ፎቶዎቹን የታላቋ ብሪታኒያ ሚዲያዎች ባያትሙም በአየርላንድ አይሪሽ ዴይሊ ስታር የተባለ ጋዜጣ ከሳምንት በፊት ፎቶዎቹን አትሞ ማሰራጨቱ ውዝግብ ፈጥሯል፡፡ ከትናንት በስቲያ ደግሞ የዴንማርክና የስዊድን ሚዲያዎችም ፎቶዎችን አትመዋል፡፡ ቤተሰቡን መሳለቂያ ያደረገው ተግባር ንግስት ኤልሳቤትበጣም እንዳስቆጣቸው ሲገለፅ የንጉሳውያን ቤተሰቡ የሚዲያዎቹን ተግባር ስግብግብነት እና በምንም አይነት ምክንያት ተገቢ ሊባል የማይችል ተግባር ብሎ እንዳወገዘ ተነግሯል፡፡
የጣሊያኑ ቻይ የኬትን ራቁት ፎቶዎች ለመልቀቅ ከፍተኛ ዘመቻ አድርጎ ሲያትም የፈረንሳዩ ክሎዘር ደግሞ ኬት ሚዲልተን ገላዋን ስትታጠብ የሚያሳዩ ፎቶዎችን አሰራጭቷል፡፡ ሁለቱ ትልልቅ ሚዲያዎች ፎቶዎቹን ከማሰራጨታቸው በፊት የለቀቁትን ማስታወቂያ በመንተራስ የንጉሳውያን ቤተሰቡጠበቆች ለማሳገድ ያደረጉት ትግል ውጤታማ አልነበረም፡፡ ቻይ እና ክሎዘር ሞንዳዶሪ በሚባለውና የቤርልስኮኒ ሴት ልጅ በምታስተዳድረው የሚዲያ ኩባንያ የሚሰሩ ናቸው፡፡ክሎዘር 414ሺ ቻይ ደግሞ 340 ቅጂዎቻቸውን የሚሸጡ ናቸው፡፡ ኩባንያው ባተማቸው ፎቶዎች ጥፋተኛ ከሆነ የገንዘብ ቅጣት ሊገጥመው ቢችል ነው ያሉ የህግ ተንታኞች ለገበያ በቀረቡ ህትመቶቻቸው ያገኘው ገቢ ጉዳቱን ያካክሰዋል ብለዋል፡፡ የንጉሳውያኑን ቤተሰብ አነጋጋሪ ፎቶዎች አስቀድሞ ያተመው የፈረንሳዩ ክሎዘር በ26 ገፆቹ ሽፋን ሲሰጥ የጣሊያኑ ቻይ ደግሞ 40 ገፆች ሽፋን ሰርቶበታል፡፡ ዊልያም እና ኬት በሩቅ ምስራቅ ላለፉት 9 ቀናት የነበራቸውን ሽርሽር አጠናቀው በሳምንቱ መጨረሻ አገራቸው ይገባሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡
ከ15 አመታት በፊት የልዑል ዊልያም እናት የነበረችው ልእልት ዲያና ለህልፈት የዳረጋት የመኪና አደጋ የተከሰተው ፓፓራዚዎች ፎቶዋን ለማንሳት በፈጠሩት የሰዶ ማሳደድ ድራማ እንደሆነ ይታወሳል፡፡