ባለፈው መጋቢት ወር ግን ግጭታቸው ከረር ያለ ስለነበር አቶ ዘላለም ለአራት ወራት ወደ ቤቱ ሳይመለስ እንደቀረ ተናግራለች - ሶሎሜ፡፡ ወ/ሮ ወርቅነሽ ህጋዊ ፍቺ ለመጠየቅ አስባ እንደነበርና ልጆቿም እናቷ ጋር እንደነበሩ የጠቆመችው ሶሎሜ፤ ሰኔ 30 ቀን 2004 ዓ.ም ከምሽቱ አንድ ሰዓት ላይ ወ/ሮ ወርቅነሽና ልጆቿ እንዲሁም እናቷ አክስቷ ቤት ተሰባስበው እንደነበር ትናገራለች - ማህበር ስለነበር፡፡ ይሄኔ ነው አቶ ዘላለም የወርቅነሽ አክስት ወ/ሮ ገነት ተዘራ ቤት ዘሎ በመግባት “መግደል የምፈልገው አንቺን ነው” በማለት ሽጉጥ አውጥቶ ሚስቱን ደረቷ ላይ ተኩሶ የመታት፡፡ በሚስቱ ብቻ ግን አልበቃውም፡፡ እራሳቸውን ለማዳን በምጣድ ስር ተከልለው የነበሩትን የወርቅነሽ እናት ወ/ሮ የክቴ ተዘራንም ተኩሶ ገድሏቸዋል፡፡ ከዚያም ወደ ወርቅነሽ አክስት ወ/ሮ ገነት ተዘራ ዞረ - እሳቸውንም ደረታቸውና ጀርባቸው ላይ በመምታት ገደላቸው፡፡ የሦስቱን ሰዎች ህይወት ያጠፋው አቶ ዘላለም፤ በመጨረሻም የያዘውን ሽጉጥ ጭንቅላቱ ላይ በመተኮስ የራሱንም ሕይወት እንዳጠፋ ታውቋል፡፡ ድርጊቱን ሊፈፅም ወደቤት ሲመጣ የሚያውቁ ሠዎች ነበሩ ያለችው ሶሎሜ፤ ዝም ያሉት እራሱን ሊያጠፋ መስሏቸው እንደሆነ ለቅሶ ላይ እንደነገሯት ገልፃለች፡፡ “እኔ 18 አመቴ ነው፤ የ11ኛ ክፍል ተማሪ ነኝ፤ ከጐኔ ማንም የለም፤ የእህቴን ልጆች ማሳደግ አልችልም” የምትለው ሶሎሜ፤ እናታቸው ልጆቿን ስትከላከል ከጀርባዋ ተመታ እንደሞተች እንባ እየተናነቃት ተናግራለች፡፡ ገዳይ በሦስቱ ሟቾች ላይ ከተኮሰው አምስት ጥይት ውጪ ስምንት ጥይት በኪሱ ውስጥ እንደተገኘ ታውቋል፡፡