ሥርዓተ ቀብራቸው ነገ በቅድስት ሥላሴ ደብር ለሚናወነው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ መታሰቢያ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች መቅረብ ጀመሩ፡፡ ከትናንት ወዲያ ምሽት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር ተከፍቶ እስከ ዛሬ በሚቀጥለው ከዘጠኝ የኪነጥበባት ማህበራት የተውጣጡ ባለሙያዎች ጠቅላይ ሚኒስትሩን የሚዘክሩ ዝግጅቶች እያቀረቡ ነው፡፡ ጋዜጠኞች እና ሌሎች የኪነጥበብ ባለሙያዎች ከነዚሁ አርቲስቶች ጋር በመሆን ረቡዕ ረፋዱ ላይ በብሔራዊ ቤተመንግሥት በመገኘት ሀዘናቸውን መግለጣቸው ይታወቃል፡፡ሐሙስ፣ አርብ እና ዛሬ በሚቀርበው ዝግጅት ከሚካተቱት መካከል በደበሽ ተመስገን እና ሽመልስ አበራ ጆሮ የሚቀርብ መነባንብ፣ በሰራዊት ፍቅሬ ተፅፎ ጥላሁን ጉግሳ ያዘጋጀው ‘ማስታወሻ’ የተሰኘ ድራማ፣ በፈለቀ አበበ እና እንዳለጌታ ከበደ ተፅፎ ደጀኔ ሃይሉ በኬርዮግራፈርነት የሰራበት 80 ወጣቶች አሳታፊ ሙዚቃዊ ድራማ ይገኙበታል፡፡ ዝግጅቱን ባህልና ቱሪዝም ሚኒስትርና አሚን አብድልቃድር ባስጀመሩት የሻማ ማብራት ሥነ ሥርዓት እና የሕሊና ፀሎት ነበር የተጀመረው፡፡