በተያያዘ ከትናንት በስቲያ በኦል አፍሪካን ጌምስ ተሳታፊ ከነበሩ የኢትዮጵያ ልዑካናት መካከል 15 አትሌቶች መጥፋታቸውን የሞዛምቢክ ፖሊስና የኢምግሬሽን ባለስልጣናት ማመልከታቸው አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ የውድድሩ አዘጋጅ ኮሚቴ በድረገፁ ይፋ ባደረገው መረጃ በኦል አፍሪካን ጌምሱ ላይ ኢትዮጵያ በ171 ስፖርተኞች ተሳተፊ እንደሆነች ቢገልም 6 በአትሌቲክስ ፤ 6 በባድሜንተን፤ 12 በቦክስ፤ 8 በብስክሌት፤ 10 በቼዝ፤ 7 በካራቴ፤ 1 በውሃ ቀዛፋ፤ 14 በዋና፤ 3 በጣረጴዛ ቴኒስ፤ 1 በሜዳ ቴኒስ እንዲሁም 13 በቴክዋንዶ ውድድሮች በድምሩ 81 ስፖርተኞች ኢትዮጵያን በመወከል እስከ 11ኛው ቀን ተሳትፈዋል፡፡ በ10ኛው ኦል አፍሪካን ጌምስ ላይ በ23 የስፖርት ውድደሮች 48 አገራትን የወከሉ እስከ 5ሺ አትሌቶች በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡ የጠፉትን የኢትዮጵያ አትሌቶች መጨረሻ በተመለከተ በይፋ የተገለፀ ነገር ባይኖርም ስፖርተኞቹ ወደ ደቡብ አፍሪካ ለማቅናት የስደተኞች መሸጋገርያ ናት ከምትባለው ሞዛምቢክ ለቅቀው መውጣታቸው ተገምቷል፡፡ በ10ኛው ኦል አፍሪካን ጌምስ ላይ የኢትዮጵያ አትሌቶች በአትሌቲክስ ውድደሮች ከ15 ቀናት በፊት በዳጉ የነበረውን ውድቀት በቀለበሰ ብቃት ተሳክቶላቸዋል፡፡ በወንዶች 10ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከሆነ ከ16 ቀናት በኋላ በርቀቱ የአፍሪካ ሻምፒዮን ሊሆን የበቃው ኢብራሂም ጄይላን ሲሆን ሌላው ኢትዮጵያዊ አዝመራ በቀለ በሁለተኛ ደረጃ የብር ሜዳልያውን ተጎናፏል፡፡ በ3ሺ መሰናክል ውድድር ኢትዮጵያWÃnù ብርሃን ጌታሁን፤ ሮባ ጋሪና ሲሳይ ኮሮሜ ከ1-3 በመውጣት ሜዳልያዎቹን ሲጠቀልሉ ፤በሴቶች 5ሺ ሜትር ሱሌ ኡታራና እመቤት መንግስቱ የወርቅና የብር ሜዳልያዎችን ማግኘት ሆኖላቸዋል፡፡ አስደናቂዋ የመከላከያ ክለብ አትሌት ሱሌ ኡታራ በ10ሺ ሜትርም በድጋሚ ተሰልፋ በማሸነፍ በኦል አፍሪካን ጌምስ በሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች የድርብ ድል ባለቤት መሆኗን ስታረጋግጥ በተመሳሳይ ውድድር የብር ሜዳልያው ለሌላዋ ኢትዮጵያዊት ውዴ አያሌው ሆኗል፡፡ በ800 ሜትር ሴቶች ፋንቱ ሚጌሶ የብር ፤ በ20 ሜትር የሴቶች ርምጃ ውድድር አይናለም እሸቱ የነሐስ፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ህይወት አያሌውና ብርቱካን አዳሙ የብርና የነሐስ ሜዳልያዎችን አግኝተዋል፡፡በኦል አፍሪካን ጌምስ ላይ እስከ ሐሙስ በተደረጉ ውድሮች 466 ሜዳልያዎች ለተሸላሚዎቹ የተበረከቱ ሲሆን የሜዳልያ ደረጃውን የምትመራው 131 ሜዳልያዎች 57 ወርቅ፣ 40 ብርና 34 ነሐስ የወሰደችው ደቡብ አፍሪካ ናት፡፡ ደቡብ አፍሪካ በሜዳልያው ደረጃ ከፍተኛውን ብልጫ ያስመዘገበችው በውሃ ዋና ውድደሮች እስከ 74 ሜዳልያዎች በማግኘቷ ነው፡፡