ቀድሞ ቦክሰኛ ለመሆን ጥረት አድርጎ የነበረው ፊፍቲ ሴንት፤ የቦክስ ግጥሚያዎችን በልዩ ሁኔታ በማዘጋጀት ከፍተኛ ገንዘብ እየሰራ መሆኑን አድንቆ የፃፈው ደግሞ ዩሮ ኒውስ ነው፡፡ በሎስአንጀለስ ከፍተኛ ደረጃ ያላቸውን ከባባድ የቦክስ ግጥሚያዎች በማዘጋጀት እና እውቅናውን ተጠቅሞ በርካታ ተመልካች እንዲታደም በመቀስቀስ 50 ሴንት ምርጥ ፕሮሞተር ሆኗል እየተባለ ነው፡፡በምርጥ የራፕ ሙዚቀኛነት፤ በስራ ፈጣሪነት፤ በፊልም ተዋናይነት፤ ጂ ዩኒት በተባለ የሙዚቃ አሳታሚው፤ በተመሳሳይ ስም በሚጠራው የልብስ ኩባንያው እና በተለያዩ የፕሮሞሽን እና የንግድ እንቅስቃሴዎቹ ስኬታማ ለመሆን የበቃው 50 ሴንት፤ 250 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ለማካበት መቻሉን ሴሌብሪቲኔትዎርዝ ድረገፅ ይገልፃል፡፡
በሚቀጥለው ዓመት በአሜሪካው የቴሌቭዥን ጣቢያ “ስታርዝ” ላይ 50 ሴንት የሚያዘጋጀውና ስለአንድ የምሽት ክለብ ባለቤት የሚተርክ ተከታታይ ፊልም መቅረብ እንደሚጀምር ታውቋል፡፡ በቅርቡ “ኪውቪሲ” በሚባል የገበያ ቻናል በስምንት ደቂቃ እስከ 177ሺ ዶላር የራሱን ኩባንያ የሄድፎን ምርቶች በመሸጥ የተደነቀው ፊፍቲ ሴንት፤ በቴሌቭዥን ስራዎቹ እንደሚሳካለት እየተነገረ ነው፡፡