አራት ኪሎ ዳግማዊ ምኒሊክ መሠናዶ ት/ቤት ግቢ የሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት የዘንድሮ ተመራቂ ተማሪዎች የሥዕል ሥራዎቻቸውን አውደርእይ ለሕዝብ አሳዩ፡፡ አውደርእዩ የቀረበው ከትናንት በስቲያ በትምህርት ቤቱ ቅጽር ግቢ ሲሆን እ.ኤ.አ ሴፕቴምበር 30 ድረስ ይቆያል፡፡ ትምህርት ቤቱ የሚያስመርቃቸው 18 ተማሪዎች የሚያቀርቡት አውደ ርእይ ሲጠናቀቅ ሥዕሎቹና ሌሎች የሥነ ጥበብ ሥራዎች የትምህርት ቤቱ ንብረት እንደሚሆኑም ለማወቅ ተችሏል፡፡ ተማሪዎቹ የሚመረቁት በቀለም ቅብ፣ ሥነ ቅርጽ፣ ግራፊክስ፣ ኢንዱስትሪያል ዲዛይን እና በሥነጥበብ መምህርነት የትምህርት ዘርፎች ነው፡፡