የሚሰዋ ፍቅር
ፍሬ ዛፍ ላይ እያለኮ፤ ቢበስልም እዚያው ላይ አይበላም
ፍሬ መልቀም የምንለው -
ሥራ እንዳለ ስናውቅ ነው፡፡
ምክንያቱም፡-
ያለ ስራ ፍሬ የለም
ያለ ስቅለትም ትንሳኤ
ያለ ትንሳኤም ስርየት
የስጋ ወደሙ ብስራት፡፡
በሂደት ነው ፍሬ ‘ሚበስል
እዛፍ ላይ አይበላም፡፡
ፍሬ በስሎ የሚበላው፡-
ወይ ራሱ በስሎ ሲወድቅ፤
ወይ እኛ ስንለቅመው ነው፤
አልያ ወድቀን መጠበቅ ነው፡፡
ትንሳኤ አይወድቅም ግና
የመስዋዕት ልብ ላለው
የሚሰዋ ፍቅር ላለው!
ትንሳኤ ሁሌ አይቀሬ ነው፡፡
(ነቢይ መኮንን፤ ግንቦት 2012 ዓ.ም)
Published in
የግጥም ጥግ