሁ- ልጄን ላንተ ካራ ማነው የሚቆጣ-ማነው ሚነደው የተስፋውን ግልገል ሳይሰባ ብታርደው አሁን የለምና! ተደፈርን የሚል-ኢትዮጵያዊ ጀግና…. እያለ ይቀጥላል፡፡ ስለማንነት ውድቀት መረር ያለ ሂስ ነው፡፡ራሳችንን ትተን ሌሎችን የመሆን አባዜ ተጠናውቶን ከርታታ ሆነናል፤የባህር ላይ ኩበት ነው የሚል!! ያ ብቻ አይደለም፣ በዚህ ሁሉ ስካር ውስጥ መንገድ ተሳስተሃል የሚል መሪም የለም፡፡ማንነቱን እየጣለ ነው የሚል ሽሙጥና ግልጽ ቁጭት፣ሽንቆጣም ነው፡፡ልምጩ ልቤን ነክቶታል፤ገርፎታልም፡፡…ገጣሚ መሪ ነው፤አስተማሪ ሳይሆን ጎልጉሎ የሚያሳይ ባለ ንስር ዓይን፡፡

ታገል የሚብከነከነው ቋንቋችን ሲንኳሰስ ነው፡፡በተጨማሪም ፈረንጅ ሃገር መሄድ ብርቅ መሆኑን ያሽሟጥጣል፡፡ዶክተር በድሉ ደግሞ ፈረንጅ ሃገር ሆኖ የሃገር ሰቀቀንን እንዲህ ገልፆታል- ”አንተንስ እኔን አያርግህ” በሚለው ግጥሙ፡- እኔም አውሮፓ ላይ ፣ በሲጋራ ጢስ ውስጥ ፣በማኪያቶ አረፋ መሽቶ የማይነጋ ቀን፣ዕድሜዬን ስገፋ፣ በሰለጠነ ዓለም”፣እትልቅ ከተማ በሰው ተከብቤ፡- ብቸኝነት ሰብሮኝ፣ፍቅርን ተርቤ፣ አንተን ባረገኝ እላለሁ፤ የታገል ግጥሞች ከወትሮው የተለየ ውበትና ጥንካሬ አይቼባቸዋለሁ፡፡ከአዳዲስ ግጥሞቹ “አመሰግናለሁ”ን እናንብብ፡- እንደ አቦል በረካው-እንደቡናው ስባት መፋጀትሽ መሃል-ላየሁት ደም ግባት አመሰግናለሁ! እንደግዚሃር ባርኮት-እንዳምላክ ስጦታ በማስጨነቅሽ ውስጥ -ለቀመስኩት ደስታ አመሰግናለሁ! እንደ ጨረቃዋ ድምቀታዊ ጉልበት በጨለማሽ መሐል -ለተቸርኩት ውበት አመሰግናለሁ እንደ መተሬ ጣም እንደ ኮሶ ቃና መራርነትሽ ውስጥ ላገኘሁት ጤና አመሰግናለሁ! ስለፍቅር የሚያወራ የሚመስለው ግጥም ከመራራ መድሃኒት ውስጥ የሚገኘውን ፈውስ ያሳያል፡፡

ደምግባት፣ደስታ፣ውበት፣ጤና ተቃራኒ ከሚመስሉ ተግዳሮቶች ውስጥ መወለዳቸውንና አንጻራዊነትን ያጎላል-ታገል፡፡ ህይወት የምትበርባቸው ክንፎች ሚዛንም ነው - ይሄ!! “ኮተታም ገጣሚ” አንዱ የታገልን አቅም የሚያሳይ ትልቅ ግጥም ነው፡፡እንደ እሳተ ገሞራ እሳት የሚተፉ ሃይለኛ ቃላት ተጠቅሞ፣ያሽሟጥጣል፡፡ግጥሙን ከባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገብረ መድህን “እከካም ተማሪ”የቀጠለ እና የተቃረነ የዘመን ፍተሻ ብሎታል-ገጣሚው፡፡ የተወሰኑ ስንኞች ልቀንጭብ፡- …ፉጨት የተራቡ-ጭብጨባ የተጠሙ “ብራቮ” እንደ ዘኬ የሚለቃቅሙ ሲባል እንደሰሙ-“ኪነት የህዝብ ናት!” እንዳዘን ቤት ንፍሮ ማንም የሚዘግናት ከሊቅ እስከ ደቂቅ እንደማህበር ፅዋ -እንደ ፀበል ፀዲቅ ሁሉ ሲዳረሳት -ሁሉ ሲቃመሳት ካልተጣደበት ድስት -ካልተያያዘ እሳት እየገነፈለ እንከን አየሁ አለ ቅኔውን ሲያሰማኝ -እዬዬውን ሲኛኝ ያ!አባቱን ኮናኝ -አምላኩን አራሚ ቀኑን አጨላሚ እሱ ኖሯል ለካ -ባንተ ቀን ለምላሚ ባንተ መድረክ ቋሚ ያ!ጭንጋፍ ገጣሚ -ኮተታም ገጣሚ… እያለ ይቀጥላል፡፡…ይሁንና የግጥሙ ርዕስና ሃሳቡ ተጋጭቷል፡፡”ኮተታም ገጣሚ” ብሎ ሃያሲውንም አስገብቷል፡፡…ግጥሙ ገጣሚውን ብቻ ሳይሆን ሃያሲውንም ይተቻል!! የታገል መድበል ሸጋ ሸጋ ግጥሞችን ይዟል ብንልም የቀለደባቸውም እንዳሉ ሳይዘነጋ ነው፡፡ “ፋሲካን ለማርታ” በሚለው ግጥሙ ከላይ እስከ ታች በሳድስ፣ሳድስም ሆኖ በአንድ “ሽ” ጀምሮ ጨርሶታል፡፡ ሌሎችም ችግሮች አሉት፡፡ ”ፍቅር ለኔና አንቺ” የሚለውን ግጥሙን በከፊል ጋብዤ ለዛሬ ቅኝቴን ልቋጭ፡፡ …ካለስዋ አይበራም ስል -የዘመኔ ፅልመት የቀኔ ጨለማው፣ አውቃለሁ ውሸት ነው -ፍሬ ቢስ ገለባ ለሰማኝ በሩቁ፣ እስከዛሬ ድረስ -የሷ አይነት አበባ በቅሎ አለማወቁ፣ ግና ይሄ ውሸት -ይህ ውዳሴ ከንቱ አገር ያቀለለው፣ በኔ እና እሷ መሐል -ዕውነት መሆኑ ነው ፍቅር የሚባለው፡፡ …አይመችም?…ፍቅር በሁለት ሰዎች መካከል የሚታይ ተዐምር ነው፡፡ባገር ሰላም ለብቻ ማበድ መሰለኝ!! ለሌላው ሰው ቀልድ፣ለተዋናዮቹ እልም ያለ ውበት፡፡…ፍቅር ለማረጋገጫ የማንንም ፊርማ አይጠይቅም፤አይፈልግም እያለ ነው፣የሁለት ሰዎች ቋንቋ ነው-ለሌሎች አይገባም፡፡ፍቅር ስንል ግን ውሲባዊ ቅብጠትን አይደለም፤የነፍስን ዜማና-ዝማሬ ነው፡፡…

Published in ጥበብ
Saturday, 26 January 2013 14:42

አቡቲ!

እትዬ ደስታ፣ ድህነት በበረታ ክንዱ ደቋቁሶ፣ከእጅ ወደ አፍ እንኳን ለማለት በማያስችል የኑሮ ወለል ያስቀመጣቸው የኑሮ ታጋይ ናቸው፡፡ ደስታ የሚል ስም ይኑራቸው እንጂ፣ በህይወታቸው ውስጥ ደስታን ያገኙበት ቀን ትዝ አይላቸውም፡፡ ኑሯቸውን አስተውሎ ለተመለከተ ሰው፣ ስማቸው በህይወታቸው ላይ የተሰነዘረ “ምፀት” ነው የሚመስለው፡፡ ባል የላቸውም፣ባላቸውን ከፈቱ ስምንት አመታቸው፡፡ አሁን ግን ድህነት ባላቸው ሆኗል፡፡ አብሯቸው ይውላል፣ አብሯቸው ያድራል፣ አብሯቸው ይኖራል … ከልጅ ልጃቸው ከአቡቲ ጋር ነው የሚኖሩት፡፡ የአቡቲ እናት አረብ ሀገር ከሄደች አንድ ወሯ፡፡ “እዚህ በባዶ ቤት በረሃብ ከምናልቅ እዛ ሄጄ ልስራ” ብላ ነው የሄደችው፡፡ ይኸው አንድ ወር ሆኗት፣መድረሷን ደውላ መልዕክት ከነገረቻቸው በኋላ፣ድምጿም የለ፡፡ ለእትዬ ደስታ የልጃቸው ድምፅ መጥፋት በኑሯቸው ላይ የተደመረ እራስ ምታት ሆነባቸው፡፡ አንዳንዴ ኑሮን ልቻልህ ሲሉት የማይቻል ይሆንባቸውና በእንባ ሊያቀሉት ይሞክራሉ፡፡

“በአራት ግድግዳ” ተከልለው ስቅስቅ ብለው ያለቅሳሉ፡፡ “ምነው … ምነው አልችለው ኑሮ ሰጠኸኝ?!” ብለው አምላካቸውን ያማርሩታል፡፡ ግን ዛሬም ከትናንት ያልተለየ “ህይወት” እየገፉ አሉ፡፡ በተለይ የዛሬው ጭንቀታቸው ይባስ፡፡ አቡቲ ከትምህርት ቤት መምጫው ሰዓት ደርሷል፡፡ እቤት ውስጥ የሚቀመስ ነገር የለም፡፡ ገና ምግብ ሊያዘጋጁ ነው፡፡ አቡቲ፣ ለንቋሣ ቢጤ ነው፤ ረሃብ የሚችል አቅም የለውም፡፡ ቁርስ እንኳን እንደነገሩ ቀምሶ ነው የሄደው፡፡ “ተሰቃይ ብሎ የፈጠረው ልጅ” ለራሳቸው አጉተመተሙ፣ እትዬ ደስታ፡፡ ከሳቸው ህመም በላይ፣ የሚያማቸው የእሱ ስቃይ ነው፡፡ ባልጠና አቅሙ ላይ የሚያርፍበት የድህነት በትር ነው የሚያቆስላቸው፡፡ አቡቲ መጣ፡፡ እትዬ ደስታ ምሳ ለማዘጋጀት ደፍ ደፍ እያሉ ነው፡፡ “እማ … ምሳ!” አለ፣ አቡቲ - እንደፈሩት! አጠያየቁ ውስጥ የረሃቡ ጥልቀት ታያቸው፡፡ “የለም” ሊሉት አልወደዱም … “የኔ ጌታ፣ አሁን አደርስልሃለሁ --- ትንሽ ጠብቀኝ” “እንዴ እማዬ …

ጠዋት እኮ በላሁ አይባልም …” እንደማልቀስ ቃጣው፡፡ “አዎ፣ አዎ አቡቲዬ … በቃ አሁን ትኩስ ገንፎ አደርስልሃለሁ፣ ገና ከወፍጮ ቤት ስለመጣሁ እኮ ነው ያልደረሰልህ…” አቡቲ በማኩረፍ ዝም አለ፡፡ እትዬ ደስታ ከሰሉን ለማቀጣጠል ቢሞክሩም አልቀጣጠል ብሎ አስቸገራቸው፡፡ “ገና እሳቱ እስኪቀጣጠል፣ ውሃው እስከሚፈላ፣ …? እንዴ!?” አለ አቡቲ፡፡ አልቅስ አልቅስ አለው፡ እንባው ኩልል ብሎ ወረደ፡፡ እትዬ ደስታ ጨነቃቸው፡ “አሁን ይደርሳል እኮ የኔ ጌታ …” እሳቸውም አቅፈውት ማልቀስ አማራቸው፡፡ ቢቸግራቸው አንድ መላ አመጡ፡፡ “አቡትዬ?... እስቲ እዚህ እነ ሚኪያስ ቤት ሂድ፡ እሱም ከትምህርት ቤት ስለሚመጣ እንጫወት ብለህ ብትሄድ ማቆያ ታገኝ ይሆናል” ቢጨንቃቸው ነው፡፡ እሳቸው ሺ ጊዜ ቢራቡ የሰው ፊት ለማየት እንደማይፈቅዱ ያውቁታል፡፡ አቡቲ ለአፍታ ዝም ብሎ ቆይቶ ተነስቶ ወጣ፡፡ እትዬ ደስታ አቡቲን ከኋላው በትካዜ አስተዋሉት፡፡ እንባቸው ግጥም ብሎ ለመውረድ ዳዳው … *** አቡቲ ከቤት እንደወጣ፣ ሚኪያስ ከትምህርት ቤት መጥቶ ወደቤት ሊገባ ሲል አየው፡፡ “ሚኪያስ?” ጠራው፡፡ “…እ…የትናንቷ ኳስ አለች?” ሆን ብሎ ነው፡፡ በዚህ ሰዓት ኳስ የመጫወት አቅም እንደሌለው አጥቶት አይደለም፡፡ “የለችም” ሚኪያስ መለሰለት፡፡ ሚኪያስ ትቶት ወደ ቤት ለመግባት ተጣድፏል፡፡ “ትናንት እኮ ኮባው ሥር ነበረች… እኔ ፈልጋታለሁ በቃ” ሚኪያስ ወደ ውስጥ ሲገባ፣ ተከትሎት ገባ፡፡

ወደ ውስጥ እንደገቡ፣ የሚኪያስ ውሻ ሚኪያስን መላፋት ጀመረ፡፡ አቡቲ ውሻውን በመራቅ ሰበብ እየተጣደፈ ወደ ሳሎኑ ገባ፡፡ ቤቱ ውስጥ የሚኪያስ እናት ነበረች፡፡ ቆጣ ባለ ድምፅ “ምንድነው አንተ!?” “አይ…ውሻው…እንዳይነክሰኝ…” …ሚኪያስ ገባ፡፡ አቡቲ ለመቀመጥ ፈለገ፡፡ ልቡ አልደፈረም፡፡ ወጣ ብሎ የቤቱን በር ተደግፎ ቆመ፡፡ የሚኪያስ እናት ድምጿ እንዳይሰማ ዝቅ አድርጋ፤ “ለምን ይዘኸው መጣህ አንተ!?” “ኧረ … እራሱ ነው ተከትሎኝ የመጣው!” “በል አሁን ትንሽ አጫውተህ ሸኘው ወደዛ” “እ…እ…ምሳስ?! “ምሳ!?...ምሳውን እንድቀልብልህ ነው እንዴ ይዘህብኝ የመጣኸው?... ሲሄድ ይሰጥሃል፣ ለማንም የማበላው እህል አልተረፈኝም” ሚኪያስ እያጉተመተመ ወጣ፡፡ አቡቲ የኳሱን ጉዳይ ትቶታል (ሆን ብሎ ረስቶታል) … ረሃቡ ነው ሃሳብ የሆነበት፡፡ የሆዱ መሞርሞር ይበልጥ እየተሰማው ሄደ፡፡ ምግብ የሚያገኝበትን መንገድ ለማሰብ ሞከረ፡፡

“ሚኪ…ቴሌቪዥን እንይ?” “እቴቴ እሺ አትልም፣ የጥናት ሰዓቴ ደርሷል” አቡቲ የሚፈጥረው መላ አጣ፡፡ የረሃብ ስሜቱ እየጠናበት ሄደ፡፡ ሰውነቱን የድካም ስሜት ተሰማው፡“ሚኪያስ?” የሚኪያስ እናት ተጣራች፡፡ “አቤት” “አንድ ጊዜ ና” ሚኪያስ ወደ ቤት ገባ፡፡ አቢቲ ከኋላ ከኋላው እያየው ባለበት ቆየ፡፡ ተከትሎት ለመግባት ቢያምረውም፣ አልደፈረም፡፡ “እንካ ይሄን ቶሎ ጐረስ ጐረስ አድርገህ ውጣ” … ሚኪያስ ተቀብሎ በፍጥነት መብላት ጀመረ፡፡ “ምኑ ቀላዋጭ ነው እቴ…” እያጉተመተመች ወደ ጓዳ ገብታ ቂጣ ይዛ ወጣች፡፡ “አቡቲ?” “አቤት…” አቡቲ በፍጥነት መጣ፡፡ እጇ ላይ ያለውን ቂጣ ሲያይ ሆዱ ተገለባበጠ፡፡ ምራቁ አፉን ሊሞላው ሆነ፡፡ “አቤት” አለ በድጋሚ አይኑን ቂጣው ላይ እንደተከለ፡፡ “እንካ እስቲ ይቺን ቂጣ ለውሻው ስጥልኝ … ቡቺ … ቡቺ … የት ሄዶ ነው አሁን እዚህ አልነበር?” “ወደ … ጓሮ ሄዶ ነው” አለ አቡቲ፣ ተስፋ ባጣ ድምፅ፡፡ “እንካ ጠርተህ ስጠው” ተቀበላት፡፡ ወደ ቤት ገባች፡፡ ጥሪዋን ቀድሞ የሰማው ውሻ ጭራውን እየቆላ መጣ፡፡ ትንሽ ቆንጥሮ ጣለለት፡፡ ቂጣውን አስተውሎ አየው፡፡ እየፈራ ወደ ቤቱ ውስጥ ዘወር ብሎ ተመለከተ፡፡ ሚኪያስም እናቱም አይታዩም፡፡ ረሃቡን ማዳመጥ ጀመረ፡፡ በቆመበት ቂጣውን በልቶ ረሃቡን ለማስታገስ ፈለገ፡፡ ይዞት ቢሄድ እንደሚሻል አሰበ፡፡ ሮጦ ከግቢው መውጣት አማረው፡፡ ከሮጠ ደግሞ ውሻው … ለውሻው በትንሹ ቆንጥሮ ራቅ አድርጐ ጣለለት፡፡ ከውሻው ጀርባ አድርጐ ራመድ፣ ራመድ እያለ ወደ መውጫው በር ተጣደፈ፡፡ ጥቂት እርምጃዎች እንደተራመደ ከኋላው የሚኪያስ ድምፅ ተሰማው፤ “አንተ!!...” ወደ ኋላው አላየም፡፡

ደመነፍሱ ያቀበለው መልስ “እሩጥ” የሚል ሆነ፡፡ ወደ በሩ ባለው ሀይል ሮጠ፡፡ “ጃስ … ጃስ … ቡቺ…” ሚኪያስ ከኋላው ይጮሃል፡፡ አቡቲ በሩ ጋ ለመድረስ ጥቂት እርምጃዎች ቀረው፡፡ በሚኪያስ “ጃስ” ትእዛዝ የተላለፈለት ውሻ፣ወደ አቡቲ እየሮጠ ነው፡፡ አቡቲ በሩ ጋ ደረሰ፡፡ በሩን በፍጥነት ከፈተው፡፡ በዛው ቅፅበት ውሻው ዘሎ እላዩ ላይ ወጣበት፡፡ አቡቲ የከፈተው በር ላይ ወደቀ፡፡ አጥብቆ የያዛት ቂጣ ከእጁ አመለጠች፡፡ ውሻውን ለመከላከል መፈራገጥ ጀመረ፡፡ ውሻው እጁን፣ እግሩን፣ ታፋው ሥር … ነካከሰው፡፡ አቢቲ ጮኸ! ጮኸ! “እማዬ… እማዬ …” አለ በጩኸት እያለቀሰ፡፡ እትዬ ደስታ፣ “ልጄን … ልጄን …” እያሉ ሲበሩ መጡ፡፡ የሚኪያስ እናት ውሻውን ለማባረር እየሞከረች ደረሱ፡፡ አቡቲ መሬት ላይ እንዳለ ያለቅሳል፡፡ እትዬ ደስታ ወዲያው ነገሩ ገባቸው፡፡ እንባቸው በአይናቸው ግጥም አለ፡፡ “እኔን … እኔን … ልጄን…” አቡቲን ይዘው አነሱት፡፡ አቡቲ እንባ በጋረዳቸው አይኖቹ በአፈር የተለወሰችውን ቂጣ አያት …፡፡ የሚኪያስ ፊት እንደ መሳቅ ብሏል፡፡ የሚኪያስ እናት ፊቷ ላይ ምንም አይነበብም፣ እትዬ ደስታና አቡቲ እስኪወጡ የምትጠብቅ ትመስላለች፡፡ እትዬ ደስታ አፈር የለበሰውን የአቡቲን ልብስ አራገፉለት፡፡ ውሻ የነከሰው እጁን ሲያዩ እንባቸው ከቁጥጥራቸው ውጪ ሆኖ ተዘረገፈ፡፡ “እኔ እኮ ተው እዚህ ቤት አትግባ፣ ውሻቹ ይነክሱሃል ብዬ ደጋግሜ ነገርከህ፣ አስለማ አልከኝ…” አሉ እትዬ ደስታ አቡቲን ይዘው እየወጡ፡፡ “ውሾቹ ይነክሱሃል” ነው ያሉት እትዬ ደስታ፡፡ አይ ድህነት፣ የማያደርገው የለም መቼስ ይሄው እትዬ ደስታን እንኳ “ባለቅኔ” አደረጋቸው፡፡ አንድ ውሻ ባለበት ግቢ፣ “…ውሾቹ ይነክሱሃል ብዬ ደጋግሜ ነገርኩህ…” ብለው ቅኔ ዘረፉ፡፡ እትዬ ደስታና አቡቲ ወጡ፡፡ የሚኪያስ እናት በሩን ከኋላቸው ዘጋች፤ የኑሮ ደረጃቸው “ድንበር” የሆነውን በር!!

Published in ልብ-ወለድ

ትንሽ ጥያቄ አለኝ - ለፕሮፌሰር መሥፍን ወልደማርያም እዚህ ላይ ፕሮፌሰር አዲስ አጣርተው ያገኙት መረጃ ምንድን ነው? ምንአልባት ወደፊት በሚያሳትሙት መፅሐፍ ወይም መጣጥፍ ይነግሩን ይሆናል እንጂ አሁን ምንም ከቀድሞው የተለየ የነገሩን ያለ ነገር የለም፡፡ በቅርቡ ለንባብ ከበቁ መፃህፍት መካከል የፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም “መክሸፍ እንደኢትዮጵያ ታሪክ” አንዱ ነው፡፡ በ238 ገፆች ተቀንብቦና በብዙ መረጃዎች ተዋዝቶ እንዲሁም በከፍተኛ የሀገርና የወገን ተቆርቋሪነት ስሜት የቀረበው መፅሐፍ፤ ጥልቅ የምርምር ውጤት ነው፡፡ ነፃና ግልፅ አስተሳሰብ የተንፀባረቀበትና ለትውልድ የእውነትን መንገድ ለማስተማር ፈር ቀዳጅ ነው ማለትም ይቻላል፡፡ሆኖም ግን መፅሐፉን በማነብበት ወቅት አንዳንድ ጉዳዮች ግልፅ አልሆኑልኝም፡፡ ለምሣሌ የመጀመሪያው ስለ አፄ ቴዎድሮስ ውድቀት የቀረበው ምክንያት ነው፡፡

“አፄ ቴዎድሮስ የዕውቀት ጥበብን በኢትዮጵያ ለማስገባት ከፍተኛ ምኞት የነበራቸው ቢሆንም ለእውቀት መስፋፋት በግድ አስፈላጊ የሆነውን ነፃነትን ለኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ለማጐናፀፍ አልቻሉም፤ አላማቸውም የከሸፈውም በዚህ ምክንያት ነው ይላሉ፡፡ (በገፅ 14- 15) ቀጥለውም:- መጀመሪያ ማኅበረሰቡን በነፃነት አእምሮውን ማፍታት ሁለተኛ ደግሞ ማኅበረሰባዊ ሕመም የሆነውን የሥልጣን ምኞት ሥልጣንን በማጋራት መፈወስ ያስፈልግ ነበር ይላሉ፡፡ እዚያ ላይ ማብራሪያ የሚያስፈልገው ማህበረሰቡን በነፃነት አእምሮውን ማፍታት ሲባል ምን ማለት ነው? እንዴት ነበር ንጉሠ ነገሥቱ የዘመናቸውን ማኅበረሰብ በነፃነት አእምሮውን ማፍታት የሚችሉበት ሥልት የሚለው ሰፋ ያለ ማብራሪያ ቢሰጥበት ግልፅ ይሆን ነበር፡፡ አፄ ቴዎድሮስ ለሰባ ዓመታት ገደማ በእርስ በርስ ሽኩቻ ተዳክማ ለነበረችው እናት ኢትዮጵያ የደረሱላት ጀግና መሆናቸው ገሀድ ሀቅ ነው፡፡ ደጃች ጐሹን፣ ራስ ዓሊን፣ ደጃች ውቤን፣ ንጉሥ ኃይለመለኮትንና ሌሎችን የጊዜው ኃይለኞችን ተራ በተራ አንበርክከው ነው የማዕከላዊ መንግስት ምሥረታ ረዥም ጉዞ የጀመሩት፡፡ መይሣው ካሣ ተቀናቃኞቻቸውን ቢያሸንፉም በመጀመሪያ የአካባቢውን አስተዳደር ለአካባቢው ተወላጆች ሰጥተው ሠላምና ፀጥታ እንዲሰፍን መክረው ነው ወደ ጐንደር የተመለሱት፡፡ ጐጃምን መጀመሪያ የሰጡት ለአካባቢው ባላባት ለደጃች ተድላ ጓሉ ነው፡፡

ሆኖም ግን ተድላ ጓሉ ወሎ እያለ አፄ ቴዎድሮስ ወደ ሸዋ ሲዘምቱ ገና ለገና ቴዎድሮስ ይሸነፋል ብሎ በማመኑ የሸፈተና እስከ ቴዎድሮስ ፍፃሜ ዘመን ድረስ ጐጃም ሲያሳምፅና ሲያውክ የነበረ ነው፡፡ በሸዋ ከኃይለ መለኮት ጋር ሲዋጉ ንጉሥ ኃይለ መለኮት በህመም ምክንያት ቢሞቱም ቀሪው የሸዋ ጦር የቴዎድሮስን መብረቃዊ ጥቃትና የውጊያ በትሩን ባለመቋቋሙ ሲሸነፍ፣ አፄ ቴዎድሮስ ለሸዋ መርድ አዝማች ኃይሌን ቢሾሙም በአቶ ሥራህ ብዙ ከሳሽነት ከስልጣን ተሽረው አቶ በዛብህ ተተክተዋል፡፡ አቶ በዛብህም በኋላ ከድተዋል፡፡ ዋግሹም ገብረመድህን ቴዎድሮስ በመጀመሪያ ሾመዋቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሸፍተው ተያዙና ደብረ ዘቢጥ ላይ በስቅላት ተቀጡ፡፡ ይህ የሚያሳየን በዘመኑ የነበሩትን ታላላቅ ግዛቶች በአካባቢው ተወላጆች እንዲመሩ ማድረጋቸውን ነው፡፡ ይህ ሥልጣን ማካፈል የማይሆነው አፄ ቴዎድሮስ እነዚህን ተሿሚዎች ንጉሥ ባለማለታቸው ይሆን? የኅብረተሰቡን ሠላም በተመለከተ ቴዎድሮስ በወሰዷቸው ተከታታይ የፍርድና የቅጣት መንገዶች፣ ገበሬው እንዲያርስና ነጋዴው እንዲነግድ እንዲሁም ሁሉም በየሞያው እንዲተዳደር ጥረት አድርገዋል፡፡ ቴዎድሮስ ነገሡና እባብ ጠፋ በጐዳና ወንበዴም ሄደ ምነና ገበያችንም አለ ፈሰስ ጋለሞታችንም አለች ፈርነስ… ተብሎ በዘመኑ ተገጥሞላቸዋል፡፡ አቶ የታሪክ ምሁሩ ተክለፃዲቅ መኩሪያ “አራሽ እረስ፣ ነጋዴም ነግድ፣ ሽፍታም ወንበዴም ተው ግባ ይሻልሃል፡፡ ተይዘህ ቀደም የበደልካቸው ቋንዣ የቆረጥህ፣ ነፍስ የገደልክ ምሬሃለው፡ ፡ በዱር በገደል ያለህ ግባ፤ አልገባም ብለህ አዋጁን ያለፍህ (የሻርህ) ግን ለአባልህ እዘንለት” ማለታቸውን ጽፈዋል፡፡

አፄ ቴዎድሮስ በገዛ ሀገራቸውና አፈራቸው ብረት አቅልጠው መድፍ ከመስራታቸው በተጨማሪ የባሪያ አገዛዝ የሻሩ፤ የካህናትን ቁጥር የወሰኑ፤ የመሬት ባለቤትነት ከመሣፍንቱ፣ ከመኳንንቱና ከቤተክርስቲያን እጅ አውጥተው በመንግሥት እጅ እንዲሆን ያደረጉ፤ በአንዳንዶች ፀሐፊዎች ደግሞ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የመሬትን ጥያቄ ለመፍታት የሞከሩ መሪ ናቸው እስከመባል ደርሰዋል፡፡ በጋፋትና በቆራጣ የዕድ-ጥበብ ሙያዎች እንዲያብቡ የደከሙ፤ የዘመናዊ ጦር ጥንሰሳ መሠረት የጣሉ፤ በተለይም የእንግሊዞችን፣ የፈረንሳዮችን፣ የቱርክን፣ የግብፆችን እና ሌሎች የአውሮፓ አገሮችን ከበባ ለመስበር ጥረት ያደረጉ፤ በታሪክ አንፀባራቂ ጀብዱ የፈፀሙ ታላቅ የኢትዮጵያ መሪ ናቸው፡፡ ውድቀታቸውን በተመለከተ ሩቢሰን የተባለው ፀሐፊ፣ የቴዎድሮስን የግል ሰብዕና፣ ፖለቲካ፣ የውስጥና የውጭ ግፊቶችን ለአፄ ቴዎድሮስ መውደቅ እንደ ምክንያት ጠቅሷል፡፡ ዶ/ር ባላንክ “ቱርክ በእንግሊዝና በፈረንሣይ እየተረዳች አገሬን ለመውጋት አስባ በሱዳን ላይ የባቡር ሐዲድ በመሥራት ላይ መሆኗን የሚገልፅ መልዕክት የያዘ ደብዳቤ ከኢየሩሳሌም ደረሰኝ” ሲል ገልጿል፡፡ ተክለፃዲቅ መኩሪያ ደግሞ “በዚያን ጊዜ የአፄ ቴዎድሮስ አንገብጋቢ ጥያቄ ከመሀመድ ዓሊ ጀምሮ የግብፅ መንግስት የሚያስተዳድራቸውንና በሰናፒ ወሰን ያሉትን ቀበሌዎች እንዲሁም በጐሰን፣ መንሰን፣ ሐልሐሃልንና ሐባብን ከ1517 ጀምሮ የቱርክ መንግስት የያዛቸውን የምፅዋን ወደብና አካባቢውን ወደ ኢትዮጵያ ለማስመለስ ነው፡፡ ሆኖም ግን ከአቡነ ቄርሎስና ከአቡነ ሲላማ የጠበቁት ተቃራኒ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ እንግሊዞች 10 ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ ያደረጉበትን ዘመቻ በመምራትና በነደጃች ካሣና በሌሎችም ኢትዮጵያውያን ትብብር ወደ መቅደላ መጥተው ኋላቀር መሣሪያ የታጠቀውን የኢትዮጵያን ጦር ለማጥቃት እንደቻሉና አፄ ቴዎድሮስን ይዞ ላመጣ ወይም ለገደለ 50ሺ ጠገራ ብር የእንግሊዝ መንግስት ጉርሻ እንደሚሰጥ ቃል መግባቱን አለቃ ዘነበ ገልፀዋል፡፡ ይህ የውጭና የውስጥ ከበባ ነው ውድቀታቸውን ያፋጠነው ይላሉ፡፡ እዚህ ላይ ሌላ ጥያቄ ማንሳት ይቻላል፡፡

በጀኔራል ናፒየር የሚመራው የእንግሊዝ ጦር ባይመጣ ኖሮ የአፄ ቴዎድሮስ ፍፃሜ የሚሆንበት ጊዜ መቼ ይሆን ነበር? አፄ ቴዎድሮስ በትግራይ፣ በወሎና በሸዋ ለተነሱት ጉልበተኞች በቀላሉ ይንበረከኩ ነበር? ሁለተኛው ጥያቄዬ ፕሮፌሰር መስፍን በገፅ 199 ላይ የጠቀሱት ነው፡፡ እንዲህ ይላል፡ “በተረጋገጠ ውነትን” ለመቀበል ምን ያህል እንደሚያስቸግራቸው ለመረዳት ብለው ብዙ ያልተፈቱ ምስጢሮች አሉ በማለት ከጠቀሷቸው ስድስት ጉዳዮች መካከል … የአፄ ኃይለሥላሴን አባት ማንነት፤ የልዑል መኮንን አሟሟት፤ የኮሎኔል መንግሥቱ እናትና አባትን የምችለውን ያህል አጣርቼ የተረጋገጠ የምለውን አግኝቻለሁ ይላሉ፡፡ እዚህ ላይ ፕሮፌሰር አዲስ አጣርተው ያገኙት መረጃ ምንድን ነው? ምንአልባት ወደፊት በሚያሳትሙት መፅሐፍ ወይም መጣጥፍ ይነግሩን ይሆናል እንጂ አሁን ምንም ከቀድሞው የተለየ የነገሩን ያለ ነገር የለም፡፡ በመጀመሪያ እስቲ በህይወት ስለአሉት ስለ ኮሎኔል መንግስቱ ኃ/ ማርያም አባት እና እናት እናንሳ፡፡ ኮሎኔሉ በተደጋጋሚ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፤ አባታቸው የሸዋ ኦሮሞ እናታቸው የመንዝ አማራ መሆናቸውን ራሳቸው ገልፀውልናል፡፡(የደጃዝማች ከበደ ተሰማ ልጅ ናቸው የሚለውን ሊያረጋግጥ የሚችል መረጃ ተገኝቶ ካልሆነ በስተቀር፡፡) ሌላው የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጉዳይ ነው፡፡ ተፈሪ የራስ መኮንን ልጅ መሆናቸውን ራሳቸውን ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ “ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ” በተባለው መፅሐፋቸው፣ ብ.ጌ.ማኅተመ.ሥላሴ ወልደ መስቀል “ቸ በለው” በሚለው መፅሐፋቸው፣ ግራጌታ ኃይለጊዮርጊስ በለጠ “የራስ መኮንን ታሪክ” በሚለው መፅሐፋቸው እንዲሁም ተክለፃዲቅ መኩሪያ “የአፄ ምኒልክና የኢትዮጵያ አንድነት” በሚለው መጽሃሕፋቸውና በሌሎችም ልዩ ልዩ መፃህፍቶች ይሄው ጉዳይ ተረጋግጧል፡፡ ራስ መኮንን ደግሞ የሸዋው የንጉሥ ሣህለ ሥላሴ ልጅ የልዕልት ተናኘ ወርቅ ልጅ መሆናቸው ግልፅ ነው፡፡ ታዲያ ይህን የሚያስተባብል ሌላ መረጃ ካለ ለምን አልቀረበም? የልዑል መኮንን አሟሟትም ነገሩን ለማሳጠር በስፋት የተነገረውና የተዘገበው በመኪና አደጋ እንደሞቱ ነው፡፡ እና እዚህ ላይ ሌላ የሚጠቀስ አዲስ መረጃ አለ ወይ? ፕሮፌሰር ያልገለፁትና ያላብራሩት መረጃም ተገኝቶ ከሆነ ሊገለፅ የሚገባው የልጅ እያሱ አሟሟትና ጠቅላላ ሁኔታ ነበር፡፡ በአጠቃላይ “መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ” ግን በይዘቱ፣ በአፃፃፍ ስልቱ፣ በሒሳዊ አቀራረቡ ብሎም ደግሞ የሀገራችን ጉዳይ በሀገራችን ሊቃውንት ተጠንቶ ለኢትዮጵያኖች መቅረብ እንዳለበት የተሰጠው ጠንከር ያለ ማሳሰቢያ እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ በተረፈ ፕሮፌሰር መስፍን ጤናና ዕድሜ ሰጥቷቸው በርካታ መረጃዎችን ለወገናቸው ማቀበላቸውን እንዲቀጥሉ እንፀልያለን፡፡

  • ስለድሮና ስለአሁኑ ፓርላማ ነፃነት እያነፃፀሩ ያስረዳሉ 
  • የሦስቱን መንግስታት ጠንካራና ደካማ ጎኖች ይገልፃሉ 
  • ስለንጉሱና ከንጉሱ ጋር ስለነበራቸው ግንኙነት ይናገራሉ 
  • “መደነስ እወድ ነበር፤እነ ራሔል ዮሐንስ ደስ ይሉኛል” ብለዋል

በአፄ ኃ/ስላሴ ዘመን የፓርላማ አባል እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ የያኔውንና የአሁኑን ሲያነፃፅሩት፤በአፄ ኃ/ ስላሴ ዘመን የነበረውን የፓርላማ ነፃነት እንዴት ይገልፁታል---- እንደ ዛሬ በፓርላማ ለሚነሱ ጥያቄዎችና በመከራከሪያ ነጥቦች ዙሪያ የሚካሄደው ውይይት ምን ይመስል ነበር?

በጣም ጥሩ ጥያቄ ነው፡፡ በዛን ጊዜ የፖለቲካ ፓርቲ አልነበረም፡፡ የገዥ ፖለቲካ፣ የተገዥ ፖለቲካ የሚባል ነገር የለም፡፡ግን በሀሳብ መስማማትና በሀሳብ ያለመቀራረብ ሁኔታዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ እኔ የምናገረው ነገር የሚጥማቸውና የሚስማማቸው አሉ ሆን ብለው ደግሞ የሚቃወሙ አሉ የሀሳብ ቡድን እንጂ የፓርቲ ቡድን አልነበረም፡፡ የአሁኑ ልዩነቱ ፓርቲ ነው፤ የፓርቲ ዲሲፕሊን አለ፡፡ ያኛው ለክርክር የበለጠ ነፃ ነው፡፡ ሁሉም እንደፈለገው ነው የሚናገረው፣ የሚመዝንለት አብዛኛው እዛው ያለው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን ፓርቲ ስለሆነ ከፓርቲ ዲሲፕሊን ውጪ ምንም መናገር አይቻልም፣ የፓርቲን ዲሲፕሊን መከተል አለበት፣ ስለዚህ ሁኔታው የተለያየ ነው፡፡

በንጉሱ ጊዜ በፓርላማ ሳሉ እንደ ህዝብ አጀንዳነት የሚከራከሩባቸው ነጥቦች ምን ምን ነበሩ? የትኞቹ የህብረተሰብ ጥያቄዎች ጎልተው ይሰማሉ?

የህዝብ ጥያቄ ሲባል መሬት ላራሹ፣ የጉልት ገዥ እንዳይኖር ማድረግ እና ሌሎችም የህዝብ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ አብዛኞቹም እንዲስተካከሉ ለማድረግ ችለናል፡፡ “ድሮና ዘንድሮ” በሚል በታተመውና የእርስዎን የህይወት ታሪክ በሚያስነብበው መጽሐፍ ላይ እንደተገለፀው፤

በንጉሱ ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ የፓርላማ ተመራጭ ሆነው ፓርላማ ሲገቡ የተሰጠዎት ቢሮ ምድር ቤትና በጣም ጠባብ ከመሆኑ የተነሳ ቢሮዎትን በራስዎት አውቶሞቢል ውስጥ አድርገው ነበር እስቲ ስለሱ ይንገሩኝ----

ነገሩ እንደዚህ አይደለም፡፡ ቢሮው ጠባብ ነው፤ ትንሽ ነው፤ ምድር ቤት አይደለም፡፡ ከእኔ በፊት የነበረው ሃይለማርያም ከበደ እዚህ ቢሮ ነበር፡፡ ከተሰጠኝ ቢሮ በላይ ያለው ሰፊ ቢሮ፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ ተብሎ ባዶውን ነው ያለው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር የህዝብ እንደራሴ አይደለም፡፡ እታች መውረድ አለበት፡፡ የህዝብ እንደራሴው መሪ የበላይ ነው፤ እላይ መሆን አለበት ነበር ጥያቄው፡፡ አይቻልም ሲሉ እንግዲያውስ እኔም አልገባም ጥሩ መኪና አለችኝ፤ዛፍ ጥላ ስር እቆምና፣ ዶክመንቱን ስታመጡ እዚሁ እፈርማለሁ፤ በኋላም አዳራሽ እገባለሁ እንጂ እዚያ ቢሮ አልገባም አልኩኝ፡፡ ይሄንን የመወሰኛ ምክር ቤት ፕሬዚደንት የነበሩት አስራተ ካሳ ሰሙ፡፡ ስለሆነም መወሠኛና መምሪያ ሁለት የተለያዩ ምክር ቤቶች ቢሆኑም ትንሽ የበላይነት አላቸው፤ የንጉሱም ምርጫ በመሆናቸው፡፡ እነኛ በህዝብ ተመርጠው ሳይሆን፣ በንጉሱ ተመርጠው ነው ሴናተርነት የሚሾሙት፡፡ የሴኔቱ ፕሬዚደንት የጋራ ጉባዔ በምናደርግበት ጊዜ እሳቸው ሰብሳቢ ናቸው፡፡ ይሄን ሲሰሙ ወዲያውኑ ዋና አስተዳዳሪውን አዘዙት፤“እሳቸው እውነታቸውን ነው፤ የህዝብ ምክር ቤቱ እላይ መሆን አለበት፤የህዝብ ምክር ቤት ይበልጣል፤ የጠየቀው ልክ ነው አንሱለት” ተባለ እንደውም በራፌ ላይ የሚቆመው ተላላኪ የቤቴን ቀለም ዓይነት የለበሰ እንዲሆን አድርገው፤በእሳቸውና በእኔ መካከል የዘውድ ማለፊያ የሚባል ነበር፤በዛችው ኮሪደር በነፃ እንድንተላለፍ አዝዘው ከሰዓት በኋላ ወደ ስራ ስገባ፤ ‹‹ወዲህ፣ ወዲህ›› አሉኝ፡፡ ‹‹ወዴት?›› አልኩኝ ‹‹ቢሮ ተከፍትዎሎታል›› ብለው አስገቡኝ፡፡ በጣም ደስ አለኝ፤ አሸነፍኩ ማለት ነው፡፡ የህዝብን የበታችነት ላለመቀበል ነው እንግዲህ አሻፈረኝ ያልኩት፡፡ በኋላ ላመሰግናቸው ቢሮዋቸው ሄጄ ነበር፤ እሳቸው ግን ‹‹ምስጋና አይገባኝም፤ትክክል ነው ጥያቄህ፤የህዝብ ምክር ቤት ነው ዋናው፤እኛ እንኳን ሹማምንቶች ነን፣ የህዝቡ ባለቤቶች እናንተ ናችሁ፣ የሚገባውን ነው የጠየቅኸው›› አሉኝና ቢሮዬ ገባሁ፡፡

ለፓርላማ ለመወዳደር ከወሰኑ በኋላ የመረጡት የምረጡኝ ቅስቀሳ መንገድ---- በመኪና እየዞሩ እና ዊንጌት ትምህርት ቤት ተገኝተው ያደረጉት ህዝባዊ ውይይት ነበር፤ በወቅቱ እንደተፎካካሪ የነበረብዎት ፈተና ምን ነበር?

የነበረው ቻሌንጅ ስለመንግስት በይፋ በአደባባይ አይነገርም ነበር፡፡ መንግስት ሲባል ህዝቡ አንድ የሚመለክ ነገር እንጂ አንድ የአስተዳደር ቡድን መሆኑን አያውቅም፡፡ ህዝቡ ይህን እንዲያውቅና መንግስት ምን እንደሆነ እንዲገነዘብ፤ የሚመርጠው እንደራሴ ምን እንደሚጠበቅበት እንዲያውቅ፣ ጥያቄም ካለው እየጠየቀ እንዲረዳ የምርጫ ካምፔን ነበር ያደረግነው፡፡ በዓይነቱ የመጀመሪያ እና ያልተለመደ ነበር፡፡ አሁን አሜሪካ ሀገር ከሚገኘው ዘውዴ ከተባለ ሰው ጋር ነበር፡፡ አንድ ቦታ ላይ የምርጫ ዘመቻ ስናደርግ በአጋጣሚ ከዊንጌት ተማሪዎች አንዱ፣ ‹‹አንተ አጭበርባሪ መቶ አለቃ እስኪ እኛ ጋ ናና እንደዚህ ተናገር›› አለኝ፡፡ ‹‹እናንተ ምንድን ናችሁ?›› ‹‹የዊንጌት ተማሪዎች›› ‹‹ታዲያ እኔ ዊንጌት ምን ይወስደኛል፤ቀራኒዮና ልደታ ነው የምርጫ ጣቢያዬ፡፡ ጥሩ እንግዲያው እመጣለሁ›› አልኩኝ፡፡ መቼም የዊንጌት ተማሪ ቤት ታውቂው እንደሆነ አዳራሹ በጣም ሰፊ ነው፡፡ ያሉ ተማሪዎች ብቻ ሳይሆን የወጡ ተማሪዎች ሁሉ ተገኙ፡፡ ከአሰብኩት በላይ አዳራሹ ጢም ብሎ ነበር፡፡ ክርክር ተጀመረ፤ ብዙ ተከራከሩኝ በዛው ት/ቤት መምሬ ዘውዴ የተባሉ የሞራል አስተማሪያቸው ምረጡኝ ብለው ቀስቅሰዋል፡፡ እና ብዙዎቹ እድሜያቸው የደረሱ ልጆች እንዲመርጧቸው አስመዝግበዋል፡፡ ለተማሪዎቹ ምን አልኳቸው፤ ‹‹ይሔ የፖለቲካ ጉዳይ ነው፤የኢትዮጵያን ፖለቲካ መሻሻል የምትፈልጉ እኔን ትመርጡኛላችሁ፤መንግስተ ሰማያት መግባት የምትፈልጉ ቁልፉ መምሬ ዘውዴ እጅ ነው፤እሳቸውን ምረጡ›› አልኳቸው(ሳቅ)፡፡

ለምንድን ነው እንደዚያ ያሉት?

ቄስ ስለሆኑ ነው፡፡ እኔ እዚያ አካባቢ ንክኪ የለኝም፡፡ መንግስተ ሰማያትንና ፖለቲካን ምን አመጣው ብትይ---- እሳቸው የሚመረጡበት ነገር ቢኖር እንዲባርኩ ብቻ ነው የሚሆነው(ሳቅ)፡፡

ይህን በመናገርዎት ምን ተፈጠረ?

መምህሬ ዘውዴ ጠዋት ዊንጌት ትምህርት ቤት ባንዲራ የሚያሰቅሉ እሳቸው ናቸው፡፡ ተማሪዎቹ የትምህርት ቤት በራፍ ላይ ጠበቁዋቸውና ‹‹ጊዜዎንም ገንዘብዎንም አያጥፉ፤ ስለ እኛ መናገር የሚችልና እኛ የገባነው ሰው አግኝተናል፤ የምንመርጠው መቶ አለቃ ግርማን ነው›› ብለው ተስፋ አስቆረጡዋቸው፡፡ እኔ ግን ከዛ አካባቢ 8 በመቶ ድምፅ አገኘሁ በዛች በአንድ ቀን ቻሌንጅ ማለት ነው፡፡

ኢትዮጵያን የዓለም ፓርላማ አባል ለማድረግ ባደረጉት ጥረት ኢትዮጵያን ወደ አንድ ደረጃ ከፍ አድርገዋታል፤ በዚህ ምን ይሰማዎታል?

በጣም ጥሩ ስሜት ነው የተሰማኝ፡፡ ሁሉ ሰው ፈርቶ ነበር፡፡ የሚገርምሽ የአለም ፓርላማ አባል ጥሪ ግብዣው አስራ ስድስት ዓመቱ ነበር፡፡ ለሴኔቱ ፕሬዚዳንት ልዑል አስራት ካሳ ሄድኩና ‹‹እኔ ይሄን ነገር ማስፈቀድ አለብኝ›› አልኳቸው፡፡ ‹‹እረ በፍጹም እንዳታደርገው፣ይጣሉሃል›› አሉኝ፡፡ ‹‹ለምን ይጣሉኛል፣እኔ የቤቴን አዘጋጅቻለሁ፤አባል ይሆናሉ ያልኳቸውን ሰዎች መርጫለሁ›› አልኳቸውም፡፡ መመዘኛው ቡድን ነበር፡፡ ‹‹ንጉሠ ነገስቱን የውጪ ጉዳይ ስለሆነ አስፈቅዳቸዋለሁ›› አልኳቸውና ንጉሠ ነገሥቱ ዘንድ ሄድኩኝ፡፡ ‹‹እንግዲህ ህዝብዎ የተፃፈ ህገ መንግስት ጥቅም ባላወቀበት ጊዜ የተፃፈ ህገ መንግስት ሰጡት፡፡ አሁን እድገቱ አንድ ቦታ ላይ ደርሶ የዓለም ፓርላማ አባል መሆን አስፈላጊ ሆኗልና ይሄንን እንዲፈቅዱ ነው›› አልኳቸው ታውቂያለሽ ምን እንዳሉ ---- ‹‹እሺ ፈቅደናል›› አይደለም ያሉት፡፡ ‹‹ባጀቱን ጭምር ፈቅደንላችኋል›› ነው ያሉት (ሳቅ)፡፡ ወጪም ቀነሱልን በጣም ደስ የሚል ሁኔታ ነበር፡፡ ንጉሱ ብዙ ግዜ ፖዘቲቭ ናቸው፤ደህና አድርገው ካስረዱዋቸው፡፡ ችግሩ ሳያስረዷቸውና አንዳንድ ሰው ለማስረዳት ስለሚፈራ ነው፡፡ እኔ ግን ማን አይዞህ እንዳለኝ አላውቅም፤ ፍርሃቷን አስወግጃለሁ (ሳቅ)፡፡

ከንጉሱ ጋር ጥሩ ግንኙነት ነበራችሁ ማለት ነው?

በጣም በጣም፡፡ ጥሩ ግንኙነት ነበረን ለማለት እችላለሁ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጊዜ እየተከሰስኩ(እየተወቀስኩ) ነበር የምቀርበው፡፡ ስቀርብ ግን አስረድቼ እወጣለሁኝ፡፡ ሳስረዳቸው ያምኑኛል፣ ያመሰግኑኛል፡፡ እንደውም አንዷ አንድ ወቅት የትራንስፖርትና መገናኛ ሚኒስትሩ አስቸገረን አሉና አቀረቡላቸው፡፡ እሱ ሲመጣ የሚናገረውን አታውቁትምና ተውት አሉ (ሳቅ) እንደውም ይከላከሉልኝ ነበር ማለት ነው፡፡

በቅኝ ግዛት ስር የነበሩ ሃገሮችን ስልጣኔና የቋንቋ ውርስነት በማገናዘብና በማየት አንዳንድ ኢትዮጵያውያን “እንደው ጣሊያን አምስት ዓመት ተጨማሪ ገዝታን በሆነ ነበር---” በሚል ሲናገሩ ይደመጣል፡፡ እርስዎ በዚያን ዘመን በተለያየ የመንግስት ስራ ሃላፊነት ላይ ነበሩ፡፡ ጣሊያኖችን እንዴት ያስታውሷቸዋል፣ የሚጠቅሱት የእነሱ ውለታ አለ?

በጣሊያኖች ጊዜ ሰራተኛ አልነበርኩም፡፡ኩሊ ነበርኩ፣ተሸካሚ የተማርኩትም ከአንድ ቤት አንጣፊ ጋር አሸዋ እየተሸከምኩለት፤ አንድ ቀን እሱ ሌላ ቦታ ሲሄድ እሱ እንደሚያደርገው ሰርቼ ስጠብቀው ከዛ በኋላ ሁለት ክፍል አንድ ክፍል እያደረገ እንዳነጥፍ እየለቀቀልኝ መጣ፡ ፡ ደሞዜም በቀን እስከ አስራአምስት ሊሬ በሳምንት መቶ ሃምሳ ሊሬ ሆነልኝ፡፡ ብስክሌት መግዛትና ምቾት መልመድ ጀመርኩኝ፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላ በብስክሌቴ እናቴን ለማየት በየሳምንቱ መሄድ ጀመርኩኝ ባለብስክሌት ነበርኩኝ ማለት ነው(ሳቅ) ጣሊያን ጥሩ ገዥ አይደለም፡ ፡ በርግጥ ጥሩ ሰራተኛ ነው በግዛቱ ይሄን አድርጎልናል፤ ለህዝብ ይመቻል የሚባል ነገር የለውም፡፡ እንደውም አፓርትይድ ነገር ነው፡፡ ለምሳሌ በጣሊያን ጊዜ ከፊት አውራሪ ሃብተ ጊዮርጊስ ድልድይ ወዲህ ማዶ እንደውም ሃበሻ አይሻገርም ነበር፡፡ የፈረንጅ ከተማ ነው ማዶ መርካቶ ግን የሀገር ህዝብ መኖሪያ ነው እስከዚህ ድረስ የሚለያይ መንግስት ነበረ ደግነቱ ረጅም ጊዜ አልኖረም እንጂ ጥሩ አልነበረም፡፡

ግን እኮ በወቅቱ ትልልቅ ድልድዮችንና መንገዶችን ሰርቷል----

እርግጥ ነው በጣም ትልልቅ መንገዶችን ሰርቷል፣ ድልድዮችንም ሰርቷል፡፡ ዋና ዋና የሆኑ መንገዶችን፤ ከአዲስ አበባ ጅማ፤ ከአዲስ አበባ አስመራ.. የመሳሰሉትንም ዘርግቷል፡፡ ግን መንገዱን የሰራው ለህዝቡ ጥቅምና ለኢኮኖሚ እድገት ብሎ ሳይሆን ለራሱ ጦር መዳረሻ ብሎ ነው፡፡ ስለዚህ የጣሊያን ብዙ እዳ ያለብን አይመስለኝም፡፡ በርግጥ የስራ ባህል ሰጥቶናል፡፡

በስልሳ ዓመት የሥራ ዘመንዎት በሀገር ውስጥ የማይደፈሩ፣ ምላሽ ያጡ፣ አይሆንም የተባሉ፣ የተረሱ የሚባሉ አካባቢዎችን፣ አይቻልም የሚባሉ ጉዳዮችን እንደ አጀንዳ በማንሳትና በመከራከር ወደ አንድ ደረጃ ያመጡ ነበር፡ ፡ ለዚች ሃገርም ባለውለታ ነዎትና ዛሬ ይሄን ሳላደርገው ብለው የሚፀፅትዎት ነገር አለ?

ላደርግ ሲገባኝ ሳላደርግ ቀረሁ፤ ይሄን ማድረግ ሲገባኝ ተበላሸብኝ ብዬ የማስታውሰው ነገር ብዙም የለም፡ ፡ በርግጥ አንዳንድ የከሸፉ ጥሩ ሃሳቦች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ እነሱን ማንሳት ለአሁኑ ትውልድ የሚጠቅመው አይሆንም፡ ፡ ይሄ ቂም ነው፡፡ ለምሳሌ ከዚህ ውስጥ አንዱን ለመጥቀስ ይህል፣ እኛ ቦሌን ሰርተን አዲስ አውሮፕላን ማረፊያ እየገነባን ሳለ እኔ ሞንቲሪያ ስብሰባ ላይ ነበርኩ፤አንድ ሃሳብ አገኘሁና---- ኬኤው የሚባል አለማቀፍ ድርጅት እየረዳ ትምህርት ቤት ያቋቁማል፣ በአንዳንድ በሰለጠኑ ሃገሮች ኢትዮጵያ የእንግሊዝም ሆነ የጣሊያን ተናጋሪ ችግር ስለሌላት፤ትምህርት ቤቱን ኢትዮጵያ ውስጥ ብታደርግ ለሁላችንም ይጠቅማል ብዬ አሰብኩና ያለውን አሮጌውን አውሮፕላን ማረፊያ ከነፋሲሊቲው እንሰጣችኋለን፡ ፡ የአቪየሽንን ኮሌጅ(ተማሪ ቤት) አዲስ አበባ አሮጌውን አውሮፕላን ማረፊያ ላይ አድርጉልን አልኳቸው፡፡ እሽ አሉኝ፡፡ መንግስት ያን ተቀብሎ ካፀደቀው በኋላ ላኩብንና እንመጣለን አሉ፡፡ በጣም ትልቅ ነገር ነበረ፡፡ እኔ ከአሜሪካኖች ጋር ብዙ ፍቅር አልነበረኝም፤ መንግስት ከሲቪል አቬሽን ወደ ትራንስፖርት ቢሮ አሻገረኝ፡፡ እኔን የሚተካ ሰው ለማግኘት ሲቪል አቬሽን ስድስት ወር ነበር የፈጀባቸው፡፡ ሰው ጠፍቶም አልነበረም፣አሜሪካን የሚወድ ሰው ሲፈልጉ ነው እኔ ደግሞ ከአሜሪካን ጋር ጠብ የለኝም፡፡ እነሱ እንኑር ይላሉ፣ እኔ ደግሞ እኛ እንተካቸው ነው የምለው፣ የጥቅም ትግል ነው፡፡ በእኔ ቦታ አባተ አግደው የተባሉ አሜሪካን አገር ካውንስላችን ሆነው ይሰሩ የነበሩ ተሾሙና መጡ፡፡ እኔ ወጣሁ ‹‹አውሮፕላን የማያይበት ሃገር ይሂድ፡፡” ነበር የተባልኩት፣ ሲፈረድብኝ፡ ፡

አውሮፕላን ማብረር ስለሚወዱ ነው----

አውሮፕላን ማብረር ስለምወድና ስለ አውሮፕላን እድገት ብዙ ስለምከራከር ነው፡፡ ልጅ አባተ ወረቀት አገኙና ንጉሱ ጋር ሄዱ፡፡ የሲቪል አቬሽኑ ት/ቤት ራቲፊኬሽን ከማግኘት ይልቅ ይሄ እብድ መቶ አለቃ ያመጣብን ጣጣ ስለሆነ ይሰረዝልን ብሎ ተከራከረ፣ ተሰረዘ፡፡ በጣም ያሳዝነኛል፡፡ ያን ጊዜ አቪየሽን ኮሌጅ እዚህ ቢሆን ኖሮ፤ ዛሬ የት ደርሰን ነበር፡፡ የሆኖ ሆኖ እንግዲህ ይሄ ቂም ነው፡፡ በተረፈ ረዥም ጊዜ የሰራሁት ኤርትራ ውስጥ ነው፡፡ የስራ ዕድሜዬ ጥሩው ክፍል (21 ዓመት) ማለት ነው፡፡ በስኬት እንጂ በውድቀት የማስበው ነገር የለም፡፡ ሌላው ቀርቶ ያልለማውን ዳህላክ ደሴት እንኳን ለማልማት ችያለሁ፡፡ ቀላል አይደለም ይሄ ስኬት ደስ የሚለኝና የምኮራበትም ነው፡፡

በአፄውም ጊዜ ሆነ በደርግ ዘመን፤ በተለያዩ መንግስታት በሃላፊነት ሲሰሩ ቤተመንግስት ቤትዎ ነበር፡፡ ለንጉሱና ፕሬዚዳንቱም ቅርብ ነበሩ፡፡ ዛሬ ያሉበትን የኃላፊነት ደረጃ አልመውት ያውቃሉ? እንዴት አርጎ ሰው እዚህ እገባለሁ ብሎ ያልማል፡፡ ሰው መቼም ህልም አለው --- ፕሬዚዳንት፣ ጠ/ሚኒስቴር፣ ዶክተር ብሆን ወይም እሆናለሁ ብሎ ያልማል----

ሠራተኛ እንጂ ህልመኛ አልነበርኩም፡፡ ሹመት ጠይቄ አላውቅም፤ የደሞዝ ጭማሪ ጠይቄ አላውቅም፡፡ ከመስራት በስተቀር፡፡ ስራ ከተሰራ ግን የሚፈለግ ነገር ሁሉ መገኘት እንደሚችል ግልፅ ነው፡፡ ስራውን ከመስራትና ስራውን ከማሸነፍ ውጪ በምኞት ደረጃ ይሄን አገኛለሁ ብዬ አነጣጥሬ የሰራሁት ነገር የለም፡፡ በዚያን ጊዜ የነበረው ንግስና በደም ነው፡፡ የንጉስ ልጅ፣ የንግስት ልጅ የምን... እንደውም ከደምም አልፎ የሰለሞን ዘር ወይም የዘር ሃረግ የሆነ ነበር ለንግስና የሚመረጠው፡፡ እኔ ይሄ የለኝም፣ የገበሬ ልጅ ነኝ፡፡ እና ይሄንን ማለም አልችልም ነበር፡፡ ትልቅ ቦታ ደረስኩ ከተባለ ... ሚኒስቴር ደረጃ ልደርስ ብችል ለእኔ በቂዬ ነበር፡፡ እና ሳላስበው ነው እዚህ የደረስኩት፡ ፡ የታሪክ አደጋ ነው፡፡ ዲሞክራሲ በመፈጠሩ ምክንያት፣ የንጉስ ደም የሌለው፣የሰለሞን ዘር ....ያልሆነ ማንም ሰው ተመርጦ ርዕሰ ብሄር የሚሆንበት ሁኔታ ስለተፈጠረ ነው እዚህ የደረስኩት፡፡

የስልሳ ዓመት የስራ ዘመን ኢዮቤልዩ በዓልዎ በቅርቡ ሲከበር ባደረጉት ንግግር፣ በስራ ዘመንዎ የተቀዳጁት ስኬት እግረ መንገድዎን ያገኙት እንጂ ሆን ብለው አነጣጥረው የሰሩት እንዳልሆነ ገልፀዋል፡፡ ትክክል ነው፣

ፈረንጆች ይሄን ዊንድፎል ይሉታል ሳታስቢው የምትደርሽበት እና የምታገኝው ነገር ነው፡፡ ለማሰብም ለመመኘትም ሁኔታው አልነበረም፡፡ የሆኖ ሆኖ እዚህ በመድረሴ ተደስቻለሁ፡፡

በሦስት መንግስታት ውስጥ አገልግለዋል፡፡የመንግስታቱን ጠንካራና ደካማ ጎን እንዴት ይገልፁታል?

የሃይለስላሴ መንግስት ምንም ደካማ ጎን አልነበረውም፡ ፡ ግን ህዝባዊ አልነበረም፡፡ የህዝብ ወገን ያልሆነ የዘውድ አገዛዝ ስለሆነ የምወደው እና የማደንቀው ሳይሆን የምቃወመው ዓይነት መንግስት ነው፡፡ ቀጥሎ የመጣው የወታደር መንግስት በመጀመሪያ አያያዙ የምደግፈው ዓይነት ነበር፡፡ የህዝብን ሃሳብ ለማሟላት፤ የህዝብን ነፃነት ለማረጋገጥ የመጣ ነው አንዳንድ ምሁራን ነን የሚሉ መጥተው ኮሚኒስት አደረጉት፤ ኮሚኒስት የሚባል ነገር የማይታወቅበት ሃገር ፍጅት አመጡ፤ ነገሩ ሌላ ሆነ፡፡ እንግዲህ የማላውቀውና የማይገባ ነገር ስለሆነ ስለዛ መናገር አልፈልግም ሂደት ስለሆነ ግን በዛ ማለፍ ነበረብን ማለት ነው፡፡ ከዛ ከነበረው ሲስተም አሁን ያለንበት ላይ ለመድረስ በመሀከሉ የነበረውን ዓይነት ሲስተም መታለፍ ነበረበት፡ ፡ ያለዚያ አሁን የምናደርገውን አናውቀውም ነበር፡ ፡ የአሁኑ ዲሞክራቲክ ነው፤ ዲሞክራሲ ደግሞ ከሁሉም የበለጠ የህዝብን ነፃነት ያከብራል፡፡ የህዝብን እድገት የሚወድ፤ህዝብ ከድህነት እንዲወጣ የሚሰራ፤የሚያስፈልግ ዓይነት መንግስት ነው፡፡ የዚህ መንግስት አባል በመሆኔ ደስታ ይሰማኛል፡፡

ወደ ንግድ ዓለምም በመግባት ላቅ ያለ ስራ ሰርተዋል፡፡ የከፋ ኢሊባቡር የእንጨት ኢንዱስትሪ አክሲዮን ማህበር፤ በጊቤ ወንዝ ተፋሰስ እርሻ ብርቱካንና ማንጎ ተክል፤ የትንባሆ የጥጥና የበቆሎ እርሻ የመሳሰሉትን ከግለሰቦች ጋር በጋራና በግል ሰርተዋል፤በመጨረሻ ምን ደረሰ?

የእንጨት ኢንዱስትሪውን ደርግ ወረሰው፡ እርሻው መንግስት ሲለወጥ እኛ አልነበርንም፤ኦፊሻሊ ተወረሰ ባይባልም ያው ተወስዷል፡፡ እርሻው ግን ጥሩ ታሪክ ያለው እርሻ ነው፡፡ አራት ሆነን ነበር ማህበር የመሰረትነው፡ አራታችንም ከተለያየ ቦታ ነው የመጣነው፤ በሃይማኖትም ሆነ በጎሳ አንድ አይደለንም፡፡ አንደኛው አቶ ዑስማን መሐመድ (ኤርትራዊ)፤ ብላታ በየነ ቢያድግልኝ (ኮንሰርቫቲቭ ኦርቶዶክስ የአድዋ ሰው)፤ዶክተር አማኑኤል ገብረ ስላሴ (የመሰረተ ክርስቶስ ሃላፊ) አራተኛው እኔ ነኝ፤ እኔም ወታደር ነበርኩ፡፡ የስራ ክፍፍል ስናደርግ ብላታ በየነ አስተዳደርና ሂሳብ፣ አቶ ዑስማን መሐመድ የቴክኒክ ሰው ስለሆኑ ትራክተር ቢበላሽ ፓምፕ ቢበላሽ የቴክኒክ ስራ የርሳቸው ነው፡፡ ከመንግስት፤ከአካባቢውና ከዝንጀሮዎች ጋር ሳይቀር ሰላም መፍጠር ደግሞ የእኔ ስራ ነው፡ ከዝንጀሮዎች ጋር የሠላም ውል ተፈራርመናል (ሳቅ)፡፡

እንዴት ማለት?

እነሱ አለም ውስጥ እኮ ነው የገባነው፡፡ ውሃ ለመጠጣት በሺህ ነው የሚመጡት እናም አልፈው የእኛን እርሻ ድምጥማጡን አጥፍተውት ነው የሚሄዱት፡፡ አንድ አሳቻ ቀን ስናያቸው አንዱ በአንዱ ላይ ቆሞ ታወር ሰርተው ምልክት ሲነገራቸው ነው የሚሸሹት፡፡ ከእኛ የበለጠ ያውቃሉ ማለት ነው፡፡ ከአዋቂ ህዝብ ጋር መሟገት አንችልምና እንገብራለን አልንና ወንዝ ወዲያ ማዶ ቀጥ ያለ እርሻ አረስን፡፡ አንድ ልጅ ጠባቂ ቀጠርን፡ ፡ በልተው ጠጥተው ከዚያ መሻገር ከፈለጉ ይመታቸዋል፡፡ መመለሱን ለመዱ፤ እኛ ነፃ ሆንን፡፡ ከመንግስትና ከዝንጀሮ ጋር መፈራረም የእኔ ፋንታ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ማህበር አይዘልቅም የሚባል ነገር ነበር፤ግን የማንተዋወቅ ሰዎች አንድ ሆንን፤ ስራውም ባይኖር አብረን ሰርተን፣ ከብረን፣ ከስረን፣ አሁንም አብረን አለን፡፡

ስለ ባለቤትዎ ወ/ሮ ሳሌም ሲናገሩ ‹‹ሳሌም ለእኔ ዛሬም ውብና ቆንጆ ናት፡፡ ማራኪ..›› ብለዋል የትናንትናና የዛሬ የፍቅርና የትዳር ዘመናችሁን እንዴት ይገልፁታል?

አህ....(የመገረም ሳቅ) እንግዲህ ፍቅር ማለት ብዙ ትርጉም ይኖረዋል፡፡ የመጀመሪያ አፍላ ፍቅር አለ፤ ከዛም በመጋባት መካከል ልጅ በመውለድ.. ከዛ ደግሞ የኃላፊነትና የአብሮ መኖር ጉዳይ ነው የሚሆነው፡፡ እኛ ይሄንን ደህና ተወጥተነዋል አሁንም አብረን ነን፡፡ ሁለታችንም አርጅተናል፣ደክመናል(ሳቅ)፡፡ ከተጋባን 65 ዓመታችን ነው፡፡ ቀላል አይደለም፡፡ ከልጆችዎ መካከል የእርስዎን አርዓያ በመከተል ወደ መንግስት ስራ፣ ወደ ፖለቲካ የገቡ አሉ? ከልጆቼ በውስጣችን የፖለቲካ ልዩነት ያለን አንድ ልጃችን ናት፡፡ እርሷም ኢህአፓ ስለነበረች የመንግስት ተቃዋሚ ነኝ ብላ ፈረንሳይ ነው ያለችው፡፡ የቀሩት ግን አንዱ ካናዳዊ ነው፤አሁን እዚህ ነው ያለው፡፡ አንዷ አሜሪካን አገር አስተማሪ ነበረች፤እስዋም እዚህ ነው ያለችው፡፡ የቀሩት የሉም፡፡ ያሉት ደህና ናቸው፡፡ በ2006 ዓ.ም. የስልጣን ዘመንዎን ይጨርሳሉ፡፡ ከሥልጣን ሲወርዱ ምን ሊሰሩ አስበዋል? ስራ ፈት አልሆንም፡፡ የምሰራውም አላጣም ይሄን ይሄን እሰራለሁ ብዬ ያቀድኩት ግን የለም፤ የሆኖ ሆኖ ሽምግልናም አንድ ስራ ሊሆን ይችላል፤የተለያዩ ሽማግሌን ሊያሳትፉ የሚችሉ ጉዳዮች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ሪሶርስ ፐርሰን ሆኖ የማማከር ሁናቴ አለ፤ ጤና ካለኝ ስራ ፈት አልሆንም፡፡

የህይወት ታሪክዎን የመፃፍ ሃሳብስ ----- እኔ የብዕር ሰው አይደለሁም፡፡ ከዚህ በፊትም ወዳጆቼ ናቸው የጻፉት፡፡ እኔ የጻፍኩት ‹‹አየርና ሰው›› የምትለውን ብቻ ነው፡፡ እቅድ የለኝም፤ ከመጣልኝ ግን አንዳንድ ነገር እሰራለሁ፡፡

በትርፍ ጊዜዎ ምን ይሠራሉ?

መጽሐፍ ማንበብ እወዳለሁ፡፡ የተማርኩትም በማንበብ ነው፡፡ ዘፈን መስማት እወዳለሁ፡፡ መጫወትም መደንስም እወድ ነበር፡፡ እነ ራሔል ዮሐንስ ደስ ይሉኛል፡፡ አሁን አለች እንደሆነ አላውቅም፡፡

አለች

አሁን አራዳውን አናውቀውምና እገሌ ይሻላል ለማለት... (ሳቅ) ይቸግራል፡፡ በጊዜዬ ግን የዘፈንና የደስታ ጠበኛ አይደለሁም፡፡ ሰው ከሰራ በኋላ ደስ ሊለው ይገባል ባይ ነኝ፡ ፡ ሰው ከሰራ በኋላ አንጎሉን ማስጨነቅ የለበትም፤ ሪላክስ ማድረግ አለበት፡፡ ሪላክስ ማድረግ ደግሞ የሚችለው በዘፈን በዳንስ ... ነው፤ እኔ በዚህ ተጠቅሜበታለሁ፡፡

የእናንተ ዘመን የአራዳ መሰባሰቢያ ደጃች ውቤ ሰፈር ነበር?

አይደለም፤የእኛ እንኳን ካሳንቺስ እነ ራሔል ዮሐንስ ጋ ነበር፡፡ አሁን ይኖሩ ይሆናል፣ ጠባያቸውን ሳይቀይሩ አይቀርም እንጂ!!

በመንግስት የሥራ ዘመንዎ በተጨዋችነታቸው የሚያስታውሷቸው ሰዎች አሉ?

በተጫዋችነት ብዙ ሰው አላውቅም፡፡ በስራ ግን ንጉሰ ነገስቱን አደንቃለሁ፡፡ ከእሳቸው ጋር በተለያየ የስራ አጋጣሚ ስለምንገናኝ ከማደንቃቸው ሰዎች አንዱ ነበሩ፡፡ በጨዋታ ካልሽ ግን እንደ እኔ ተጫዋች የለም፡፡

አንዳንድ ብሩህ ተስፈኞች ኢትዮጵያ ወደፊት ተለውጣና ከራሷ አልፋ ሌሎችን በዲቪ የምትቀበል አገር ትሆናለች ይላሉ፡፡ እርስዎ የነገዋን ኢትዮጵያ እንዴት ይገልፁዋታል----

ኢትዮጵያ አሁን በሙሉ ኃይሏ እየሰራች ነው ድህነት መውጣት የመጀመሪያው ነገር ነው፡፡ እየወጣን ነው፡፡ 31 ዩኒቨርስቲ ይዘን ብዙ አዋቂ እያፈራን፣ ከድህነት የማንወጣበት ምክንያት የለም፡፡ እንግዲህ በዲቪ የሚመጡ ካሉ እንቀበላለን፡፡ ከሁሉ በፊት ዲያስፖራ እንዲመለስ እናደርጋለን፡፡ አገሩ ይሻለዋል፡፡ ከዛ የተቀሩት መምጣት ከፈለጉ እንቀበላለን፡፡

በባህር ዳር ዩኒቨርስቲ ሥር በሚገኙ አራት ካምፓሶች የሚማሩ ከ700 በላይ የሚሆኑ ተማሪዎች ከግቢው መባረራቸውን የገለፁ ምንጮች፤ ለተማሪዎቹ መውጣት ምክንያቱ በዩኒቨርስቲ ውስጥ የትኛውም የሃይማኖት ሥርዓትን ማከናወን እና የሃይማኖት አልባሣትን መልበስ የሚከለክለው ደንብ ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ “ኒቃን” የተባለውን ቀሚስ ለብሰው በተገኙ 15 ሴት የእስልምና እምነት ተከታይ ተማሪዎች ላይ በተጣለ የዲስፕሊን እገዳ እንደሆነ ጠቆሙ፡፡ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ፖሊቴክኒክ ግቢ ተማሪ እንደገለፀው፤ በእስልምና ሃይማኖት በቀን አምስት ጊዜ የስግደት ሥርዓት እንደሚከናወንና በአቅራቢያቸው መስጊድ ባለመኖሩ በግቢ ውስጥ በጋራ እንደሚሰግዱ፣ በሌላ በኩል በሃይማኖት ሥርዓት አንዲት ሴት “ኒቃን” የተባለውን ልብስ መልበስ ከጀመረች በኋላ ማውለቅ ክልክል እንደሆነ ጠቁሞ፣ በዚህም ምክንያት የወጣውን ደንብ ሊያከብሩ አለመቻላቸውን ተናግሯል፡፡ ባለፈው ሰኞም በ15 ሴቶች ላይ በተወሰደው የማባረር እርምጃ በፈጠረው አለመግባባት ፔዳ፣ ፖሊ፣ ዘንዘልማና ይባብ ከተባሉ አራት ካምፓሶች ከ700 በላይ ተማሪዎች መባረራቸው ታውቋል፡፡

“ምንም እንኳ ደንቡ የሁሉንም እምነት ተከታዮች የሚገዛ ቢሆንም ለእስልምና እምነት ተከታዮች ግን እጅግ ከባድ ነው” ስትል ለአዲስ አድማስ የገለፀችው ሌላዋ የፔዳ ተማሪና የእስልምና እምነት ተከታይ ወጣት፤ “በቀን አምስት ጊዜ ከግቢ እየወጡ መስገድ ከባድ መሆኑንና ይህም እንዲሻሻል በተደጋጋሚ ብንደራደርም ደንቡ ሊሻሻል ባለመቻሉ ችግሩ ሊከሠት እንደቻለ ተናግራለች፡ ፡ ሌላው ወጣት በበኩሉ፤ “ጉዳዩ በሠላማዊ መንገድ እንዲያልቅ ብዙ ድርድር ቢደረግም ደንቡን አክብረን የማንማር ከሆነ ከግቢ መውጣት እንዳለብን በዩኒቨርስቲው ፕሬዚዳንት በዶ/ር ባይሌ ሲነገረን፣ ጥቂቶቹ ተባረው አብዛኞቻችን አንማርም በሚል በልጆቹ ላይ የተወሰደውን እርምጃ በመቃወማችን ነው” ብሏል፡፡ ያነጋገርናቸው ተማሪዎች፤ ዩኒቨርስቲው “ሴት ተማሪዎች ‘ኒቃን’ መልበስ ካልተፈቀደላቸው እና የተባረሩት ተማሪዎች የተወሰደባቸው የዲስፕሊን እርምጃ ተነስቶላቸው እንዲማሩ ካልተደረገ ገብተን አንማርም” ብለዋል፡፡ አዲስ አድማስ ያነጋገራቸው ስማቸውን መጥቀስ ያልፈለጉ የባህርዳር ዩኒቨርስቲ ከፍተኛ ኃላፊ፤ ግቢውን ጥለው የወጡት ተማሪዎች “ሕግ አናከብርም ያሉ ተማሪዎች በገዛ ፈቃዳቸው ነው እንጂ ዩኒቨርስቲው አንድም ተማሪ አላባረረም” ብለዋል፡፡ ኃላፊው እንዳሉት፤ በግቢው ውስጥ በቡድን መስገድና ሃይማኖታዊ አልባሣት መልበስ የተከለከለ መሆኑን እያወቁ ድርጊቱን መፈፀማቸው ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ቢሰጣቸውም ይህን ደንብ ባላከበሩ ሦስት ሴቶችና በአንድ ወንድ ተማሪ ላይ የዲስፕሊን እርምጃ መወሰዱንና 15 ሴቶች ተባረሩ የሚለው ወሬ ከእውነት የራቀ ነው ሲሉ አጣጥለውታል፡፡

ከ700 በላይ ተማሪዎች ከግቢው ተባረዋል ለሚባለውም “ከግቢ የወጡት 100 አይሞሉም፣ የወጡትም ዩኒቨርስቲው አባሯቸው ሳይሆን በአራቱ ተማሪዎች ላይ ለምን የዲስፕሊን እገዳ ተደረገ በሚል ነው፡፡” ብለዋል፡፡ በዩኒቨርስቲው ውስጥ በአጠቃላይ 20ሺህ ተማሪዎች መኖራቸው የገለፁት ሀላፊው፤ ይህን ሁሉ ተማሪ በተረጋጋ መንፈስ እንዲማር ለማድረግ ጥቂት ሕግ የማያከብሩ ተማሪዎች ላይ እገዳ መጣሉ አግባብ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ “ለጉዳዩ እልባት ለመስጠትና ተማሪው ትምህርቱን በአግባቡ እንዲቀጥል የሀይማኖት አባቶችንና የተማሪ ወላጆችን ጠርተን በሰፊው ከተነጋገርን በኋላ፣ ጉዳዩ በዚህ መልኩ መቀጠሉ አግባብ አይደለም፡፡ በግቢው ውስጥ የየትኛውም እምነት ተከታይ የሆነ ተማሪ በግሉ መስገድና መፀለይ ተፈቅዶለት ሳለ፡ የግድ በሕግ የተከለከለውን ካላደረግን ማለት የሀገሪቱን ሕግና መመሪያ መናቅ ይሆናል” ብለዋል፡፡ በአቅራቢያቸው የፀሎት ቦታ አለመኖሩን በተመለከተም ከክልሉ መንግሥት ጋር በመመካከር ችግሩ መፍትሔ እንዲያገኝ እንደሚጥሩ ገልፀዋል። ተማሪዎች ወደ ግቢ ተመልሰው ትምሕርታቸውን እንዲቀጥሉ ጥሪ እናስተላልፋለንም ብለዋል፡፡

Published in ዜና

የካናዳው ‹‹ቃሌ የኢትጵያውያን የውይይት መድረክ›› ከጎናችሁ ነኝ ብሎናል

29ኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች በጋራ ለመታገል ባለ አስራ አምስት ነጥብ የመግባቢያ ሰነዱ ላይ ነገ ተወያይተው እንደሚያፀድቁት የተገለፀ ሲሆን አገሪቱንና ኢትዮጵያውያንን ተጠቃሚ ያደርጋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የፓርቲዎቹ ሰብሳቢ አስታወቁ፡፡ የመግባቢያ ሰነዱ የህዝብ የበላይነት እንዲሁም ዲሞክራሲያዊ መብቶች የተከበረበት ዘላቂ ህገ መንግስታዊ የመድብለ ፓርቲ ድሞክራሲያዊ ስርዓት መገንባትን ዓላማ ያደረገ እንደሆነና ውይይቱ ፓርቲዎቹን ወደ አንድ ፓርቲነት ሊያመጣቸው እንደሚችል ተገልጿል፡፡ የመድረክ የስራ አስፈፃሚ አባልና የፓርቲዎች ሰብሳቢ አቶ አስራት ጣሴ ለአዲስ አድማስ እንደጠቆሙት፤ ለሃያ ዘጠኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች የመግባቢያ ሰነዱ የተበተነላቸው ሲሆን ፓርቲዎችም በባለ 15 የመግባቢያ ነጥቦች ላይ በመስማማታቸው፣ በነገው ዕለት ውይይት አድርገው በሰነዱ ላይ ለመፈራረም ተዘጋጅተዋል።

የመግባቢያ ሰነዶቹ በዋናነት የኢትዮጵያን ዘላቂ ጥቅሞች የሚነኩ ጉዳዮችንና መንግስት በሚወስዳቸው የሀገርና የህዝብ ጥቅም በሚጎዱ እርምጃዎች ላይ የጋራ አቋም መያዝ፣ የመግባቢያ ሰነዱን የሚፈርሙ ፓርቲዎች አባላት ከመንግስትም ሆነ ከገዥው ፓርቲ የሚደርስባቸውን የተለያዩ ህገወጥ ርምጃ በጋራ መታገል፤ ምርጫን በተመለከተ የጋራ ስትራቴጂ መቀየስ፤ ፓርቲዎቹ በሚያደርጉት ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ሁሉ በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ወጥነት ያለው አቋም መያዝና ትግላቸው ለማቀናጀት እንዲችሉ የህዝቡን የአንድነት መንፈስ የሚያጐለብቱ እርምጃዎችን በጋራ መውሰድ፣ አፍራሽ የመከፋፈል የማጋጨት እርምጃዎችን መከላከል፣ ትብብሩን ወደ ላቀ የፓርቲ አደረጃጀት ደረጃ ለማድረስ የሚያስችል የጋራ አቅጣጫ መቀየስ እና ሌሎች አገራዊና ህዝባዊ ነጥቦች ላይ በጋራ ለመስራት ያለሙ ሲሆን ለዚህም አብይ ኮሚቴና የተግባር ኮሚቴ እንደሚዋቀር ታውቋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ የሃያ ዘጠኙ ፓርቲዎች አመራር አባላት በካናዳ አገር ከሚገኘው ‹‹ቃሌ የኢትጵያውያን የውይይት መድረክ›› ጋር በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይና የፖለቲካ ሁኔታ ላይ በፓልቶክ ውይይት ያደረጉ ሲሆን መድረኩ በማቴሪያል፣ በፋይናንስና በዲፕሎማሲ ድጋፍ እንደሚያደርግላቸው ሰብሳቢው አስታውቀዋል፡፡ የካናዳው ‹‹ቃሌ የኢትጵያውያን የውይይት መድረክ›› በምታደርጉት ሰላማዊ ትግል ከጎናችሁ ነን ብሎናል ብለዋል - አቶ አስራት፡፡ መድረኩ ይሄን ስያሜ ለራሱ የሰጠው የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር የነበረችውን የወ/ሮ ብርቱካን ሚደቅሳን ‹‹ቃሌ›› ዝግጅት ለማስታወስ ይሆናል ያሉት አቶ አስራት፤ አንድነት ፓርቲ ከዚህ በፊት በየወሩ “ቃሌ የጥበብ ምሽት” በሚል የሻማ ማብራትና የውይይት መድረክ ያካሂድ እንደነበርና አሁን ግን ‹‹ቃሌ ምሽት››ን ቀይሮ ‹‹የፖለቲካና የህሊና እስረኞች ምሽት›› በሚል በየወሩ የሻማ ማብራትና ውይይት እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

በካሚላት መህዲን ላይ አሲድ ደፍቷል በመባል የተከሰሰው እና የዕድሜ ልክ እስራት የተፈረደበት ደምሰው ድርጊቱን እንዳልፈፀመና “የፈፀምነው እኛ ነን” ያሉ ወጣቶች ሰሞኑን ለፖሊስ ቃል መስጠታቸውን ምንጮች ጠቆሙ፡፡ ከዛሬ ስድስት ዓመት በፊት የፍቅር ጓደኛው በሆነችው ካሚላት ላይ የአሲድ ጥቃት ማድረሱ በሰው ምስክርና በማስረጃ ተረጋግጧል ተብሎ የተከሰሰው ደምሰው፤ጉዳዩን እንዳልፈፀመ በመናገር ቢከራከርም በሰውና በሠነድ ማስረጃዎች ተረጋግጧል በማለት ፍ/ቤት በሞት እንዲቀጣ ወስኖ ነበር፡፡

ተከሳሽ ይግባኝ ጠይቆ ቅጣቱ ወደ 20 ዓመት ዝቅ ብሎለት የነበረ ቢሆንም ዐቃቤ ሕግ እና የሕግ ባለሞያ ሴቶች ማኅበር ይግባኝ በማለት ተከሳሹ በዕድሜ ልክ እስራት እንዲቀጣ መወሰኑ ይታወቃል፡፡ ከስድስት ዓመታት በኋላ ሰሞኑን “ድርጊቱን እኛ ነን የፈፀምነው” ያሉ ግለሰቦች መገኘታቸውን የተከሳሹ ወላጅ እናት ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን መጠቆማቸውን የሚናገሩት ምንጮች፤ የተባሉት ሦስት ወጣቶች ጫት ቤት ተቀምጠው የፈፀሙትን ድርጊት እያነሱ ሲያወሩ የሰሙ ሰዎች፣ ለተከሳሽ ቤተሰብ በመንገር ጉዳዩ ክትትል እንዲደረግበት ጥቆማ መሰጠቱን ገልፀዋል፡፡ የተባሉት ወጣቶችም ተይዘው በሰጡት ቃል፤ ድርጊቱን መፈፀማቸውን አምነው ቃላቸውን መስጠታቸውን እና ትላንት ደምሰው ከማረሚያ ቤት ወጥቶ በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ቃሉን ሰጥቶ መመለሱን ምንጮቻችን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጉዳዩን እያጣራ በመሆኑ መረጃ ለመስጠት እንደማይችል ገልፆልናል፡፡

Published in ዜና
  • ቤቶቹ ከቤተ መድኃኔዓለም እና ቤተ ዐማኑኤል አጠገብ የተሠሩ ነበሩ 
  • በልደት ክብረ በዓል የቱሪስቶች ቁጥር መቀነሱ ኅብረተሰቡን አስደንግጧል 

በቅዱስ ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም ከዐሥራ አንዱ ውቅር አብያተ መቅደስ ጋር በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ አራት ጥንታውያን ቤቶች በእሳት ቃጠሎ መውደማቸው ተገለጸ፡፡ ባለፈው እሁድ ለሰኞ አጥቢያ መንሥኤው ባልታወቀ ምክንያት በተነሣው የእሳት ቃጠሎ የወደሙት አራት ቤቶች የሣር ክዳን ያላቸው ፎቅ ቤቶች ሲኾኑ፣ የላሊበላን ጥንታዊ የቤቶች አሠራር የሚያሳዩ በመኾናቸው እየተጠገኑ እንዲጠበቁ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ በቃጠሎው የወደሙት ጥንታውያኑ ቤቶች፤ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች መካከል በቅኔና ዜማ ትምህርት መስጫነት ሲያገለግሉ እንደቆዩ ተገልጧል፡፡ ገኛ ቦታቸውም ከዐሥራ አንዱ አብያተ መቅደስ መካከል በታላቁ ቤተ መድኃኔዓለም እና በቤተ ዐማኑኤል አጠገብ ከ20 - 30 ሜትር ርቀት ላይ መኾኑ፣ የገዳሙ አስተዳደር ጽ/ቤት ለቅርሶቹ ደኅንነት ትኩረት ሰጥቶ በቂ ጥበቃና ክብካቤ እንደማያደርግ በካህናቱ እና ምእመናኑ የሚነሡበትን ስጋቶችና ተቃውሞዎች ያጠናከረ ነው ተብሏል፡፡ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማው ነዋሪዎች እንደሚያስረዱት÷ የቃጠሎ አደጋው በደረሰበት ዕለት ሌሊት በሁለቱም አብያተ መቅደስ አካባቢ የገዳሙ ጥበቃ አባላት አልነበሩም፡፡

ከሙስና እና ብልሹ አሠራር ጋር ተያይዞ ጥያቄ የሚነሣባቸውና ላለፉት ስምንት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት የገዳሙ መምህርም ቃጠሎው በደረሰበት ስፍራ የተገኙት ከሁለት ቀናት በኋላ ነው፡፡ ቤቶቹ ሰው በማይኖርበትና ‹‹ኮር ዞን›› ተብሎ በዩኔስኮ በሚታወቀው ለቅርሶች የተለየ ስፍራ የሚገኙ ኾነው ሳለ የተከሠተው ይኸው አደጋ፣ ‹‹በአስተዳደሩ ላይ እየተጠናከሩ የመጡትን ተቃውሞዎች ትኩረት ለማስቀየስ የተፈጠረ›› አድርገው እንደሚወስዱት የስፍራው ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም በአንድ ጊዜ በተደረገው የ160 በመቶ የቱሪስቶች ዋጋ ጭማሪ ሳቢያ ዘንድሮ በተከበረው የልደተ ክርስቶስ (ቤዛ ኵሉ) እና ጥምቀት በዓላት ላይ የተገኙት የውጭ ቱሪስቶች ፍሰት ቀንሶ መስተዋሉን የዜናው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የቱሪዝሙ ባለድርሻ አካላት በበቂ ባልመከሩበት ኹኔታ በአንድ ወገን ውሳኔ ገቢን ከፍ ለማድረግ ብቻ ታስቦ ከጥር አንድ ቀን ጀምሮ በተፈጸመው በዚሁ ጭማሪ ብር 350 የነበረው የቱሪስት መግቢያ ብር 1000 እንዲኾን ተደርጓል፡፡ ባለፈው ዓመት የጥምቀት በዓል ብቻ ከአንድ ሺሕ በላይ የውጭ ቱሪስቶች መገኘታቸውን ያስታወሱት ምንጮቹ፣ በዚህ ዓመት ግን ለቱሪስቱ አስቀድሞ ከተገለጸለት የመግቢያ ዋጋ በተለየና በራቀ አኳኋን ጭማሪ በመደረጉ ምክንያት ቁጥሩ በግማሽ አንሶ መገኘቱን ገልጸዋል፡ ፡ በተለይም ያለቱር ኦፕሬተርስ በግላቸው ለጉብኝት የመጡ ቱሪስቶች ከስፍራው ከደረሱ በኋላ በናረው የመግቢያ ዋጋ ምክንያት ውቅር አብያተ መቅደሱን ሳይጎበኙ የተመለሱ እንዳሉ፣ ከእኒህም መካከል ላሊበላን መጎብኘት አዳጋች መኾኑን ለሚዲያዎች ሐሳብ የሰጡ እንደሚገኙበት ተነግሯል፡፡

የቱሪስት ፍሰት መቀነሱ በዋናነት የላሊበላ ውቅር አብያተ መቅደስ ያለውን የቱሪስት መስሕብነት ማእከል በማድረግ የተመሠረተውን የአስተዳደሩን የልማት እንቅስቃሴና የኅብረተሰቡን ኑሮ ይጎዳል ያሉት ምንጮቹ፣ በከተማው ነዋሪ ላይ ከፍተኛ ድንጋጤ መፍጠሩንም ለዝግጅት ክፍሉ አስረድተዋል፡፡ በልማትና በቅርስ ሀብቱ ተጠቃሚ ከመኾን አኳያ አካባቢው ‹‹ዕድለ ቢስ ነው›› የሚሉት የከተማው ነዋሪዎች፤ ከተማውን ከሌሎች ከተሞች ጋር ከሚያገናኙ መንገዶች አንሥቶ የተሟላ የሆስፒታል መገልገያ ዕቃዎችና የሕክምና ባለሞያዎች ያላገኘውና አገሪቱን በቱሪዝም ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችለው ላሊበላ:- ለመልካም አስተዳደር መስፈን የሚያሰማው ጩኽት ሰሚ ያጣ የቁራ ጩኸት እንዳይኾን በድጋሚ ጥያቄያቸውን ለማቅረብ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

Published in ዜና
Page 2 of 11