Saturday, 24 September 2011 09:07

ደመራው ባይወድቅስ

Written by  ኤልያስ አባይ
Rate this item
(0 votes)

በገባሁበት ታክሲ ውስጥ ሁለት ሰዎችን አጠጋግቼና አጣብቤ ስቀመጥ፤ የጨዋታ አቦል ላይ ልድረስ ወይም በረካ በላውቅም ጨዋታቸው ግን ሳበኝ፡፡ የጨዋታቸው ፍሬ ሀሳብ በመስቀሉ ደመራ ላይ ሳይሆን በአወዳደቁ ላይ ያነጣጠረ ነበር፡፡ እኔ እድሜዬን ሙሉ በዓሉን በግል ስሳተፍ የደመራው ተምሳሌትነት እንጂ የአወዳደቁ ትንቢት ነጋሪነት ተገልፆልኝ አያውቅም፡፡ ቤ/ክንም አላስተማረችኝም፡፡ ምናልባት ያስተማሩኝ ሰዎች ላይማሩት አልያም... ዘንግተውት ይሆናል፡፡ ከሁሉም የገረመኝ ወደ ሰሜን ከወደቀ የደመራው ትንቢት ከጦርነት ጋር መያያዙ ነው፡፡ በመርህ ደረጃ፤ ነገሩን እንደ ግለሰቦቹ አስተያየት አድርጌ ብቀበለውም ከመርሆቼ አንዱ አላረኩትም፡፡

በመርህ ደረጃ የተቀበልኩትን አስተያየት፤ በመርህ መነር መረመርኩት፡፡ ውጤቱ ግን እንደ አዛውንቶቹ በአራቱ አቅጣጫዎች ላይ ያነጣጠረ ሳይሆን የአራቱ አቅጣጫዎች ባለቤት ወደ ሆነው ወደ አርባ አራቱ ነገደ - ኢትዮጵይ ላይ ያተኮረ ሆነ፡፡ ደነገጥኩ፡፡ እነሱ እንዳይወድቅ የምፈራላቸው ነገዶች ብዛት በአይነትና በመጠን ከመብዛታቸው የተነሳ፣ አንድ በአንድ መዘርዘር ስለከበደኝ በጋንታና በጓንት ሰብሰብ አድርጌ ለማቅረብ ተገደድኩ፡፡
ከሁሉም በፊት ወደ ነገደ ክህነት አየሁ - ማንንና እንዴት ማገልገል እንዳለባቸው ሳይገባቸው ግራ ወደሚያጋቡን የሐይማኖት መሪዎች፡፡ ቤተ-ክህነትን ቤተ-ብሔር ለማድረግ ተግተው ወደሚባዝኑ፤ የሚገባው ቀርቶ የማይገባው ሲሰራ እያዩ ባላየ ወደሚያልፉ አለቆች አቅጣጫ ምነው ባልወደቀ አልኩ፡፡
ከሚማረክ ነፍስ ይልቅ ከዓለም ለሰበሰቡት ሳንቲም ክብርን ወደሚሰጡ፣ ሁሉንም በጐች እኩል መጠበቅ ሲገባቸው ስብ ለታደለው ወደሚያደሉ፤ ጠዋት የመቅደሱን ቅዱስ እቃዎች በነኩበት እጃቸው ከሰዓት የአልኮል ጠርሙስ ወደሚጨብጡ፤ ድቁናቸው ድርቅናቸውን ወዳልቀረፈላቸው፤ የተሻለ አሰራር ያመጡ ወንድሞችን መደገፍ ሲገባቸው የስም ማጥፊያ ታርጋ ወደሚለጥፉ፣ በሰባኪነት ልብስ ተጀቡነው በሰባቂነት ወደሚፋጁ ደመራው ባልወደቀ ተመኘሁ፡፡
የዘማሪነትና ዘፋኝነት ልዩነቱ ሳይገነዘቡ ለአገልግሎት ሲጠየቁ፣ የኮንሰርት ያህል ሒሳብ ወደሚጠይቁ፣ ከወንድሞች ግጭት መፍትሔ ከማፈላለግ ይልቅ ለማፋታት አንደኛውን በጭፍን ወደሚወግኑት፣ ስለትና ሥጦታ ለማዥጐድጐድ መግቢያውን ከማየት በቀር በመውጪያው በኩል ማን እንደሚወስደው ወደማይገዳቸው ምዕመናን አቅጣጫም ደመራው ባልወደቀ!
ተከታይ ወደሆነችው ነገደ ሥልጣን አየሁ፡፡ የወንበሩ መግነጢስ ላልለቀቃቸው እንዲለቃቸውም ወደ¥ይፈልጉት፣ ሊሰሙት ቃል የገቡለትን ህዝብ አፍ ወደሚደፍኑ፣ ከድህነት እናወጣዋለን ብለውን ባስቀመጥናቸው ቦታ ወደ ማናገኛቸው፣ በሚመሩት ተቋም ጓዳቸውን ለማቋቋም ወደሚጥሩት፣ የሚመሩትን ተቋም ሥሙን እንጂ ተግባሩን ወደረሱት፤ የቀረበውን አጀንዳ ከማንበባቸው በፊት ቀድመው እጃቸውን ለድጋፍ ወደ¸ÃWlbLbù# ከነሱ ፓርቲ ውጪ የሆነ እንቅልፍ አጥቶ በመረጣቸው ህዝብ ጉዳይ ላይ ወደ ሚያንኮራፉት አቅጣጫ - ደመራው ባልወደቀ፡፡
የእነሱን ቀኖና ያልተቀበለውን ቀንጥሰው ለመጣል ወደሚጣደፉ፣ ካድሬነት የካራቴ ቤልት ወደሚመስላቸው፣ የበታች ሰራተኞችን የቤታቸው አገልጋይ አድርገው ወደሚቆጥሩ፣ በእግሩ የሚመጣ ሳይሆን በእጁ የሚመጣ ሰውን ለመቀበል ወደሚሽቀዳደሙ፣ የሀላፊነት ቦታቸውን ብዙዎችን ለህልፈት ካልዳረገ ወደማይጥማቸው አለቆች አቅጣጫ - ደመራው ባልወደቀ፡፡
አለቃቸው ቢሮ ተጎልቶ ስብሰባ ላይ ነው ወደሚሉ፤ አለቆቻቸውን ሁሉ እንደምን አደሩ ከማለት ይልቅ ..ነግቷል ጌታዬ.. ማለትን ወደሚቋምጡ፤ ከህሊና በላይ የአለቃ ቁጥጥር # ሥራቸውን የሚያቆሙበትን ምክንያት እንጂ የሚቋጩበትን ብልሃት ወደማይወዱ... ባጠቃላይ ሰብዓዊነታቸውን አይተን ስንዝናና በአራዊትነት ወደሚያሸብሩን፣ ነገደ ባለስልጣንነት ወደሚመስላችው... አቅጣጫ ደመራው ባልወደቀ፡፡
ሦስተኛ ወደ ሆነችው ነገደ ተቃውሞ አየሁ፡፡ ተቃውሞ በአመለካከትና በፖሊሲ ልዩነት ሳይሆን በዘረኝነትና በጭፍን ጥላቻ ወደሚያራምዱ፣ ላገራቸው ጉዳይ ካገራቸው ጠላትም ጋር ቢሆን ለመሞከር ወደሚሞክሩ፤ የሀገር ውስጥ ሁከት ለኩሰው በውጭ አገር ዘና ብለው ወደሚያዩ፣ መሪዎች ይሆናሉ ብለን ስናስብ መሰሪዎች ወደሚሆኑበን፣ ዲሞክራሲን ሊያስገኙ ቃል ገብተው ትውልድን በየአደባባይ ዲሞ ወደ¸ÃdRgùT# ነገደ-ተቃውሞ ነገደ-ተቃውጦ ወደሚመስላቸው አቅጣጫ... ባልወደቀ፡፡
ወደ ነገደ-ፀጋም አየሁ፡፡ በላብ ጥረት ሳይሆን በደም - በሌብነት ይዞታቸው ወደ ሰፋ፣ መሰረት አጥብቀው ምሰሶ አቁመው ይገነባሉ ተብሎ ሲጠበቅ ቆርቆሮ አጥረው መሬት ቆሞ እንዲቀር ወደሚያደርጉ፤ በነፃ ገበያ ከመወዳደር በሰው ህይወት ላይ መደራደር ለሚያምራቸው፤ በጥሩ ምርት ለመክበር መጣር ትተው በጥሩ ምርቶች መለያ ተጠቅመው ወደ መነገድና መሸጥ... ከማንደድና መላጨት ጋር ወደተምታታባቸውና በሀቅ ከመመዘን ይልቅ የስስታቸው ደርዘን ወደ ሚጭኑብን አቅጣጫ ደመራው ባልወደቀ፡፡
ወደ ነገደ-ላብ አደር አቅጣጫም አየሁ፡፡ የደሞዝ ጭማሪንና ዕድገትን ከመጠየቅ በቀር የስራውን ባህሪ ለመልመድና ሙያውን ለማሳደግ ጥረት ወደማያረግ፣ ድህነት ላይ ክንዱን ከመሰንዘር የድርጅቱን እቃዎች ወደሚሰብር፣ የስራ ፈትነት ከፈናቸው በሰራተኝነት መታወቂያ ወደገነዙ፣ በአጠቃላይ ነገደ-ላብ አደርነትን በነገደ-አልቦ ለመቀየር ወደሚለፉት አቅጣጫ ደመራው... ባልወደቀ፡፡
ደመራው ወደነዚህ ነገዶችና አባላት ከሚወደቅ ባይወድቅስ? መውደቅ አልያም ከቦታው መንቀሳቀስ የግድ የሚለው ከሆነ ግን፤ እያለ የሌለ ያህል ዝም ወዳለን አምላክ ብሶታችንንና እሮሮዋችንን ቋጥሮ ይመንጠቅልን፡፡

 

Read 3973 times Last modified on Saturday, 24 September 2011 09:21