30ኛው ኦሎምፒያድ ከተከፈተ ሳምንት ቢያልፈውም ኢትዮጵያውያን ኦሎምፒያኖች የሚደምቁበት የአትሌቲክስ ውድድር ትናንት ተጀመረ፡፡ በ800ሜ፤ በ1500ሜ፤ በ3ሺ መሰናክል፡ በ5ሺሜ፤ በ10ሺሜ እና በማራቶን ውድድሮች በሁለቱም ፆታዎች ለቀረቡ ሜዳልያዎች አሸናፊነት ከፍተኛውን ግምት የወሰዱት ኬንያ እና ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ ከ4 ዓመት በፊት ቤጂንግ ላይ በተለይ በአትሌቲክስ ውድድሮች ኢትዮጵያና ኬንያ በሰበሰቧቸው ሜዳልያዎች ከ1 እስከ 5 በተሰጠው የአለም አገራት ደረጃ ነበሩበት፡፡ ኬንያ በ14 ሜዳልያዎች (6 የወርቅ፤ 4 የብርና 4 የነሐስ) ስብስብ ከአሜሪካ እና ከራሽያ በመቀጠል ሶስተኛ ደረጃ ነበራት፡፡ ኢትዮጵያ 7 ሜዳልያዎች (4 የወርቅ፤ 1 የብርና 2 የነሃስ) አግኝታ 4ኛ ደረጃ ከነበረችው ጃማይካ በመቀጠል 5ኛ ደረጃ ላይ ነበረች፡፡የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ በለንደን ኦሎምፒክ 12 ሜዳልያዎች (4 የወርቅ፤ 4 የብርና 4 የነሐስ) አቅዷል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ትንበያዎች ደግሞ ለኢትዮጵያ የተገመተው 3 እና አራት የወርቅ ሜዳልያዎች እንዲሁም በአጠቃላይ 8 ሜዳልያዎች ነው፡፡