Saturday, 21 July 2012 11:05

የዝናብ ህልም

Written by  ኪሩቤል ሳሙኤል
Rate this item
(1 Vote)

ሲዘንብ ሁሌ የሚታወሰኝ ቦታ አለ፡፡ አሁን ከዛ ቦታ ፊት ለፊት ቆሜያለሁ፡፡

ዝናቡን የመፍራት ፍላጐቱ ስለሌለኝ ዝናቡ አፍቅሮኛል፡፡ ዝናብ በግድ ያፈቅራል… ልንሸሸው ብንፈልግም እኛን ፍለጋ ቁልቁል መወርወሩን አያቆምም፣ ብንጠለልም ስብርባሪ ድንጋይ እየፈለገና እየተጋጨ ከእግራችን ስር ማልቀሱን አይዘነጋም፡፡ ጥላቻን ወደመውደድ ሃይል የሚለውጥ አንደኛው የስነፍጥረት ውበት ዝናብ ነው፡፡ የኔ የመጥላት ቅርፅ በአለመፈለግ መጥረቢያ የተቀረፀ ነው፡፡ ከፊት ለፊቴ ያሉት የጥቁር ሻሽ ባለቤት እናትና የጫማ ባለቤት ያልሆነው ጥንጡ ልጃቸው ደግሞ ዝናቡን አለመፈለጋቸውን የሚገልፁት በንፋስ በተናቀ ላስቲክ አማካኝነት ነው -ከጭንቅላታቸው በላይ በመደረብ፡፡ ሃይለኛ ዝናብ ስለዘነበ ሰው መንገዱ ላይ የለም… መንገዱ ደግሞ ንዴቱን ፊቱን በማጨቅየት ይገልፀዋል፡፡

እነዚህ ከፊት ለፊቴ ያሉትን ሁለት የምድር ታሪክ ውስጥ ተቀላቅለው፣ አንድ ታሪክ ሆነው ወይም አንድ ታሪክ ፈልገው ለማለቅ የሚተውኑትን እናትና ልጅ መከታተል ከጀመርኩ ረዥም የሰዓታት ዘመኖች አሳልፌያለሁ፡፡ የቤቴ ግድግዳ ስዕልና የጭንቅላቴ የምስል አለም የተጥለቀለቀው በነዚህ ምስኪን የመንገድ ዳር ውበቶች ነው፡፡ ሁልጊዜ ግን ለምን ከተደገፉት የስልክ እንጨት ግድግዳ ላይ አንስቼ በተንጣለለው ግቢዬ ውስጥ አንድ ክፍል ቤት አልሰጣቸውም እያልኩ አስባለሁ፡፡

ነገር ግን ከዛ የተዋበ ፍሬም አንስቼ ወደ ውብ ግድግዳ ባስጠጋቸው ውበቴ መሆንን ያቆማሉ፡፡

እኔም አንዳች የምስለው ነገር አይኖረኝም፡፡ ከቤቴ ወጥቶ የነሱን ጥቁርና ግራጫ የበዛበት አለም ማየትና ያየሁትን ቤቴ ይዤ ሄጄ መሳል የመኖሬ ምክንያት አድርጌ ቆጥሬዋለሁ፡፡

የልጁ ጨዋታ የኑሮዋቸውን ዜማ እንዳዳምጥ ይነግረኛል፡፡

የእናትየው ትካዜ ከዚህ በፊትም እንዳልተፃፈ… ወደፊትም እንደማይፃፍ አይነት ትልቅ የመፅሃፍ ግዝፈትን ያሳየኛል፡፡ ሁለቱ አብረው ሲሆኑና ዝም ሲሉ ወይም ሲተኙ ያኔ ትክክለኛው የፈጣሪ ምስጥር ከፊቴ ፍንትው ብሎ ይታየኛል፡፡ ሲዘንብ ግን ሌላ ነገር ይከሰታል፣ ከምንማቸው ውስጥ የማያወጡት፣ ከብቸኛው ረዳታቸው ንፋስ እየተገፋ የሚመጣላቸውን የላስቲክ ቤት ይሰራሉ… ላስቲኩ እንደነፍሰ-ብርሃን ሆኖ ይከሰታል… በላያቸው ላይ ተጥመልምሎ አብሯቸው ከዝናቡ ጋር ያለቅሳል፡፡ ያን ማየት በኔ አለም ውስጥ ቤቴ ከከመርኩት ብዝሃ ሀብት በላይ የሆነ ቅርስ ነው፡፡

በስቃያቸው ተደስቼ አላውቅም፡፡ በመኖራቸው ውስጥ የለገሱኝን ውበታቸውን ያለፍቃዳቸው ባይኔ ነጥቄያቸው ገብቼ ከሳልኩ በኋላ ከምስለው ከያንዳንዱ ምስል ፊት ደም እንባ አነባለሁ፡፡ መጠለያቸውን ላስቲኩን እያሰብኩ፣ እሱ ካለቀሰላቸው በላይ ለመሆን ከሙሉው ሰውነቴ በእንባዬ እናጣለሁ፡፡ ሸራዬ ላይ ነፍስ ሲዘሩ ከስልክ እንጨቱ ግድግዳቸው ላይ የሚሞቱ እየመሰለኝ በፍርሃትና በስጋት እርዳለሁ፡፡ ግን የስነጥበብ መጥፎ ልክፍት ይዞ በመጣው የውበት መስፈርት ስለተመታሁ ስለዋሉልኝ ውለታ ምስጋናዬን ወደ ቤት ውስጥ በማስገባት በሙቀትና በመብል ላጠግባቸው አልቻልኩም፡፡

ምክንያቱም ፍሬማቸው ስልክ እንጨቱ ከሌለ… የቀለም ወንዛቸው አዳፋው ከላያቸው ላይ ከተነሳ… ያይናቸው ሰቀቀንና የትካዜ ውርወራቸው ከቆመ፣ የኔም የመኖርና የመሳል ዘመኔ እንደሚቋረጥ አውቃለሁ፡፡ ስለዚህ እዚያው እተዋቸዋለሁ… ስለዚህ እስላቸኋለሁ፡፡

ማታ ላይ ሰዎች ለፀሎት እንደሚንበረከኩት እንበረከክና የስዕሉን ጥበብ እንድኖር ለፈረደብኝ አምላክ እርግማኔን አወርድለታለሁ፡፡

የገባሁበት የቀለም ጉድጓድ እንደሌላው በሰላም እንድተነፍስ አልፈቀደልኝም፡፡ ሃጥያቴን የምናዘዝባቸው የቀለም ብሩሾች ለአንድም ቀን የእፎይታ ስሜት ሰጥተውኝ አያውቁም፡፡

አሁን ማነው ሃጥያቴን መጥቶ የሚያጠራልኝ? አሁን ማነው በሽታዬን የሚጋራኝ? እነዛን ፃድቃን ውበቶቼን ስናፍቅ መጥቶ የቀለማቸውን ድምቀት በቃል የሚፈታልኝ?... በዝምታው የሚጮህልኝ… እያለቀሰ ቀለማቸውን ካይኖቹ እንባን እያፈሰሰ የሚፈጥርልኝ?

የመጀመሪያው የዝናብ እንክብል ከምድር ዘር ወጥቶ ከሰማይ ችግኙን ሲልክና መጥቶ ከምድር ነፍስ ሲዘራ የነፍሴ ሻካራና ጐርበጥባጣ ህልውና መፈራረሱን ይጀምራል፡፡ ጣርያ ባይኖር የዝናብ ድምፅ አይኖር ይሆን እያልኩ የቤቴን ጣርያዎች በሙሉ አነሳቸኋለሁ… ዝናቡ ግን ያኔም ነበር፡፡ እደግምና ዝናብ የማይገጨው ነገር ልፈልግ በማለት በሃይል እሮጣለሁ፡፡ ከርቀቴ ፊት ያጋጠመኝ ወንዝ ካገኘሁ ከዛው ውስጥ ሰጥሜ… ውሃው ውስጥ ትንፋሼን ይዤ እቆያለሁ፡፡ ያኔ ጥቂት ዝምታን አገኛለሁ፣ ዝናቡም አይሰማኝም፡፡ ከባህሩ ውስጥ ሆኜ ወደ ላይ ሳንጋጥጥ የዝናቡ ግልፅ ሚስጥር በባህሩ መልክ ላይ ሲመላለስ የእነዛን የእናትና ልጅ ህይወት እያስታወሰ ሲያነዝረኝ ይታወቀኛል፡፡

ይህ ሁሉ መዘዝ… ይህን ሁሉ የነፍስ መወራጨት ይዞ የመጣው ከዕለታት አንድ ቀንን እየጠበቀ ታሪኩን ከምድር ከሚያትመው ብዙ የዝናብ ታሪኮች መካከል ያንዱ ቀን ታሪክ ነው፡፡ ያን ቀን ከቤቴ በለሊት ማልጄ ሁለቱን ምስኪን ፍጥረቶች፣ ምስኪን ውበቶች ባይኔ ከትቼ በሸራዬ ላበዛቸው ወስኜ የመጣሁበት ቀን ነበር… ያ ቀን ከመኖራቸው ግድግዳ፣ ከስልክ እንጨታቸው ስር ተደግፈው፣ የሌሊት ውበት መስለው ተቃቅፈው ግራጫ ብርሃን የረጩበት ቀን ነበር… ያ ቀን ግማሽ ቀን ሙሉ ካለሁበት ያልተንቀሳቀስኩበት የመጀመሪያው የደመና ቀን… የትካዜዬ ዝምታ ነበር… ያ ቀን በግማሹ ቀን ሙሉ ስጠብቃቸው ምንም አይነት የመኖር ምልክት ከውዶቹ ላይ መመልከት ያቃተኝ ቀን ነበር፡፡

በትላንትናው ምሽት ሙሉ ሌሊቱን ሃይለኛ ዝናብ ሲዘንብ ስለነሱ በማሰብ እየተጨነቅሁ ነበር ያደርኩት፡፡ በጭንቅላቴ ውስጥ ሁለቱም ሲመላለሱ ቀጠሮ እየሰጡኝ መሆኑን አልተረዳሁም ነበር፡፡ ቀጠሮው የዘላለም ነበር፣ ቀጠሮው ያለመምጣት ነበር፣ ቀጠሮው የህይወቴ ርዝመት ነበር፡፡

አዎ… በዛን ቀን የሌሊት ድምፅ ውስጥ የሁለቱ ውበቶች ፀጥታ ሞታቸውን አረዳኝ፡፡ በምድር ገፅ ላይ እንደዚህ ያለ ውበት ማንስ ማግኘት ይቻለዋል? ሞተውም ባይኔ ላይ ይንከራተቱ ነበር፤ ህፃኑ አሁንም የማጣጣር ጨዋት እንዴት እንደሆነ እያሳየ ነበር፣ እናት ደግሞ ምድርን የመተው ዝምታ ምን እንደሚመስል ለግራጫው ሌሊት እየነገረችው ነበር፡፡ ይህን ከኔ ውጪ የሚያውቅ ማንም አልነበረም፡፡ ሁሉም ይመጣሉ፣ ሁሉም ይሄዳሉ፣ ከዛ ሁሉ ግን የኔ ቀለሞች በሞት ውስጥ ተክዘው ውበትን ይተነፍሱ ነበር፡፡

መሞታቸውን ለማንም አልተናገርኩም… ብናገርም ሁሉን ሚስጥሬን ለሚያውቀው ሸራዬ ነበር፡፡ እስካሁን ይገርመኝ ነበር… እንዴት ሦስት ቀናት ያህል መሞታቸውን የመንደሩ ሰው እንዳላወቀ፡፡ እኔ ግን ለአንድ ሳምንት ያህል ከነፍሴ በላይ የሆኑ ስዕሎችን ስስል ነበር፡፡ ስጋዬን የሚያስንቅ ሞት ከሞተ ስጋ ላይ እየቦጨቅሁ በቀለሜ እጮህ ነበር፡፡

ዛሬም ላይ ከዛ ቦታ ላይ ቆሜ ባዶውን የስልክ እንጨት ራቁቱን እያየሁ ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ የሚያለቅስ እንደሚመስል ሁሉ እርጥበቱ ደርቆ አያውቅም፡፡ እሱም እንደኔ ውዶቹን የት ወስደው እንደቀበሯቸው ለማወቅ ባለ ጉጉት፣ በተስፋ ማጣት የሚሄድበት አጥቶ የተገተረ መሰለኝ፡፡

ዛሬም የግድግዳ ላይ ትዝታዬንና ሃጥያቴን እያሰብኩና እራሴን እየቀጣሁ ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ እያዩ በመኖር መገረም አንደኛው የመጨነቅ ፍልስፍናዬ አድርጌ፣ ከቤቴ ስልክ እንጨቱ ጋር፣ ከስልክ እንጨቱ ቤቴ ብቻ በመመላለስ የህይወቴን ስፋት ማቅጠን ላይ ነኝ፡፡

እንዳልገደልኳቸው አውቃለሁ… ዝናቡም ከማፍቀር ውጭ የሞከረው ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ሞተዋል የሚል ቢመጣ እንኳን ከስልክ እንጨቱ ፊት ለፊት ቆሜ ስተክዝ የሚሰማኝ ድምፃቸው፣ የፍቅር ንቅናቄያቸው ከውስጤ ፍቆ ካላወጣው በቀር ማንም ሊያሳምነኝ አይችልም፡፡

የምንም ጥያቄ መላሽ አይደለሁም፣ ምንም ማየት አልችልም፤ ነገር ግን ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ እናም ዝናቡ ይዘንባል፣ ከሰው ጋር ፍቅር ይራጫል… በፍለጋ ያፏጫል፤ ፉጨቱ ውስጥ ጥሪ ያለው መሆኑን ያወቅሁት እኔ ብቻ ነኝ እላለሁ፡፡ ፉጨቱን እኔም ዝናቡም ስናፏጨው እስካሁን ተጉዘናል፡፡ ፉጨታችን ላፈሩ ነው… ላየሩ… ለላስቲኩ… ለምድር ጨርቆች… ለሸራዎች… ለብሩሾች… ለቀለሞች… ለፈጣሪ.. ለህልማችን… ለራሳችን፡፡

ዝናቡ ሲያባራ እኔ አንቀላፋለሁ… ዝናቡ ሲመጣ ይቀሰቅሰኛል፣ ከኔ ቀድሞ እነዛን ውበቶቼን… መኖሮቼን አይቷቸው እንደመጣ ይነግረኛል… ሰዓሊ አይደለሁ… ያየውን የሰማውን እየነገረኝ ውዶቼን መሳሌን እቀጥላለሁ፡፡ ለመታረቂያ እንዲሆነኝ የእናትና የልጅን እርግማን ተሸክሜ፣ የዘላለሜን ቀጠሮ በውበታቸው እየሳልኩና እያነባሁ እቀጣላቸኋለሁ፡፡

 

ሲዘንብ ሁሌ የሚታወሰኝ ቦታ አለ፡፡ አሁን ከዛ ቦታ ፊት ለፊት ቆሜያለሁ፡፡

ዝናቡን የመፍራት ፍላጐቱ ስለሌለኝ ዝናቡ አፍቅሮኛል፡፡ ዝናብ በግድ ያፈቅራል… ልንሸሸው ብንፈልግም እኛን ፍለጋ ቁልቁል መወርወሩን አያቆምም፣ ብንጠለልም ስብርባሪ ድንጋይ እየፈለገና እየተጋጨ ከእግራችን ስር ማልቀሱን አይዘነጋም፡፡ ጥላቻን ወደመውደድ ሃይል የሚለውጥ አንደኛው የስነፍጥረት ውበት ዝናብ ነው፡፡ የኔ የመጥላት ቅርፅ በአለመፈለግ መጥረቢያ የተቀረፀ ነው፡፡ ከፊት ለፊቴ ያሉት የጥቁር ሻሽ ባለቤት እናትና የጫማ ባለቤት ያልሆነው ጥንጡ ልጃቸው ደግሞ ዝናቡን አለመፈለጋቸውን የሚገልፁት በንፋስ በተናቀ ላስቲክ አማካኝነት ነው -ከጭንቅላታቸው በላይ በመደረብ፡፡ ሃይለኛ ዝናብ ስለዘነበ ሰው መንገዱ ላይ የለም… መንገዱ ደግሞ ንዴቱን ፊቱን በማጨቅየት ይገልፀዋል፡፡

እነዚህ ከፊት ለፊቴ ያሉትን ሁለት የምድር ታሪክ ውስጥ ተቀላቅለው፣ አንድ ታሪክ ሆነው ወይም አንድ ታሪክ ፈልገው ለማለቅ የሚተውኑትን እናትና ልጅ መከታተል ከጀመርኩ ረዥም የሰዓታት ዘመኖች አሳልፌያለሁ፡፡ የቤቴ ግድግዳ ስዕልና የጭንቅላቴ የምስል አለም የተጥለቀለቀው በነዚህ ምስኪን የመንገድ ዳር ውበቶች ነው፡፡ ሁልጊዜ ግን ለምን ከተደገፉት የስልክ እንጨት ግድግዳ ላይ አንስቼ በተንጣለለው ግቢዬ ውስጥ አንድ ክፍል ቤት አልሰጣቸውም እያልኩ አስባለሁ፡፡

ነገር ግን ከዛ የተዋበ ፍሬም አንስቼ ወደ ውብ ግድግዳ ባስጠጋቸው ውበቴ መሆንን ያቆማሉ፡፡

እኔም አንዳች የምስለው ነገር አይኖረኝም፡፡ ከቤቴ ወጥቶ የነሱን ጥቁርና ግራጫ የበዛበት አለም ማየትና ያየሁትን ቤቴ ይዤ ሄጄ መሳል የመኖሬ ምክንያት አድርጌ ቆጥሬዋለሁ፡፡

የልጁ ጨዋታ የኑሮዋቸውን ዜማ እንዳዳምጥ ይነግረኛል፡፡

የእናትየው ትካዜ ከዚህ በፊትም እንዳልተፃፈ… ወደፊትም እንደማይፃፍ አይነት ትልቅ የመፅሃፍ ግዝፈትን ያሳየኛል፡፡ ሁለቱ አብረው ሲሆኑና ዝም ሲሉ ወይም ሲተኙ ያኔ ትክክለኛው የፈጣሪ ምስጥር ከፊቴ ፍንትው ብሎ ይታየኛል፡፡ ሲዘንብ ግን ሌላ ነገር ይከሰታል፣ ከምንማቸው ውስጥ የማያወጡት፣ ከብቸኛው ረዳታቸው ንፋስ እየተገፋ የሚመጣላቸውን የላስቲክ ቤት ይሰራሉ… ላስቲኩ እንደነፍሰ-ብርሃን ሆኖ ይከሰታል… በላያቸው ላይ ተጥመልምሎ አብሯቸው ከዝናቡ ጋር ያለቅሳል፡፡ ያን ማየት በኔ አለም ውስጥ ቤቴ ከከመርኩት ብዝሃ ሀብት በላይ የሆነ ቅርስ ነው፡፡

በስቃያቸው ተደስቼ አላውቅም፡፡ በመኖራቸው ውስጥ የለገሱኝን ውበታቸውን ያለፍቃዳቸው ባይኔ ነጥቄያቸው ገብቼ ከሳልኩ በኋላ ከምስለው ከያንዳንዱ ምስል ፊት ደም እንባ አነባለሁ፡፡ መጠለያቸውን ላስቲኩን እያሰብኩ፣ እሱ ካለቀሰላቸው በላይ ለመሆን ከሙሉው ሰውነቴ በእንባዬ እናጣለሁ፡፡ ሸራዬ ላይ ነፍስ ሲዘሩ ከስልክ እንጨቱ ግድግዳቸው ላይ የሚሞቱ እየመሰለኝ በፍርሃትና በስጋት እርዳለሁ፡፡ ግን የስነጥበብ መጥፎ ልክፍት ይዞ በመጣው የውበት መስፈርት ስለተመታሁ ስለዋሉልኝ ውለታ ምስጋናዬን ወደ ቤት ውስጥ በማስገባት በሙቀትና በመብል ላጠግባቸው አልቻልኩም፡፡

ምክንያቱም ፍሬማቸው ስልክ እንጨቱ ከሌለ… የቀለም ወንዛቸው አዳፋው ከላያቸው ላይ ከተነሳ… ያይናቸው ሰቀቀንና የትካዜ ውርወራቸው ከቆመ፣ የኔም የመኖርና የመሳል ዘመኔ እንደሚቋረጥ አውቃለሁ፡፡ ስለዚህ እዚያው እተዋቸዋለሁ… ስለዚህ እስላቸኋለሁ፡፡

ማታ ላይ ሰዎች ለፀሎት እንደሚንበረከኩት እንበረከክና የስዕሉን ጥበብ እንድኖር ለፈረደብኝ አምላክ እርግማኔን አወርድለታለሁ፡፡

የገባሁበት የቀለም ጉድጓድ እንደሌላው በሰላም እንድተነፍስ አልፈቀደልኝም፡፡ ሃጥያቴን የምናዘዝባቸው የቀለም ብሩሾች ለአንድም ቀን የእፎይታ ስሜት ሰጥተውኝ አያውቁም፡፡

አሁን ማነው ሃጥያቴን መጥቶ የሚያጠራልኝ? አሁን ማነው በሽታዬን የሚጋራኝ? እነዛን ፃድቃን ውበቶቼን ስናፍቅ መጥቶ የቀለማቸውን ድምቀት በቃል የሚፈታልኝ?... በዝምታው የሚጮህልኝ… እያለቀሰ ቀለማቸውን ካይኖቹ እንባን እያፈሰሰ የሚፈጥርልኝ?

የመጀመሪያው የዝናብ እንክብል ከምድር ዘር ወጥቶ ከሰማይ ችግኙን ሲልክና መጥቶ ከምድር ነፍስ ሲዘራ የነፍሴ ሻካራና ጐርበጥባጣ ህልውና መፈራረሱን ይጀምራል፡፡ ጣርያ ባይኖር የዝናብ ድምፅ አይኖር ይሆን እያልኩ የቤቴን ጣርያዎች በሙሉ አነሳቸኋለሁ… ዝናቡ ግን ያኔም ነበር፡፡ እደግምና ዝናብ የማይገጨው ነገር ልፈልግ በማለት በሃይል እሮጣለሁ፡፡ ከርቀቴ ፊት ያጋጠመኝ ወንዝ ካገኘሁ ከዛው ውስጥ ሰጥሜ… ውሃው ውስጥ ትንፋሼን ይዤ እቆያለሁ፡፡ ያኔ ጥቂት ዝምታን አገኛለሁ፣ ዝናቡም አይሰማኝም፡፡ ከባህሩ ውስጥ ሆኜ ወደ ላይ ሳንጋጥጥ የዝናቡ ግልፅ ሚስጥር በባህሩ መልክ ላይ ሲመላለስ የእነዛን የእናትና ልጅ ህይወት እያስታወሰ ሲያነዝረኝ ይታወቀኛል፡፡

ይህ ሁሉ መዘዝ… ይህን ሁሉ የነፍስ መወራጨት ይዞ የመጣው ከዕለታት አንድ ቀንን እየጠበቀ ታሪኩን ከምድር ከሚያትመው ብዙ የዝናብ ታሪኮች መካከል ያንዱ ቀን ታሪክ ነው፡፡ ያን ቀን ከቤቴ በለሊት ማልጄ ሁለቱን ምስኪን ፍጥረቶች፣ ምስኪን ውበቶች ባይኔ ከትቼ በሸራዬ ላበዛቸው ወስኜ የመጣሁበት ቀን ነበር… ያ ቀን ከመኖራቸው ግድግዳ፣ ከስልክ እንጨታቸው ስር ተደግፈው፣ የሌሊት ውበት መስለው ተቃቅፈው ግራጫ ብርሃን የረጩበት ቀን ነበር… ያ ቀን ግማሽ ቀን ሙሉ ካለሁበት ያልተንቀሳቀስኩበት የመጀመሪያው የደመና ቀን… የትካዜዬ ዝምታ ነበር… ያ ቀን በግማሹ ቀን ሙሉ ስጠብቃቸው ምንም አይነት የመኖር ምልክት ከውዶቹ ላይ መመልከት ያቃተኝ ቀን ነበር፡፡

በትላንትናው ምሽት ሙሉ ሌሊቱን ሃይለኛ ዝናብ ሲዘንብ ስለነሱ በማሰብ እየተጨነቅሁ ነበር ያደርኩት፡፡ በጭንቅላቴ ውስጥ ሁለቱም ሲመላለሱ ቀጠሮ እየሰጡኝ መሆኑን አልተረዳሁም ነበር፡፡ ቀጠሮው የዘላለም ነበር፣ ቀጠሮው ያለመምጣት ነበር፣ ቀጠሮው የህይወቴ ርዝመት ነበር፡፡

አዎ… በዛን ቀን የሌሊት ድምፅ ውስጥ የሁለቱ ውበቶች ፀጥታ ሞታቸውን አረዳኝ፡፡ በምድር ገፅ ላይ እንደዚህ ያለ ውበት ማንስ ማግኘት ይቻለዋል? ሞተውም ባይኔ ላይ ይንከራተቱ ነበር፤ ህፃኑ አሁንም የማጣጣር ጨዋት እንዴት እንደሆነ እያሳየ ነበር፣ እናት ደግሞ ምድርን የመተው ዝምታ ምን እንደሚመስል ለግራጫው ሌሊት እየነገረችው ነበር፡፡ ይህን ከኔ ውጪ የሚያውቅ ማንም አልነበረም፡፡ ሁሉም ይመጣሉ፣ ሁሉም ይሄዳሉ፣ ከዛ ሁሉ ግን የኔ ቀለሞች በሞት ውስጥ ተክዘው ውበትን ይተነፍሱ ነበር፡፡

መሞታቸውን ለማንም አልተናገርኩም… ብናገርም ሁሉን ሚስጥሬን ለሚያውቀው ሸራዬ ነበር፡፡ እስካሁን ይገርመኝ ነበር… እንዴት ሦስት ቀናት ያህል መሞታቸውን የመንደሩ ሰው እንዳላወቀ፡፡ እኔ ግን ለአንድ ሳምንት ያህል ከነፍሴ በላይ የሆኑ ስዕሎችን ስስል ነበር፡፡ ስጋዬን የሚያስንቅ ሞት ከሞተ ስጋ ላይ እየቦጨቅሁ በቀለሜ እጮህ ነበር፡፡

ዛሬም ላይ ከዛ ቦታ ላይ ቆሜ ባዶውን የስልክ እንጨት ራቁቱን እያየሁ ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ የሚያለቅስ እንደሚመስል ሁሉ እርጥበቱ ደርቆ አያውቅም፡፡ እሱም እንደኔ ውዶቹን የት ወስደው እንደቀበሯቸው ለማወቅ ባለ ጉጉት፣ በተስፋ ማጣት የሚሄድበት አጥቶ የተገተረ መሰለኝ፡፡

ዛሬም የግድግዳ ላይ ትዝታዬንና ሃጥያቴን እያሰብኩና እራሴን እየቀጣሁ ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ እያዩ በመኖር መገረም አንደኛው የመጨነቅ ፍልስፍናዬ አድርጌ፣ ከቤቴ ስልክ እንጨቱ ጋር፣ ከስልክ እንጨቱ ቤቴ ብቻ በመመላለስ የህይወቴን ስፋት ማቅጠን ላይ ነኝ፡፡

እንዳልገደልኳቸው አውቃለሁ… ዝናቡም ከማፍቀር ውጭ የሞከረው ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ሞተዋል የሚል ቢመጣ እንኳን ከስልክ እንጨቱ ፊት ለፊት ቆሜ ስተክዝ የሚሰማኝ ድምፃቸው፣ የፍቅር ንቅናቄያቸው ከውስጤ ፍቆ ካላወጣው በቀር ማንም ሊያሳምነኝ አይችልም፡፡

የምንም ጥያቄ መላሽ አይደለሁም፣ ምንም ማየት አልችልም፤ ነገር ግን ሰዓሊ ነኝ እላለሁ፡፡ እናም ዝናቡ ይዘንባል፣ ከሰው ጋር ፍቅር ይራጫል… በፍለጋ ያፏጫል፤ ፉጨቱ ውስጥ ጥሪ ያለው መሆኑን ያወቅሁት እኔ ብቻ ነኝ እላለሁ፡፡ ፉጨቱን እኔም ዝናቡም ስናፏጨው እስካሁን ተጉዘናል፡፡ ፉጨታችን ላፈሩ ነው… ላየሩ… ለላስቲኩ… ለምድር ጨርቆች… ለሸራዎች… ለብሩሾች… ለቀለሞች… ለፈጣሪ.. ለህልማችን… ለራሳችን፡፡

ዝናቡ ሲያባራ እኔ አንቀላፋለሁ… ዝናቡ ሲመጣ ይቀሰቅሰኛል፣ ከኔ ቀድሞ እነዛን ውበቶቼን… መኖሮቼን አይቷቸው እንደመጣ ይነግረኛል… ሰዓሊ አይደለሁ… ያየውን የሰማውን እየነገረኝ ውዶቼን መሳሌን እቀጥላለሁ፡፡ ለመታረቂያ እንዲሆነኝ የእናትና የልጅን እርግማን ተሸክሜ፣ የዘላለሜን ቀጠሮ በውበታቸው እየሳልኩና እያነባሁ እቀጣላቸኋለሁ፡፡

 

 

 

 

Read 3750 times Last modified on Saturday, 28 July 2012 15:17