የደቡብ አፍሪካው የብሮድካስት ኩባንያ መልቲ ቾይዝ በዲኤስቲቪ ኔትዎርክ 8 አዳዲስ የፊልም ቻናሎችን ከወር በኋላ እንደሚለቅ አስታወቀ፡፡ አዳዲስ ቻናሎቹ በጣቢያው የሚሰራጩትን ፊልሞች አይነትና ብዛት ለማሳደግ ተብለው መጨመራቸውን የገለፀው ኩባንያው ለደንበኞቹ ሰፊ የምርጫ እድል ለመስጠት በማቀድ ለውጥ መደረጉን አስታውቋል፡፡ በዲኤስቲቪ የተጨመሩት ስምንቱ የፊልም ቻናሎች በተለያዩ ዘውጎች ትኩስ እና አዳዲስ ፊልሞች የሚቀርብባቸው ሲሆኑ ለአክሽን፤ ለኮሜዲ እና ለቤተሰብ የፊልም ዘውጎች የየራሳቸው ቻናል እንደሚኖራቸው ይጠበቃል፡፡በሃይዴፍኔሽን ስርጭት የሚኖራቸው የፊልም ቻናሎች ብዛት አዲስ ከሚጀመሩት ጋር ወደ 14 አድጓል፡፡ በተመሳሳይ ወቅት ጣቢያው በኤምኔት ሁለት የአፍሪካ ማጂክ ቻናሎች ስርጭት ይጀምራሉም ተብሏል፡፡ መልቲ ቾይዝ አዳዲስ ቻናሎችን ለመክፈት የወሰነው ኢንተርሳት አይኤስ20 የተባለችውን እና የ15 አመት እድሜ ያላትን የማሰራጫ ሳተላይ ወደ ጠፈር ካመጠቀ በኋላ ነው፡፡