በአዲሱ ዓመት የሚቀርበው “ከለርስ ኦቭ ዘ ናይል ዓለምአቀፍ የፊልም አውደርእይ” አካል እንደሆነ የተነገረለት የኢትዮ ሲኒማ የግማሽ ቀን አውደ ጥናት ዛሬ ይካሄዳል፡፡አውደ ጥናቱን ብሉ ናይል የፊልም እና ቴሌቪዢን አካዳሚ ከኢትዮጵያ ፊልም ሰሪዎች ማህበር ጋር በመሆን ያሰናዱት ሲሆን የሚቀርበውም ካዛንቺስ በሚገኘው ጁፒተር ዓለምአቀፍ ሆቴል ነው፡፡ ሆቴሉ የዝግጅቱ ስፖንሰር እንደሆነም ታውቋል፡፡ ባለፈው ሰኔ 8 ቀን 2004 ዓ.ም ለፊልም ባለሙያዎችና ከኢትዮ ሲኒማ ጋር በተባባሪነት ይሰራሉ ተብለው ለሚጠበቁ ባለሀብቶች በኩሪፍቱ ዲፕሎማት ላውንጅ የመተዋወቂያ ስብሰባ መካሄዱ ይታወቃል፡፡ ኢትዮ ሲኒማ በከፍተኛ ፈጠራ እና ጥራት ዓለምአቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ተወዳዳሪ እና ትርፋማ የኢትዮጵያ ፊልም ኢንዱስትሪን ለመገንባት ያለመ መሆኑን የ”ከለርስ ኦቭ ዘ ናይል አለምአቀፍ የፊልም አውደርእይ” ፕሬዚዳንት አብርሃም ኃይሌ ብሩ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡