Monday, 08 June 2026 15:12

በ2025 ከፍተኛ ወታደራዊ ወጪ ያደረጉ 5 የአፍሪካ ሀገራት

Written by 
Rate this item
(0 votes)
በ2025 የአፍሪካ ወታደራዊ በጀት በእጅጉ ጨምሯል፤ የአህጉሪቱ አምስት ከፍተኛ ወታደራዊ ወጪ ያደረጉ ሀገራት በክልላዊ ግጭቶች፣ በድንበር ውጥረቶችና ጦራቸውን ዘመናዊ ለማድረግ ባላቸው ፍላጎት የተነሳ ከ33 ቢሊዮን ዶላር በላይ ለደህንነት መከላከያ መድበዋል።
አልጄሪያ ከቀደመው ዓመት የ11% ጭማሪ በማሳየት 25.4 ቢሊዮን ዶላር በመመደብ መሪነቱን የያዘች ሲሆን፣ ይህም በሰሜን አፍሪካም ሆነ በአጠቃላይ በአህጉሪቱ ከፍተኛውን ወታደራዊ ወጪ ያደረገች ሀገር ያደርጋታል። ሞሮኮ በ6.6% ዕድገት 6.3 ቢሊዮን ዶላር በማውጣት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ፣ እነዚህ ሁለቱ የሰሜን አፍሪካ ሀገራት ለብቻቸው ከ90% በላይ የክፍለ-አህጉሩን የወታደራዊ ወጪ ድርሻ ይይዛሉ። ይህ የወጪ ጭማሪ በተለይም በምዕራባዊ ሰሃራ ዙሪያ ያለውን የቆየ ፉክክርና በሳህል እንዲሁም በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ ያሉ ሰፋፊ የደህንነት ስጋቶችን ያንጸባርቃል።
ከሰሃራ በታች ባለው አፍሪካ ደግሞ ናይጄሪያና የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ለወጪው መጨመር ዋነኞቹ ምክንያቶች ሆነዋል። ናይጄሪያ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ የመጣውን የአክራሪ ጥቃት ለመመከት የመከላከያ በጀቷን በ55% በማሳደግ 2.1 ቢሊዮን ዶላር አድርሳለች። በሌላ በኩል ኮንጎ ከኤም23 አማፂያን ጋር በነበረው ውጊያ ምክንያት የወታደራዊ ወጪዋን በ20% በመጨመር 1.2 ቢሊዮን ዶላር ያደረሰች ቢሆንም፣ በሀምሌ ወር ላይ የተኩስ አቁም ስምምነት ተደርጓል።
እንደ ስቶክሆልም ዓለም አቀፍ የሰላም ምርምር ተቋም መረጃ ከሆነ፣ በአጠቃላይ በአህጉሪቱ ያለው የወታደራዊ ወጪ በ2025 ወደ 58.2 ቢሊዮን ዶላር የደረሰ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ8.5% እንዲሁም ከ2016 ጀምሮ የ45% ጭማሪ አሳይቷል።
ይህ የወጪ መጨመር ከፍተኛ ክርክርና አነጋጋሪ ጉዳዮችን አስከትሏል፤ የአለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ጥናት እንደሚያሳየው፣ ከፍተኛ ወታደራዊ ወጪ ማድረግ በተለይም የውጭ ዕርዳታ ውስን በሆነባቸው አካባቢዎች ለጤና እና ለትምህርት ሊመደብ የሚችለውን በጀት ሊሻማና ሊቀንስ ይችላል።
Read 9047 times