Print this page
Saturday, 24 November 2012 11:25

ስታቲስቲክስ ለአንድ አገር ዕድገት በጣም አስፈላጊ ነው

Written by  መንግሥቱ አበበ
Rate this item
(5 votes)

በሁሉም የአፍሪካ አገራት በየዓመቱ ኅዳር 9 ቀን የሚከበረው የአፍሪካ የስታቲስቲክስ ቀን “ሥርዓተ ፆታን ያካተተ ስታቲስቲካዊ መረጃ በማመንጨት ልማታችንን እናፋጥን” በሚል መሪ መልዕክት ትናንት በአገራችን ተከብሯል፡፡
ቀኑ የሚከበረው የአፍሪካ ሕዝቦች ስለ ስታቲስቲክስ ጠቀሜታ በቂ ግንዛቤ እንዲያገኙና አገሪቱና መንግሥታት የስታቲስቲክስን የመረጃ ጥራት ለማስጠበቅ በሚያደርጉት ጥረት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ለማብቃት እንደሆነ የጠቀሰው ማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ የስታቲስቲክስ ዕድገት የስታቲስቲክስ መረጃ ወቅታዊነትና ጥራት አጠባበቅ በሚሉ ርዕሶች ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጐባቸዋል፡፡

በየጊዜው ለሚለዋወጠው የሕዝብ ዕድገት ትክክለኛ ምላሽ ለመስጠትና የፖሊሲ ውሳኔ ለውጥ ለማድረግ ጥሩ መረጃ (ዳታ) በጣም አስፈላጊ ነው ያሉት የዩ ኤን ኤፍ ፒ ኤ ተወካይ፤ የሚሠራና የሚተማመኑበት ወቅታዊ፣ ባህላዊ ጠቀሜታ ያለውና በዓለም አቀፍ ደረጃ በማነፃፀር ፖሊሲ ለመቅረጽና ለፕሮግራም ልማት ትግበራ ክትትልና ምዘና ጥሩ መረጃ በጣም ጠቃሚ ነው ብለዋል፡፡ 
ገንዘብ ፈንድ በማድረግና በማኔጅመንት ተጨባጭ ውጤትና ለማስመዝገብና ተጠያቂነትን ለማስፈን መረጃ በሁሉም የዩ ኤን ኤጀንሲዎች ጠቃሚ መሆኑን ተወካዩ ገልፀው፤ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ምርምር በማድረግ የልማት ተሳትፎ የልማት ውጤትን ምን ያህል እንደሚጐዳና እንደሚጠቅም ለመረዳት መረጃ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡
በብዙ የአፍሪካ አገሮች የትምህርትና የጤና መረጃዎችን በማሰባሰብ ጥሩ መሻሻሎች ቢኖሩም፣ የጊዜ አጠቃቀምን ጨምሮ በፆታ ጉዳዮች ፣ በሴቶች ላይ በሚፈፀም ጥቃትና የሥራ ቅጥርን በተመለከተ መረጃዎችን ማጠናቀር ገና ብዙ እንደሚቀር ገልፀዋል፡፡
በዓሉን ማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ ከተመድ የሥነ ሕዝብ ጽ/ቤትና ከአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የስታቲስቲክስ ዘርፍ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን ኤጀንሲው ላለፉት 50 ዓመታት ያደረገው የሥራ እንቅስቃሴና ያለፈባቸውን የዕድገት ደረጃዎች የሚያሳይ ኤግዚቢሽን ቀርቧል፡፡

Read 6128 times