ደራሲና ጋዜጠኛ ሰለሞን ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ በስልክ ሑፍ መልእክት መላኩ እስከ ሰኔ 7 ከሌሊቱ 6፡30 የሚቀጥል ሲሆን ከፊልሙ መጀመር በፊት ባለው ግማሽ ሰዓት ከሚከናወነው የእጣ ሽልማት በተጨማሪ ለየት ያሉ ነገሮች ይኖራሉ፡፡ ድርጅቱ ከፊልሙ ጋር በተያያዘ ባዘጋጀው የእጣ ሽልማት ባለ 32 ኢንች ሳምሰንግ ቴሌቭዥን፣ ሁለት ሳምሰንግ ሞባይሎች፣ 12 የአምባሳደር ሙሉ ልብሶችና እያንዳንዳቸው 50 ብር የሚያወጡ 100 የፊልሙ መግቢያ ካርዶችን እሸልማለሁ ብሏል፡፡ ሽልማቶቹን የሚያስተዋውቁ አንድ ባለ 220 ሜትር ካሬ ቢልቦርድ እና ሌሎች ቢልቦርዶች ከትናንት ጀምሮ፣ በመስቀል አደባባይና በሌሎች ቦታዎች ይቆማሉ ተብሏል፡፡ በፊልሙ ማህሌት በቀለ፣ ሉሊት ገረመው፣ ምክረ ድንበሩ፣ አንተነህ አለማየሁ፣ ችሮታው ከልካይና ሌሎችም ተውነዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ መቼቱን ጅማ ጀምሮ አዲስ አበባ የሚያጠናቅቀው ..አልሞትም.. የተሰኘው ፊልም ነገ በአዲስ አበባና በሌሎች 15 ከተሞች እንደሚመረቅ ተገለፀ፡፡ ሰለሞን ገብሬ ያሰናዳው ፊልም በሶላር ፊልም ፕሮዳክሽን የቀረበ ሲሆን የ100 ደቂቃ ፊልሙን ለመስራት ዘጠኝ ወራት ፈጅቷል፡፡ ዋነኛ የምረቃ ሥነሥርአቱ በአምባሳደር ሲኒማ የሚከናወነው ፊልም ከነገ ጀምሮ ለሕዝብ መቅረብ ይጀምራል፡፡ በፊልሙ ውስጥ ሰለሞን ገብሬ፣ ታጠቅ መለሰ፣ አድያም ዓለምና ሌሎችም ተውነዋል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት በተመሳሳይ ርእስ አብዛኞቹን ተዋንያን ያሳተፈ ሌላ ፊልም ለሕዝብ መቅረቡ የሚታወስ ሲሆን ስለዚሁ ከዝግጅት ክፍላችን የተጠየቁት አዘጋጆች፤ በአዲሱ ፊልም ሌላ ታሪክ ይዘን ቀርበናል ብለዋል፡፡