Print this page
Saturday, 20 August 2011 10:33

የኢትዮጵያ የረዳት ተዋናይነት.. ሚና በዓለም ታሪክ

Written by  ስብሃት ገ/እግዚአብዓሔር
Rate this item
(0 votes)

..ወንዝም ገነትን ያጠጣ ዘንድ ከኤደን ይወጣ ነበር፡፡ ከዚያም ለአራት ክፍል ይከፈል ነበር፡፡...የሁለተኛውም ወንዝ ስም ግዮን ነው፤ እርሱም የኢትዮጵያን ምድር ሁሉ ይከብባል..
(ኦሪት ዘፍጥረት ምእ.2 ቁ፡ 11-13)
የተከበራችሁ አንባብያን :-
የዛሬ ጽሑፋችን መዝናኛ ከመሆኑ ባሻገር፣ ፀሐፊውም አብዛኛው አንባቢም ሀገር ወዳድ ብቻ ሳንሆን ኢትዮጵያዊ የምንኮራ ዜጋዎች መሆናችንን ለመመስከር የተሰነዘረ ነው፡፡

የሶስት ሺ አመት ታሪክ ቀላል አይደለም፡፡ ከዚህም ጋር አንድ ስርወ መንግስት ከቀዳማዊ ምኒልክ አንስቶ እስከ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድረስ ሁለት መቶ ሰላሳ አምስት ነገስታት ሲያስቆጥር የመጨረሻው ንጉስ ደግሞ ስሙ የሥላሴዎቹ ሀይል ማለት ሲሆን በህይወት ዘመኑ እያለ በአምላክነቱ የተመለከ፣ ዛሬም ፣ Ras Tafarians በሬጌ ሙዚቃቸው ለመላው አለም  የሚሰብኩት   
ሲኒማ ውስጥ Supporting actor የሚባል ገፀባህሪ አለ፡፡ አንዳንድ ተዋናይ በረዳት ተዋናይነት Oscar ይሸለማል፡፡ ይኸውላችሁ እንግዲህ ኢትዮጵያችን በአለም ታሪክ መድረክ ላይ ዋና ዋናዎቹ ድራማዎች ላይ ረዳት ተዋናይ ሆና ስትጫወት እንከታተል፡፡
አንድ - የጥንታዊትዋ ግሪክ አማልክት የሰው ልጆችን ውጣ ውረድ ሲያስተዳድሩ አንድ   አመት በስራ ተጠምደው ካሳለፉ በኋላ፣ ሁለት ሳምንት አርፈው ለመመለስ ካገር ይጠፉ ነበር፡፡ Land of the Hospitable People እግዚአብሔር የቀባቸው እንግዳ ተቀባይ ህዝብ!
ሁለት - በአንድ ሺ አመተ አለም ጠቢቡ ንጉስ ሰሎሞን በኢየሩሳሌም ያሳነፀው ቤተመንግስት አለምን አስደነቀ፡፡ አክሱማዊቱ ንግስተ ሳባም እዚያ ደርሰው ከተመለሱ ነጋዴዎች ስለዚህ ቤተመንግስት ብዙ አወሩላት፡፡ እንዳይቀርባት ሄዳ እንድታየው ጐተጐቷት፡፡ የንጉስ ሰሎሞን ጥበብ ደግሞ ከቤተመንግስት እጅግ የላቀ መሆኑን ደጋገሙላት፡፡ ለመሄድ ወሰነች፡፡ ለመሆኑ ንግስተ ሳባ ማን ነበረች?
የአክሱምን ነገስት የሚያስገብር አንድ ዘንዶ ነበር፣ በዋሻ የሚኖር፡፡ በበአል ቀን ንፁህ ደናግል ወንዶችም ሴቶችም እንደ መስዋእት ይቀርቡለታል፡፡ በአዘቦት ቀን ግን በቀን አንድ ፍየል ይበቃዋል፡፡
አንድ ቀን አንድ ቁመናው ያማረ፣ ግርማ ሞገስ የተላበሰ እንግዳ መጣ፣ እግዜር እጁን ታጥቦ ከፈጠራት ወጣት ጋር፡፡ ንጉሱን ..አንጋቦስ እባላለሁ.. አላቸው ..ዘንዶውን ብገድልላችሁ፣ ከእርስዎ ቀጥሎ እቺን ልጄን ታነግሱዋታላችሁ?..
አሰቡበት፣ ተማከሩበት፡፡ ..እንቀበላለን.. አለ ..ግን ድንግልናዋን እስከጠበቀች ድረስ ብቻ ነው፡፡ አለዚያ እንሽራታለን፡፡.. ስምምነቱ በመሀላ ፀና፡፡
ከዘንዶው ዋሻ ሀምሳ ሜትር ያህል ርቆ አንድ ዛፍ አለ፡፡ እሱ ላይ ፍየል ይታሰርለታል፡፡ መሬት ለመሬት እየተምዘገዘገ መጥቶ ፍየሉን እየጐተተ ወደ ዋሻው ይገባል፡፡ አንጋቦስ እንዴት ገደለው? መልሱን ማግኘት እንደ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ፈልገን ፈልገን አናገኘውም፡፡ ከተነገረን በኋላ ግን ምን ያህል ቀላል እንደነበረ ሲታየን እንዴት ልንደርስበት እንዳልተቻለን ይገርመናል፡፡
አንጋቦስና ሰባት ጓዶቹ ቁመቱ አንድ ክንድ የሚያካክል ብዙ እንጨት ቆርጠው አስቀመጡ፡፡ እና ጫፍ ጫፉን እንዲዋጋ አድርገው አሾሉት፡፡ በሌሊት (ዘንዶው እንደተኛ) እንጨቶቹን ሹሉን ወደ ወሻው በር አነጣጥረው በሰያፍ ተከሉት፡፡
ጧት ዘንዶው ወደ ታሰረለት ፍየል እየተስገበገበ በተቻለው ፍጥነት ሲንፏቀቅ እንደ ካስማ የተዘጋጀለት የእንጨት ሰልፍ በሳስቶ ገደለው፡፡
አክሱም በደስታ ፈነጠዘች
ጊዜ አለፈ፡፡ አንጋቦስ ሞተ፡፡ የተዋዋለው ንጉስም ሞተ፡፡ ሳባ አንግሱኝ አለች፡፡  
ሽምጥጥ አርገው ካዷት፡፡
ሳባ ብቻዋን ወደ አባትዋ መቃብር ሄዳ መራር እንባ አነባች፡፡  
እና ከአንዱ የእንባ ጠብታ ያ አንጋቦስ የገደለው ዘንዶ ነብስ ዘርቶ ተነሳ፡፡ ከሀዲዎቹ መሪዎች በብዙ ምልጃ፣ በብዙ ካሳ ታረቁዋትና ይኸኛውን ዘንዶ እንድትገድልላቸው የአማልክቱን ስም ጠርተው ተማፀኑዋት፡፡ አባትዋ ባወረሳት ሰይፍ ቆረጠችው፡፡ ሊሞት ሲፈራገጥ አንድ ጠብታ ደም እግርዋ ላይ አረፈ፡፡ ያ እግርዋ (እዝጌር እጁን ታጥቦ የፈጠረው) ወደ አህያ ሰኮና (ኮቴ) ተለወጠ፡፡  
እስከዚህ ያነበባችሁት legend ይባላል፡፡ የብዙ አገሮች ታሪክ በሌጀንድ ይጀምራል፡፡ (የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት የነበረችው United States ግን ሰው ሰራሽ አገር ስለሆነች ያለፈ ሌጀንድ የላትም፣ የወደፊት ዘመናት ሌጀንድ ነው የሚኖራት፣ Space exploration (ህዋውን ማስሰ) ለምሳሌ “Star Trek” የሚባለው የቴሌቪዥን ተከታታይ ፕሮግራም፡፡   
ሶስት - ኢትዮጵያ በታሪካዊ ረዳት ተዋናይነትዋ Oscar የምትሸለምበት ታላቁ ተውኔት እንደሚከተለው ይነበባል (ፈጣሪ እንደፃፈው) ንግስተ ሳባ እኩያዋና የልብ ጓደኛዋ ምስጢረኛዋ የሆነች አገልጋይ ነበረቻት (በዘመኑ ቋንቋ ..ደንገጡር.. ትባለለች) ሁለቱም ተስማምተው ያንን አለም ያደነቀውን ቤተ መቅደስ ለመጐብኘትና የንጉሱንም ጥበብ ለማየት ወደ ኢየሩሳሌም አቀኑ፡፡ ተገቢውን ገፀ በረከት ይዘው፣ በየብስም በባህርም ተጉዘው ደረሱ፡፡  
የቤተ መንግስት የስነ ስርአት ሹም በንግስቲቱ ውበትና ግርማ እየተገረመ የቅጽር ግቢውን በር ከፈተላት፡፡ ልትገባ ደፉን ስትሻገር ያ የአህያ ሰኰና ተስፈንጥሮ ወደቀ፡፡ የእግርዋ ውበት ተመለሰላት፡፡ የዚህ ተአምር ምስጢሩ ምን ነበር? ቢሉ፣ ደፉ ተራ እንጨት አልነበረምና፣ የዚያች አዳምና ሄዋን የተከለከለ ፍሬዋን የበሏት እፀ በለስ የግንድ ቁራጭ ነበር እንጂ፡፡ ንግስተ ሳባን የንጉሱ ጥበብ ይህን ተአምር በመስራት ..እንኳን ደህና መጣሽ! ቤት ለአግዚአብሔር እንግዳ.. አላት፡፡ዘይገርም
ጠቢቡ ሁለቱን ውበቶች ተቀብሎ መሀላቸው እየተራመደ ኩሬ ተሻገሩ፣ በውሃው መስተዋት ሰሎሞን የሳባን ጭኖች አየ፡፡ እግዚአብሔር እጁን ታጥቦ የፈጠራቸው! ሳባ ሳይታወቃት በጭኖችዋ ትርኢት ተፈታተነችው፣ ፈተናውን ለመውደቅ ተጣደፈ! (..ውድቀቴን አሳምርልኝ.. እያለ በተንኰለኛ ልቡ)
መስተንግዶው ለሳምንታት ቀጠለ፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ሳባ ብዙ ቀለማት ባሏቸው ክሮች አበባዎችን በስፌት ፈጠረች፡፡ ቀድሞ ፈንድተው ከነበሩ አበባዎች ጋር አሰባጥራ ተከለቻቸው፡፡ ሰሎሞንን አምጥታ እያሳየችው ..እወቅ እስቲ.. አለችው ..የትኛዎቹ ናቸው የግዜር አበባዎች? የትኛዎቹስ ናቸው የኔ አበባዎች?..
..እስክመረምራቸው ጊዜ ያስፈልገኛል፡፡ እስከዘያው ድረስ አንድ ቁም ነገር ላናግርሽ መልካም ፈቃድሽ ይሁን..
..እሺ ደስ ይለኛል..
|እግዚአብሔር እሺ ይበልሽ ገና እንዳየሁሽ ፍቅር ያዘኝ፡፡ በዚህ አጭር ጊዜ ሳውቅሽማ ውስጤ እሳትና በረዶ ሆነልሽ ስሞትልሽ መላ በይኝ..
..ለሱ ለሱማ እኔም ገና አይኔ ሲያርፍብህ ነው ፍቅር የያዘኝ፡፡ ግን መላ እንዳልልህ የሚከለክለኝ በቂ ምክንያት አለኝ.. ብላ፣ የአንጋቦስንና የዘንዶውን ታሪክ ነግራ ..ድንግል ንግስት.. ሆና መኖር እንዳለባት ነገረችው፡፡
|እግዚአብሔር ሁለታችንን እንደተያያን ፍቅር ያስያዘን እንቁልልጭ ብሎ ኩም ሊያደርገን አይደለም  አላት |እግዚአብሔር ደግሞ ከፈሪ ከሀዲ ንጉስና ከመማክርቱና ከወራሾቹ የበለጠ እንደሚያውቅ እናውቃለን፡፡ ስለዚህ ላስጠንቅቅሽ፡፡ አብረሽኝ ሳታድሪ ከዚህ ግቢ አትወጪም..
..ልታስገድደኝ?..
|እግዚአብሔር ያውቃል፡፡ ጊዜው ሲደርስ የማደርገውን ያመለክተኛል፡፡ ወይም እምቢታሽን ወደ ውዴታ ይለውጥልኛል፡፡ ለሁሉም ጊዜ አለው..
ከአጭር ዝምታ በኋላ ..የአበባዎችሽን እንቆቅልሽ ልፍታልሽ?..
..ፍታልኝ.. ስትለው፣ የክር አበቦችዋን አንድ በአንድ ልቅም አድርጐ አሳያት
..እንዴት አወቅክ?.. አለችው እየተደነቀች
|yእግዚአብሔር ጥቃቅን በራሪ ነፍሳት ያንቺን አበባዎች ችላ ብለው የፈጣሪን አበባዎች ይጐበኛሉ፡፡ እያቸው፡፡ የእውቀት መጀመሪያ እግዚአብሔር መኖሩን ማወቅ ነው፡፡ የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔ መፍራት ነው.. እያለ ወደፊት ከሚደርሰው መጽሐፍ ጠቃቀሰላት፡፡
ወይ ፍንክች ሳባ ያባ ቢላዋ ልጅ በበርበሬና በሚጥሚጣ ያደገች ቆፍጣና የሀበሻ ልጅ...
...ሰሎሞንስ ቢሆን ምኑ ዋዛ ነው? ለራሱ ስንትዋን እቁባት ያግበሰበሰ ሴት አዋይ  ስውር ሴራ ¹rbƬ መጀመሪያ ከወጥ ቤቱ ጋር ተመሳጠረ፡፡  
አርብ የቀን tN÷l¾ ማታ ንጉስ ሰሎሞን፣ ለእንግዳው ለንግስተ ሳባ ክብር ግብር ጣለ፡፡
ምስጢረኛው ወጥ ቤት ለሳባና ለደንጉጡርዋ ብቻ የተሰራ፤ ጨው በጣም ቢበዛበትም ጣት የሚያስቆረጥም አሳ ጥብስ አቀረበላቸው፡፡ በወይን ጠጅ እያወራረዱ ኮመኮሙት፣ ምንም ሳያስተርፉ!
ወደ መኝታቸው ተሸኙ፡፡ የሚመስጡ ጨዋታዎች እያወራላቸው ወይን ጠጅ በላይ በላዩ እየቀዳላቸው ስላመሸ፣ ለመኝታ ሲጋደሙ ሞቅ ብሏቸዋል፡፡ እና ክፉኛ ጠምቷቸዋል፡፡ ቢመለከቱ ያ ሁልጊዜ ራስጌያቸው የሚያገኙት ውሃ ዛሬ የለም፡፡ አጠገባቸው ካለው ከንጉሱ መኝታ ቤት ውሃ ሰርቀው ማምጣት ነበረባቸው፡፡ እስካሁን ሳባ፣ ሰሎሞን እንዳጠመዳቸው ገብቷታል፡፡
መጀመሪያ ደንገጡርዋ በብዙ ጥንቃቄ ገብታ አየች፡፡ ንጉሱ በጀርባው ተጋድሞ ወደ ጣራው ያፈጣል፡፡ ተመልሳ ለሳባ ነገረቻት፡፡ እስኪተኛላቸው በአሰቃቂ ውሃ ጥም እየደረቁ ታገሱ፡፡
ሳባ ተራዋን እድልዋን ለመሞከር ሄደች፡፡ ተኝቷል! በልብዋ ተመስገን እያለች ወሃውን አንስታ ዥው አርጋ ጠጣች፡፡ እጁን ሰደደና ለቀም አደረጋት! (ጠቢቡ ሲያስፈልገው እንደ ቡዳ ያደርገዋል፡፡ ሲተኛ አይኑን ከፍቶ ነው፣ ሲነቃ አይኑን ጨፍኖ ያያል!
..ንብረቴን በመስረቅሽ እምቢ ያልሽኝን በካሳ መልክ አሁን እሺ ትይኛለሽ.. አላት በሹክሹክታ፡፡  
..ለዚች ለጥርኝ ውሃ?..
..እና ጥርኝ ውሀን የሚያህል ዋጋ ያለው ምን ንብረት አለሽ?..
..ምንም.. አለችና ድንግልዋን አስረከበች፡፡
ወደ መኝታዋ ስትመለስ ደንገጡርዋ ..ምነው ቆየሽ?.. አለቻት
..ሰውየው ካሁን ካሁን እንቅልፍ ይወስደዋል በሚል ከንቱ ተስፋ ነዋ..
ለነሱ የሰአታት ርዝመት ያላቸው ጥቂት ደቂቃዎች ካለፉ በኋላ ደንገጡር እድልዋን ለመሞከር ሄደች፣ ሳባ ላይ የደረሰው ጥቃት ደረሰባት፡፡
በዚያች የጨው ሌሊት ምኒልክና ዛጉዌ ተፀነሱ፡፡  ትግስትና ደንገጡር ተልእኮዋቸውን ፈጽመው ንጉስ ሲሸኛቸው፣ ለሳባ ቀለበት እየሰጣት ..ወንድ ልጅ የወለድሽ እንደሆነ፣ ሲያድግ ይህን ቀለበት ስጪውና ላኪልኝ.. አላት፡፡
አገራቸው በሰላም ደረሱ፣ ምኒልክና ዛጉዌ ተወለዱ፣ አብረው አደጉ፣ እንደ እናቶቻቸው የልብ ጓደኛሞች ሆኑ፡፡ አንድ ቀን ጐረምሶች የገና ጨዋታ ሲጫወቱ፣ ምኒልክ ስላሸነፈው የተናደደ ጐበዝ ድል አድራጊውን ..የሴት ልጅ.. ብሎ ሰደበው፡፡ ምኒልክ በጥፊ በቡጢ በክርን በእርግጫ አጣደፈዋ! ምንስ ቢሆን የአንጋቦስ የልጅ ልጅ አይደለም?
ቤት እንደገባ እናቱን ..አባቴ ማን ነው?.. ብሎ ጠየቃት፡፡ ለራሷ በትዝታ ..ለሁሉ ጊዜ አለው.. እያለች ታሪኩን በዝርዝር ከነገረችው በኋላ ሰሎሞን የሰጣትን ቀለበት ሰጠችው፡፡ ሳባና ደንገጡርዋ ስንቅ አዘጋጅተው ልጆቻቸውን ወደ ኢየሩሳሌም ሲሸኙዋቸው፣ ሳባ ልጅዋን ..አባትህ መልኩ ቁርጥ አንተን ነው የሚመስለው.. አለችው፡፡
አራት - ንጉስ ሰሎሞን ከኢትዮጵያ ሁለት ልኡላን መጥተዋል ሲሉት፣ ጮሌነቱ ተነሳበት፡፡ እናቶቻቸውን እንዳታለለ እነሱንም ለማሞኘት (ወይስ ለመታዘብ?) አቅዶ ከባለሟሎቹ አንዱን የገዛ ካባውን አልብሶ፣ ዘውዱን ደፋለትና ዙፋኑ ላይ አስቀመጠው፡፡ ንጉሱ የባለሟሉን ካባ ለብሶ ወንበሩ ላይ ተቀመጠ፡፡ ወንድማማቾቹ ሲገቡ፣ ዛጉዌ ወደ ዙፋኑ ተራምዶ
..ልጅህ ዛጉዌ ነኝ.. ብሎ ሳመው፡፡
ምኒልክ ግን እዚያ የነበሩትን መሳፍንትና መኳንንት በፈጣን አይን ከፈተሸ በኋላ አባቱን ለይቶ ሄዶ ..የሳባ ልጅ ምኒልክ ነኝ.. ብሎ ሳመው፡፡ ጠቢቡ ንጉስ ሁለቱን ልጆቹን ወግና ስነስርአት እና ይልቁንም የእስራኤልን ታሪክ፣ ሀይማኖት እና ባህል (ማለትም ኦሪትን) ሲያስተምራቸው ሁለት አመት እንደ ሁለት ሳምንት እየበረረ አለፈ......አንድ ቀን መሳፍንቱ፣ መኳንንቱ እና ሌሎች ባለሟሎቹ ንጉሱን እንዲህ አሉት ..ሺ አመት ንገስ መልካም ፈቃድህ ይሁንና፣ ሀሳባችንን ስማ፡፡ በነዚህ ሁለት ልኡላን ፍቅር ልብህ ጠፍቶ እስራኤልን የመጠበቅ ተግባርህን ችላ ብለሀል፣ ባትረሳውም፡፡ ስለዚህ በቅርብ ቀን ወደ አገራቸው እንድትልካቸው እናሳስብሀለን.. ..መልካም.. አለ ጠቢቡ ..እልካቸዋለሁ፡፡ እናንተም በበኩላችሁ እያንዳንዳችሁ የበኸር ወንድ ልጆቻችሁን ታዋጣላችሁ፣ yእግዚአብሔርN ቃል ወደ ሌላ አገር ወስደው ያስተምሩ ዘንድ..
በውሳኔው ሁሉም ተስማሙ፡፡ እነ ምኒሊክን ለማጀብ ከተመረጡት አንዱ የታቦቱ ባለ አደራ ጠባቂ የሳዶቅ ልጅ ነበረ፡፡ መሄዳቸው ሲነገረው ብልሀት መጣለት፡፡ ከሙሴ ሲተላለፍ የኖረውን ታቦት በሌላ ድንጋይ ላይ በጥንቃቄ ቀረፀ፡፡ ታቦቱን አንስቶ በቦታው ቅርፁን አኖረ፡፡ ይህን ለማንም አልተናገረም፡፡ እነምኒልክ ከአጀባቸው ጋር ቀይ ባህር ሲደርሱ ሳዶቅ የስርቆቱን ምስጢር ለምኒልክ ተናዘዘ፡፡ እና ..ተሳስቼ ከሆነ ታቦቱን ይዤ እንድመለስ እዘዘኝ.. ..ታቦቱ አብሮን መምጣት ባይፈልግ ኖሮ ገና እንደነካኸው አቃጥሎ ይገድልህ ነበር፡፡ ስለዚህ አብሮን እየጠበቀን ይጓዝ..በዚህ አኳኋን እቺ ቅድስታገር የእስራኤልን በረከት ወረሰች፡፡ ከአንድ ሺ አመት በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስን እስራኤላውያን ሰቀሉት፡፡ የቅድስታገር ልጆችም ..መስቀል ቤዛነ፤ መስቀል ሀይልነ፡፡ አይሁድ ክህዱ፣ ንህነሳ አመንነ.. ብለው ለእስራኤል የተላከውን በረከት ወረሱ፡፡
አምስት - አንባብያን ሆይ፣ የኢትዮጵያ ታሪካዊ best supporting actress ሚና ሲቀጥል፣ ወደ ኢየሱስ ሰአት እንደርሳለን፡፡
ሆነም፤ የኢትዮጵያ ንግስት ህንደኬ ጃንደረባ (ማለትም በሚቀጥሉት የአገልግሎት አመታቱ (ሴቶች እንዳያሳስቱት ታስቦ፣ ገና ለአቅመ አዳም እንደደረሰ የተሰለበ ሁነኛ አገልጋይ) ሀዋርያቱ የኢየሱስን ወንጌል በሚሰብኩበት ወቅት ለሀገር ጉዳይ ወደ ኢየሩሳሌም ተልኮ ነበረ፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ፣ ከአንዱ ሀዋርያ ጋር ባንድ ሰረገላ ተሳፍረው ሲጓዙ፣ ሀዋርያው የኢየሱስን ወንጌል (ማለትም የዘለአለም ህይወት የተለገሰልን መሆኑን የደስ ደስ የምስራች የሚነግረን ዜና) አስተማረው፡፡  
ውሀ ካለበት ቦታ ሲደርሱ ጃንደረባችን ሀዋርያውን ..በኢየሱስ ያመነ የተጠመቀም እንደሚድን አምናለሁ፡፡ አጥምቀኝ.. አለው፡፡ ተጠመቀ፣ ክርስትናን ይዞልን መጣ፡፡  
ስድስት - ነብዩ መሐመድ (ሰአወ) የተወለዱት The year of the Elephant  ባለፈ በአርባ አመቱ ነው፡፡ የአፄ ካሌብ ቀይ ባህርን ተሻግሮ በዝሆን ክፍለ ጦሩ አስደንጋጭነት ምክንያት ባጭር ጊዜ ውጊያ አኩሪ ድል መጐናፀፉን እናስታውሳለን፡፡ ወደ መካ - መዲና ታሪክ ስንመጣ፣ እስልምናን ከተቀበሉት መጀመሪያዎች አንዱ ቢላል የሚባል ኢትዮጵያዊ ባሪያ ነበር፡፡ ነብዩ (ሰአወ) ስለወደዱት በገንዘባቸው ገዙት፣ ነፃነቱን ሰጡት፣ አዛን እየጮኸ ..አላሁ xKbR´ እያለ ሙስሊሞችን ወደ መስጊድ የሚጠራቸው ሰው እሱ ሆነ፡፡ ..መረዋ ድምፁ.. ሲያምር፣ እጅግ ያስደስት ነበር ይባላል፡፡
yመጀመሪያãcÜN ሙስሊሞች ጠላቶች ሊፈጁዋቸው ሲሆን ጊዜ፣ ነብዩ (ሰ.አ.ወ) ወደ ኢትዮጵያ እንዲሸሹ አዘዙዋቸው፡፡ ነጃሺ የተባለው መሪ ተቀብሎ አስተናገዳቸው፣ እሱም ሰለመ፡፡...
...የተከበራችሁ አንባብያን
የጥንታዊት ግሪክ አማልክትን በማስተናገድ የተጀመረው የኢትዮጵያWÃN ዝነኛ እንግዳ ተቀባይነት፣ የእስልምናን ተከታዮች ተቀብለው ሲያስተናግዱ ያበቃል፡፡
ቸር ይግጠመን

Read 2532 times