Error
  • JUser: :_load: Unable to load user with ID: 62
Print this page
Monday, 10 September 2012 14:39

ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊና ቀ/ኃ/ሥ በሽልማት ዙሪያ

Written by 
Rate this item
(0 votes)

ዶክተር ዩን - ፕዮ ሺን የሐናም ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት (ኮሪያ) የእንኳን ደስ አለዎ ደብዳቤ

የዓለም ሰላምንና ዕርቅን በመላው ዓለም ለማስፋፋት የዓለም የሰላም ጓድ (World peace Corps) ያደረገውን ክቡር ጥረት መሠረት አድረጌ የኢትዮጵያ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የዓለም ሰላም የክብር ተሸላሚ ሆነው በመመረጣቸው ከልብ እንኳን ደስ አለዎ እላለሁ፡፡ …ደከመኝ ታከተኝ በማይል የክርስቲያን ጽኑ መንፈስ ህይወታቸውን በ”ሙሉ ለሰላምና ለፍትሕ ላገለገሉት ለአቶ መለስ ዜናዊ ይህ ሽልማት ልዩ ትርጉም እንደሚሰጣቸው እርግጠኛ ነኝ፡፡ የዓለም የሰላም ሽልማት የሚሰጠው የሰላምን ዘር በዓለም ዙሪያ ለመዝራት ከሃይማኖት፣ ከዘር ወይም ከፖለቲካ ነፃ የሆነ መልካም ተግባር ለፈፀሙ ግለሰቦች ነው፡፡

የዓለም ሰላም ሽልማት ድርጅት የተቋቋመው የዓለምን ሰላም ሠረት ለመጣል የጥላቻና የባላንጣነት ግድግዳ ማፍረስና በየአካባቢያችን ሰላምን ማገልገልና ለሰላም መሥራት አለብን፡፡

በዚህ አንፃር የመለስ ዜናዊን የክብር ሽልማት ውሳኔ እንደተገቢና ተፈጥሮአዊ ነገር አድርጌ ነው የምቆጥረው፡፡

እንደገና እንኳን ለ2002 የዓለም ሰላም ሽልማት አበቃዎት ልል እወዳለሁ፡፡

የአምላክ በረከት በርስዎ ላይ ይረፍ፡፡ በዚህ ሽልማት አማካኝነትና በተቀባዩም ክቡር ጥረት የአለም ሰላምና ህብርነት ወደተሻሻለ ደረጃ እንዲያድግ እፀልያለሁ፡፡

በመጨረሻ መለስ ዜናዊ ይህን የክብር የፖለቲካ ሳይንስ ዶክትሬት ዲግሪ በማግኘትዎ እንኳን ደስ አለዎት እላለሁ፡

የጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሽልማት

(ጠ/ሚኒስትር መለስ በተሸለሙበት ወቅት ካደረጉት ንግግር በከፊል የተቆነፀለ፡፡)

“…ሰላምን ማግኘት በረከት የማይሆንለት አገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ሆኖም ከአፍሪካ ህዝቦች የበለጠ ይህን በረከት የሚፈልግ ያለ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱ ግልጽ ነው፡፡ የኢኮኖሚ ሁኔታችንና የምንኖርበት የድህነት ህይወት ሁሉንም ያስረዳልና!

በዚህ ረገድ ለማንኛውም የአፍሪካ አመራር በሰላምና በጦርነት ጉዳይ ላይ መወሰን የጭንቅ የምጥ አጣብቂኝ ይሆንበታል፡፡ ይህ ውሳኔ ጦርነት በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ከሚያደርሰው ጥፋትና ውድመት ባሻገር ለአንድ የተራበ ህፃን ቁራሽ ዳቦ በማግኘትና በጥይት መካከል የመምረጥ ጥያቄን ያስከትላሉ፡፡

ከዚህ አንፃር ለህዝባችን የገባንለትን ቃል አለማጠፋችንን በንፁህ ህሊና ስናገር በመንግስት ስም ኩራት ይሰማኛል፡፡

በተቻለንም አቅም ሁሉ ሰላምን ለማስፈን የተገኘውን አጋጣሚ ሁሉ ለመጠቀም ሞክረናል፡፡ እውነቱን ለመናገር ፖለቲካ፣ ዲፕሎማሲና ዓለምአቀፍ ግንኙነቶች ሁሉ እንዳሉ እያሉ ለአንድ ለተራበ ህፃን ቁራሽ ዳቦ በማግኘትና በጥይት መካከል የመምረጥ ጥያቄ ሲባል ርህራሄ አልባነት ይመስላል፡፡ ሆኖም ጉዳዩ ሁሌ ቀላል ሆኖ አይገኝም፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ አጋሮቻቸው ትክክለኛውንና ተገቢውን ምርጫ እንዳያደርጉ እንቅፋት የሚሆኑ ወገኖች ይኖራሉ፡፡

ሰላም በፍላጐትና በምኞት ብቻ የሚገለፅ አይደለም፡፡

ሰላም ይሰፍን ዘንድ ተባባሪ አጋር ይፈልጋል፡፡ ሰላም እንዲኖርና እንዲጠበቅ አጋር አለመኖሩ (አለመገኘቱ) አንዱ ችግር ሲሆን…ከዚህም በላይ እጅግ አስጨናቂውን ውሳኔ የሚወስኑ ወገኖች ዲፕሎማሲ በሀሰት የማስመሰያ መድረክ ለከመሆኑንና አለም አቀፍ ህጉም ጠባቂ ዘብ እንደሌለው የሚገነዘቡበት ሁኔታ መከሰቱ ነው፡፡

በዚህ አንፃር የኢትዮጵያ ህዝብ ለአመታት ቅር መሰኘቱ ጥርጥር የለውም፡፡ ያም ሆኖ በማናቸውም የችግርና የመከፋት ጊዜ እንዳደረገው በትዕግሥትና በሀሞተ መራርነት ለሰላም ያለውን ጽናት አረጋግጧል፡፡

…ህዝብ ሰላምን ይፈልጋል ብሎ ማሰብ ምንም አደጋ አያስከትልም፡፡ መንግሥታትም ይፈልጋሉ የሚለው ግን ሁልጊዜ አያዋጣም፡፡

…ምክር ቤቱ በዚህ ሽልማት አማካኝነት የኢትዮጵያ ህዝብ ለሰላም ያለውን ጽናት በማረጋገጡና እውቅና ሰጥቶ አብሮ በመቆሙ አድናቆቴን ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡

ስም :- መለስ ዜናዊ

የትውልድ ቀን :- ግንቦት 8,1955 (እኤአ)

የትውልድ ሥፍራ:- አድዋ ትግራይ ሰሜን ኢትዮጵያ

የጋብቻ ሁኔታ:- አግብተዋል ሦስት ልጆች አሏቸው

የትምህርት ሁኔታ

የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት :- ንግስት ሳባ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት፣ አድዋ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት:- ጄኔራል ዊንጌት ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት፣ በ1972 በከፍተኛ ማዕረግ አጠናቀቁ፡፡

ዩኒቨርሲቲ:- ህክምና ፋከሊቲ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ጥቅምት 1974 የሁለተኛ ዓመት ተማሪ ሳሉ ዩኒቨርሲቲውን ለቀው ከትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር ጋር ተቀላቀሉ፡፡

ከእንግሊዝ አገር ኦፕን ዩኒቨርሲቲ በተልዕኮ MBA አገኙ፡፡ በአሁኑ ሰዓት ለማስትሬታቸው በኢኮኖሚክስ ማኔጅመንት በተልዕኮ እየተማሩ ይገኛሉ፡፡

ፖለቲካዊና ሙያዊ ተሳትፎ

1974:- ከትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር ጋር ተቀላቀሉ

1979:- የትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ሆኑ

1983:- የትግራይ ህዝብ ነፃነት ግንባር ፖሊት ቢሮ አባል ሆኑ

1989:- የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲ ግንባር ሊቀመንበር ሆኑ

1991-1995 የኢትዮጵያ የሽግግር መንግስት ፕሬዚዳንትና የተወካዮች ምክር ቤት ሊቀመንበር ከላይ በተጠቀሱት ግንባሮች የነበራቸው ኃላፊነት እንደተጠበቀ ሆኖ ከ1995 ጀምሮ - የፌዴራል ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር በዓለም አቀፍና በአህጉራዊ ደረጃ ያደረጉት እንቅስቃሴ

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአፍሪካ አንድነት ድርጅትና ከኢጋድ በተሰጣቸው ማንዴት መሠረት በሶማልያ ብሔራዊ እርቅ ሂደት ላይ የላቀ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡ በሱዳን የነበረውን ግጭት ለማቆም በኢጋድ በተደረገው ጥረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡ በግሬት ሌክስ ኤርያ የነበረውን ቀውስ ለመፍታት በተደረገው የአፍሪካውያን ጥረት ውስጥ ተሳትፈዋል፡፡

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሊቀመንበር በመሆን እ.ኤ.አ ከሰኔ 1995 እስከ 1996 ሰርተዋል፡፡

የግርማዊ ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ የክብር ዶክትሬት

ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የሃያ የዓለም ዩኒቨርሲቲዎችን የክብር ዶክትሬት ተሸላሚ ነበሩ፡፡ እነዚህም የሕግ፣ የፈትሐብሔር ህግ፣ የእርሻ፣ የሥነጽሑፍና የፍልስፍና የክብር ዶክትሬትነት ማዕረጐች ናቸው፡፡

ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ከኬምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ሐምሌ 11 ቀን 1916 ዓ.ም የሕግ ዶክተርነት ሲቀበሉ በኬምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ስለ ልዑል አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን የተነገረ፡፡

ልዑል ሆይ

ባለቅኔው ሆሜር የኢትዮጵያ ሰዎች ነውር የሌለባቸው ናቸው ብሏል፡፡ ሄሮዱተስም የኢትዮጵያ ሰዎች ፈጽሞ የወይን ጠጅ አይጠጡምና ዕድሜያቸው ረዥም ነው ብሏል፡፡

የኢትዮጵያ ሰዎች ለካምባይሰሰና ለፋርስ ግብር አንገብርም ማለታቸው ርግጥ ነው፡፡

ከዚያም በኋላ ማንንም ሀገራቸውን ለመውሰድ የመጣውን ሁሉ እንዳይገባ ከለከሉት፡፡ ይህንም ሁሉ ካደረጉ በኋላ አሳባቸው ሁሉ ነጻነታቸው እንዳይነካ ነው፡፡

የሳባ ንግሥት የሰሎሞንን ዝና ሰምታ ሽቶና ቅመም ወርቅና አልማዝ ይዛ ሰሎሞንን በዋና ጥያቄ ለመፈተን በግመል እንደመጣች የማያውቅ ማነው፡፡

የነገሥታትስ ሁሉ እናት ትሆን ዘንድ ወደ ሀገሬ እንደተመለሰች የማያውቅ ማነው፡፡

ምንስ ዘመኑ ቢበዛ ከዳዊት ዘር መሆናቸውን የማያስብ ማን ነበር፡፡ የንግሥት ክንዳሲስ ወገን መሆናቸውን የማያውቅ ማን ነበረ፡፡

ይህም ሁሉ ክርስቲያንነታቸውን በሙሉ ኢትዮጵያ እንደ መሠረቱ የቀድሞ እምነት የብዙ ዘመን ታሪክ እንዳላቸው ያስረዳልና፡፡

የኢትዮጵያውያንን መጻሕፍትና የሕግ መጻሕፍታቸውን ባለፈው ዓመታት በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ በክርስቶስ ኮሌጅ የተማረ አንድ ሰው ለእንግሊዞች ገለፀው፡፡

አሁንም ዛሬ የኢትዮጵያ መንግሥት አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን መካከላችን አሉ፡፡ እርሳቸውም የቀድሞ ያባቶቻችንን መንገድ ይዘው የሚከተሉት ከምሥራቃውያንና ከግብጻውያን ይልቅ ዕውቀት ያላቸው ናቸው፡፡

የቀድሞውንም የዛሬውንም ጥበብና ዕውቀት ይመረምራሉ፡

የቀድሞውን የክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ መርምረዋል፡፡ አዲሱንም ዕውቀት ለማግኘት ይጥራሉ፡፡

ከኢትዮጵያ የመንግስት አልጋ ወራሾች በመጀመሪያ ወደ አይሮፕላን ላይ የወጡ ልዑል ተፈሪ መኮንን ናቸው፡፡

ደግሞ የዮሐንስ አፈወርቅን የማር ይስሐቅን መጻሕፍት ከግእዝ ቋንቋ እያስተረጐሙ በገዛ ማተሚያቸው አሳትመዋል፡፡

እነዚህም መጻሕፍት በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ በመጻሕፍት ቤት ይገኛሉ፡፡

ከዚህም በቀር ለኢትዮጵያ ልጆች መመሪያ እንዲሆን ትምህርት ቤት ሠርተዋል፡፡ ስለዚህ ትልቁን የኢትዮጵያ መንግሥት አልጋ ወራሽና እንደራሴ ከጥንት ዘር የመጡትን የኢትዮጵያን ተስፋ ተፈሪ መኮንንን እናስተዋውቃችኋለን” ብሎ ጨረሰ፡፡ የልዑል አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኮንን መልስ

ክቡር ሆይ

ለልዩ ልዩ ሕዝብ የዕውቀትና የጥበብ ምንጭ የሚመነጭበትን የካምብሪጅን ዩኒቨርሲቲ በማየቴ እጅግ ደስ ብሎኛል፡፡

እናንተም በታላቅ ደስታና በልብ ፍቅር አክብራችሁ ስለተቀበላችሁኝ አመሰግናችኋለሁ፡፡

ይልቁንም ደግሞ የኢትዮጵያን ነፃነትና የኢትዮትያን ክርስቲያንነት ከብዙ ዘመን አስቀድሞ መሆኑን አስረድታችሁ ታሪኳን በመናገራችሁ ደስታዬ ከልክ ያለፈ ሆነ፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት በጣም ቀደምትነት እንዳላትና ከተመሠረተች ረዥም ዘመን እንደሆነ የማያውቁ ምናልባት አንዳንድ ሰዎች ይኖራሉ፡ ነገር ግን ታሪኳን በጣም ቢመለከቱ ከግብጻውያንና ከሮማውያንም አስቀድማ ፀንታ የኖረች መሆኗን ለመረዳት ይችሉ ነበር፡፡ በዳዊትና በሰሎሞን ዘመን እንኳ በጣም የታወቀች መንግሥት ነበረች፡፡

ነገር ግን በዘመን ብዛትና በመንገድ ርቀት እስካሁን ከአውሮጳ መንግሥቶች ጋራ በጣም ሳትቃረብ በመቆየቷ እጅግ እናዝናለን፡፡

አሁን ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ጥቂት በጥቂት እያለች ለመቃረብና ለመገናኘት ደረሰች፡፡ ባለፈውም ዓመት ወደ መንግሥታት ማህበር ስለገባች በጣም ለመቃረብ እንደተመቻት ያስረዳል፡፡

ደግሞ የኢትዮጵያን ልጆች በአውሮጳና በሌሎችም ስፍራዎች ለትምህርት ስለ ሰደድናቸው እነርሱም ለትምህርታቸው በጣም ስለተጉ ከጥቂቶች ዘመናት በኋላ የዩኒቨርሲቲ ትምህርት ለመማር ወደ ካምብሪጅ እንዲመጡና ወደ ሀገራቸው ተመልሰው መንግሥታቸውን እንዲያገለግሉ በሙሉ ተስፋ አደርጋለሁ ብለው ጨረሱ፡፡

 

 

Read 2685 times Last modified on Monday, 10 September 2012 14:47

Latest from