Monday, 16 May 2022 05:43

አንድ_ቤት

Written by 
Rate this item
(4 votes)

በምትነድ ሀገር ላይ አይኖርም እልልታ
ባዘነች እናት ቤት አይሰማም ፌሽታ
በስብሰባ ብዛት አያልቅም ስሞታ
ትናንትናን እንጂ ...........
ነገን አያውቀውም የዘፈን ትዝታ!

በረገፈ ጥለት - ላይደረብ ኩታ
ጥርስን ቢነቀሱት ...........
ውስጡን እያመመው አይስቅም ለአፍታ!
የሰው ልኩ ከብሮ ካልሞላ ሚዛኑ
ዓመት በዓል ተብሎ .....
ቢበላ ቢጠጣ መች ይደምቃል ቀኑ ?
-
ከልብ ካልፈለቀ .........
ከነፍስ ካልሸተተ የፍቅር እጣኑ
በርግጎ ካልወጣ የቤት ውስጥ ሰይጣኑ
-- እንደተካሰሱ
--- እንደተዋቀሱ
---- እንደተላቀሱ
----- እንደተቧቀሱ እንደተኳነኑ
ወንዝ ዳር ሲደርሱ
እንደ ተማማሉ
አንድ ቤት አይተኙም አዋቂና ህጻኑ ?
***

ደስ ይላል
እንደ ቀልድ አጫውቶ ጉም ደመና ሆኖ
<አለ!> ሲሉት ተንኖ የሚጠፋ በንኖ
ከእጅ እየጠፋ ከመዳፍ ውስጥ መክኖ
ጊዜ ጉድ አረገን በማያልቅ ተቃርኖ !
-
ከእግር የሚያዳልጥ የማይረጋ ጸንቶ
ሲረግጡት የሚያሰምጥ እንደ ውሃ ረግቶ
እድሜ ይሉት ተአምር ጊዜ ይሉት ጸጋ
ጤዛ ነው ርጋፊ የሰው መሆን ሥጋ !
-
<< የወዛ ፍካቱ የበዛ ድምቀቱ
እንደምን ረገፈ የዚያን ክንደ ብርቱ ?
የፀና ጉልበቱ ተፈትቶ ጅማቱ
ምን ነክቶት ታጠፈ ስንት ቻይ አንጀቱ ?
አስተዋይ ጥበቡ ድንቅ ብርቅ እውቀቱ
እንዴት ከአፉ ጠፋ ከርቱእ ከአንደበቱ?>>
ብሎ እየጠየቀ በቆላ በደጋ
መልሱን አነበበው
ቆዳው ተጨራምቶ
ዓይኑ አቅም አትቶ በለበሰው ሥጋ !
-
ወፌ ቆመች ብሎ የእናት እግር ይዞ
በእንግድግድ የቆመ ጉልበት ተመርኩዞ
አድጎ ከዘመን ጋር ሲላፋ ከኑሮ
ጊዜ ድል አረገው
እንደ ሰፈር ሩጫ እድሜውን አባርሮ !
-
እድሜ ሲያጃጅለው ሰው ዘመኑን ረስቶ
እሞታለሁ አይልም ..........
አፈር መሸከሙን ለሰከንድ ዘንግቶ!
-
ትከሻው ላይ አዝሎ ደረቱ ላይ ሰፍቶ
ክንዱ ላይ ተነቅሶ ነፍሱ ላይ አጣፍቶ
እየተተካካ ኡደቱን ጠብቆ
የመጣው ይሄዳል ቀን ወሩን ጠብቆ!
-
ካልቀረ መሄዱ ከዓለም ተገንጥሎ
ፍቅርን እንደ ችግኝ በሰው መንፈስ ተክሎ
ትዝታውን ቢተው ቅዱስ ስሙን ጥሎ
ማለፍ ደስ ያሰኛል
በልጆች ልብ ላይ አዲስ ቀለም ስሎ!
ነፃነት አምሳሉ አፈወርቅ

Read 2042 times