Monday, 27 September 2021 13:37

3 ጊዜ በዕድሜ ልክ እስራት የተቀጣው ካርሎስ ቀበሮው እስሩ እንዲቀነስለት ተማጸነ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 ሶስት ጊዜ የእድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት በፈረንሳይ በእስር ላይ የሚገኘውና ከአለማችን ጨካኝ ወንጀለኞች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ቬንዙዌላዊው የ71 አመት ገዳይ ካርሎስ ቀበሮው፣ ከሰሞኑ በፈረንሳይ ለሚገኝ ፍርድ ቤት ባቀረበው አቤቱታ የእስራት ዘመኑ እንዲቀነስለት መማጸኑን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ካርሎስ ቀበሮው በሚል ስሙ የሚታወቀውና እ.ኤ.አ በ1974 በፓሪስ በሚገኝ የገበያ ማዕከል በፈጸመው ጥቃት ከ4 አመታት በፊት የዕድሜ ልክ እስራት ተፈርዶበት በእስር ላይ የሚገኘው ኢሊች ራሚሬዝ ሳንቼዝ፣ ባለፈው ረቡዕ ለፍርድ ቤት ባስገባው ማመልከቻ እስሩ እንዲቀንስለት መማጸኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ከአራት አመታት በፊት የዕድሜ ልክ እስራት በተፈረደበት ችሎት ላይ ሲቀርብ የሙያ መስክህ ምንድን ነው በሚል ከችሎቱ ለቀረበለት ጥያቄ፣ ብቁ አብዮተኛ ሲል ምላሽ መስጠቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ዕድሜውን ሲጠየቅም 17 ነው፤ ደስ ካላችሁ 50 አመት ጨምሩበት ሲል ማላገጡን አስነብቧል፡፡
ከ27 አመታት በፊት በፈረንሳይ ልዩ ሃይል ክትትል በካርቱም በቁጥጥር ስር የዋለው ቬንዙዋላዊው አደገኛ ገዳይ ካርሎስ፤ በ1970 ዎቹ እና 80 ዎቹ በፈጸማቸውና ባስፈጸማቸው በርካታ የግድያ ወንጀሎች ለሶስት ጊዜያት የእድሜ ልክ እስራት እንደተፈረደበትና ከዚያ ጊዜ አንስቶ በፈረንሳይ በእስር ላይ እንደሚገኝም ዘገባው አስታውሷል፡፡


Read 1819 times