ከካሜሩን፣ ከብራዚል፣ ከስፔን፣ ከአሜሪካ፣ ከደቡብ አፍሪካ፣ ከናይጄሪያና ሌሎች ሀገራት የመጡ ፎቶዎች የሚቀርቡበት አውደርእይ፤ የዛሬ ሳምንት የሚጠናቀቅ ሲሆን በጎንደር ከተማ ለሦስት ቀናት እንደሚቀጥልም አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
በሌላም በኩል የሦስት ሰአሊያን ሥራዎች የቀረቡበት የሥእል አውደርእይ ባለፈው ሳምንት ሐሙስ ካዛንቺስ በሚገኘው የጀርመን ልማት ተቋም (ጂቲዜድ) ዋና መሥርያ ቤት ተከፈተ፡፡ “Meeting Here” የተሰኘውን የስዕል አውደርእይ ያቀረቡት ሰዓሊ አሳየ ንጉሤ፣ ሔለን ዘሩ እና ማርጋሬት ናጋዋ ናቸው፡፡ አውደርእዩ ከጧቱ 3 ሰዓት እስከ ምሽቱ 1 ሰዓት ከሰኞ እስከ አርብ የሚታይ ሲሆን እስከ ታሕሳስ 12 ቀን 2005 ዓ.ም ለሕዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡
በየሁለት ዓመቱ የሚካሄደው “አዲስ ፎቶ ፌስት” የፎቶግራፍ አውደርእይ የፊታችን ሰኞ በጣይቱ ሆቴል እንደሚቀርብ አዘጋጆች ገለፁ፡፡ ከአፍሪካ፣ ከአውሮፓና ከአሜሪካ የመጡ 42 የፎቶ ጋዜጠኞች ሥራዎች በአውደርዕዩ ላይ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ በጣይቱ ሆቴል የሚከናወነው የመክፈቻ ሥነ ስርዓት በጥሪ ወረቀት ብቻ የሚገባ ቢሆንም ከዚያ በኋላ በዚሁ ሆቴል፣ በአልያንስ ኢትዮ ፍራንሴስ፣ በጎተ የጀርመን ባህል ተቋም፣ በጣሊያን የባህል ተቋም፣ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር፣ በአፍሪካ ሕብረት አዲሱ አዳራሽ እና በሥነ ጥበባት ትምህርት ቤት በነፃ መታደም እንደሚቻል አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና