የደራሲ፣ ተዋናይት ፕሮዲዩሰርና ፀሀፊ እስከዳር ግርማይ ስራ የሆነውና በተለያዩ ኢትዮጵያዊያን ህይወትና ተግዳሮቶች ላይ የሚያወሳው “ኢትዮጵያዊ ሀገሩ የት ነው” መፅሐፍ አርብ ጥር 27 ቀን 2013 ዓ.ም ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ መገናኛ በሚገኘው ቤልቪው ሆቴል ይመረቃል፡፡
በዕለቱ በደራሲና ተርጓሚ ቴዎድሮስ አጥላው በመፅሀፉ ላይ ዳሰሳ የሚቀርብ ሲሆን፣ አሮጌ መፅፍት ሻጮች በክብር እንግድነት እንደሚጋበዙም ታውቋል፡፡ በሁለገቧ ከያኒ አዜብ ወርቁ በሚመራው በዚህ መድረክ ዶ/ር ምህረት ደበበ፣ መጋቢ ሀዲስ እሸቱ አለማየሁ፣ ደራሲና መምህር ሀይለመለኮት መዋዕል፣ ገጣሚና ደራሲ ታገል ሰይፉና የሜሪ ጆይ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ሲስተር ዘቢደር ዘውዴ ንግገር እንደሚያደርጉም ታውቋል፡፡ በዕለቱ ድምጻዊ ሀይለ እየሱስ ፈይሳ ከመረዋ የሙዚቃ ባንድ ጋር የሙዚቃ ስራ እንደሚያቀርብ የምርቃቱ አዘጋጅ ሰምና ወርቅ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን አስታውቋል፡፡
ደረሲዋ ከዚህ ቀደም “ሰውነቷ” የተሰኘ ፊልም ደራሲ፣ ተዋናይና ፕሮዲዩሰር እንዲሁም በጉዲፈቻ ላይ የሚያተኩረው “ጥቁር እንግዳ” ፊልም ተዋናይና ፕሮዲዩሰር ስትሆን በባህሬን ለህዳሴው ግድብ ገንዘብ በማሰባሰብና በባህሬን የሚካሄዱ የፋሽን ትርኢቶች ላይ በዲዛይነርነት ስትሳተፍ መቆየቷም ተገልጿል፡፡
Published in
ኪነ-ጥበባዊ ዜና