በ5 ዓመት ውስጥ ለ300ሺ ዜጎች የሥራ እድል ይፈጥራል
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከሃይብሪድ ዲዛይንስ (ራይድ) ጋር ለአምስት ዓመታት የሚቆይ፣ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል የሚፈጥር የስራ ስምምነት ተፈራረሙ። ስምምነቱ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር የሚያስችልና ለአምስት አመት የሚቆይ መሆኑም ተመላክቷል።
በመድረኩ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል እንደገለፁት፤ በሃገር ደረጃ የስራ ዕድል ፈጠራን ለማሳዳግ በትኩረት እየተሰራ ነው። ይህ ስምምነትም ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር፣ የአገልግሎት ዘርፉን ከማዘመን ባሻገር ፍትሀዊ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የማይተካ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ስምምነቱ ሚኒስቴሩ በሚዘረጋው የስራ መስመር መሰረት በህጋዊ መንገድ ብዙ ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርግ ሲሆን፤ በሁሉም ክልሎች ስራ ላይ እንዲውል አቅጣጫ መውጣቱን ተናግረዋል።
የሃይብሪድ ዲዛይንስ (ራይድ) መስራችና ስራ አስፈፃሚ ሳምራዊት ፍቅሩ በበኩላቸው፤ ኩባንያቸው የስራ እድል ለመፍጠርና ስራ የለም የሚባለው ነገር እንዲቆም በርካታ ስራዎች እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። እስካሁን ለ120 ሺ ዜጎች የስራ እድል እንደተፈጠረ የገለፁት ስራ አስፈፃሚዋ፤ ይህ ስምምነትም በሚቀጥሉት አምስት አመታት 300ሺ ለሚሆኑ ወጣቶችና ሴቶች የስራ እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል።

