ለአዲስ አመት ዋዜማ ታስቦ የነበረው ኮንሰርት፤ በጠ/ሚ መለስ ዜና እረፍትና በብሔራዊው ሀዘን ምክንያት እንደተራዘመ ይታወቃል።ለኮንሰርቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጅትና ልምምድ አድርገናል ያለው ቴዲ አፍሮ፤ የኮንሰርቱ መድረክ የኢትዮጵያን የስልጣኔ ታሪክና ቅርፅ አጉልቶ በሚያሳይ መንገድ ይገነባል ብሏል። እንደሌላው ጊዜ ሳይሆን፤ ኮንሰርቱ ሳይዘገይ በሰዓቱ እንዲጀመር እንጠነቀቃለን ብሏል። በኮንሰርቱ ከሚቀርቡ አዳዲስ ዘፈኖች መካከል “ወደ ፍቅር” የተሰኘ ይገኝበታል።ቂም ይዞ ማዝገሙ ላቃታት ሕይወቴሰተት ብለህ ግባ ንፁሕ ፍቅር ቤቴኦላን ይዤ አላፍርም ምን እጠብቃለሁወደ ፍቅር ልሂድ ምን እጠብቃለሁ(ኦላ ማለት ፈጣሪ ማለት ነው)ኮንሰርቱ፤ “ወደ ፍቅር” በሚል የተሰየመ ሲሆን፤ ከዚህ ጋር በማያያዝ፤ በሰርጉ እለት ከሰዓሊ ለማ ጉያ የተበረከተለትን ስጦታ ያስታውሳል። ካሁን በፊት የሰጡት ሥዕል፤ የአፄ ቴዎድሮስን ኃይለኝነትና ኮስታራነት፣ ጀግንነትና ቁጣ የሚያሳይ ነበር። በሰርጉ እለት ያበረከቱለት ሥዕል ግን የአፄ ቴዎድሮስን ትዕግስትና ሰላማዊነት ያሳያል። የሰላም ጊዜ ስለሆነ ጦራቸውና ጋሻቸው፣ ግድግዳ ላይ ተሰቅሏል። ነጭ የአገር ባህል ልብስ አድርገዋል። አጠገባቸው ካሉት ሁለቱ አንበሶች መካከል አንዱ በእርጋታ ተቀምጧል፤ ሁለተኛው አንበሳ እንደመቆጣት ሲያደርገው፣ አፄ ቴዎድሮስ በእጃቸው ያረጋጉታል። ሰዓሊ ለማ ጉያ “ጥሩ ምሳሌ ሰጥቼሃለሁ፤ ካንተ የሚጠበቀውም የፍቅርና የሰላም ስራ ነው” በማለት ትልቅ መልእክት አሸክመውኛል ብሏል ቴዲ አፍሮ ስለ ሰርግ ስጦታው ሲናገር። ሙሽራዬ የሚለው ዘፈን ምን ያህል እንደሚያስደነግጥ ያወቅኩት በሰርጉ እለት ነው የሚለው ቴዲ አፍሮ፤ የኔ ሕይወት ወደ አንድ ምዕራፍ ሲሸጋገር በማየት ከኔ ጋር እኩል የተደሰቱ አድናቂዎቼና አፍቃሪዎቼ በተለያዩ ቦታዎች ደስታቸውን ገልፀውልኛል፤ በጣም አመሰግናለሁ ብሏል።ለሙሽራዋ ለአምለሰት ሙሼ ያበረከተላት ስጦታዎችን በሚመለከት እንደ ስርዓቱና እንደ ዘመኑ አድርጌያለሁ ከማለት ያለፈ ለመናገር አልፈለገም። በግል የተሰጡትን ስጦታዎችም በአደባባይ መግለፅ ባይገልፅም፤ በእለቱ ስሜቱን ከነኩት ስጦታዎች መካከል ሁለቱን ጠቅሷል። አንዱ የእናቴ ስጦታ ነው፤ ግጥም ፅፋ ስታቀርብ በጣም ነበር የገረመኝ፤ ግጥም መፃፏን ማንም አልነገረኝም፤ አመሰግናታለሁ ብሏል። ሁለተኛው ስጦታ የሰዓሊ ለማ ጉያ ያበረከቱለት ስጦታ ነው። ከወዳጅ ዘመድ፣ ከሙያ ጓደኞችና ባልደረቦች፤ በአጠቃላይ አድናቂዎችና አፍረቃሪዎችን ማመስገን እፈልጋለሁ። ባለቤቱም የላቀ ስጦታ ልታበረክትለት ነው፤ የአራት ወር ነፍሰጡር ነች።