Saturday, 10 December 2022 12:53

የኢትዮጵያ ሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት ኤክስፖ በአዲስ አበባ ይካሄዳል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

    5ኛው የኢትዮጵያ ሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት  ኤክስፖ በመጪው ታህሳስ 8 እና 9 ቀን 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስካይላይት ሆቴል እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡
በዚህ ኤክስፖ መጠነ-ሰፊ የሪል እስቴት መኖሪያ ቤቶች፣ አገልግሎቶችና አልሚዎች ለቤት ፈላጊዎች የሚቀርቡበት ነው  ተብሏል፡፡
ኤክስፖው ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ ከተሞች፤ በተለይም በአዲስ አበባ፣ የመኖሪያ ቤቶች ፍላጎት በከፍተኛ ደረጃ ባደገበት ወቅት የሚካሄድ መሆኑም ተጠቁሟል።
የዓለም ባንክ መረጃ እንደሚያሳየው፤ በመጪዎቹ ዓመታት የኢትዮጵያ የከተማ መሬትና የከተማ ህዝብ ብዛት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያድግ የሚጠበቅ ሲሆን ይህም ተጨማሪ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ይዞ ይመጣል ተብሏል።
“251 ኮሙኒኬሽንና ማርኬቲንግ” ፤ እያደገ ለመጣው የሪል እስቴት መኖሪያ ቤቶች ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት እንዲሁም ቤት አልሚዎችና ሸማቾች የሚገናኙበት መድረክ ለመፍጠር ባለፉት ዓመታት አራት ስኬታማ ኤክስፖዎችን ማዘጋጀቱን አስታውሶ፤ በእነዚህም መድረኮች ለመጀመሪያ ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችና ግንባር ቀደም የአገር ውስጥና ዓለማቀፍ  አልሚዎች በአንድ ጣራ ሥር መገናኘት መቻላቸውን አመልክቷል።
 የዘንድሮው 5ኛው የሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት አልሚዎች ኤክስፖ ታህሳስ 8 ቀን 2015 ዓ.ም የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ተጋባዥ እንግዶችና የሚዲያ አባላት በተገኙበት በስካይላይት ሆቴል በይፋ እንደሚከፈትም ታውቋል፡፡
ላለፉት አስርት ዓመታት ትላልቅ ዓለማቀፍ ኹነቶችን በማዘጋጀት የዳበረ ልምድ ያካበተው “251 ኮሙኒኬሽንና ማርኬቲንግ”፤ 5ኛውን የሪል እስቴትና መኖሪያ ቤት አልሚዎች ኤክስፖ ለማካሄድ ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡



Read 11757 times