በአሜሪካ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ 2012 ሲጋመስ በካንትሪ ስልት የተሰሩ የሙዚቃ አልበሞች ገበያ መድራቱን ኤምቲቪ አስታወቀ፡፡ ባለፈው ስድስት ወር ብቻ በአሜሪካ የሙዚቃ ገበያ ላይ የቀረቡ አልበሞች ፤ ነጠላ ዜማዎች፤ ክሊፖች እና ዲጅታል ትራኮች ሽያጭ ብዛት 853.2 ሚሊዮን እንደነበር ኔልሰን ሳውንድ ስካን የተባለ ተቋም ይፋ አድርጓል፡፡ ከዚሁ የሙዚቃ ገበያ በካንትሪ ስልት የተሰሩ አልበሞች ድርሻ 19.4 ሚሊዮን እንደሆነ የገለፀው ኤምቲቪ፤ ከፍተኛ ሽያጭ አስመዝግበው ከ1 እስከ 10 ደረጃ ከወጣላቸው አልበሞች ሦስት የካንትሪ አልበሞች መሆናቸውን አመልክቷል፡፡
በሙዚቃ ገበያው በከፍተኛ የሽያጭ ብዛት የሚመራው የእንግሊዛዊቷ አቀንቃኝ አዴሌ “21” የተባለው አልበም 3 ሚሊዮን 668ሺ ቅጂ እንደተሸጠ ታውቋል፡፡ የሊዮኔል ሪቼ “ታስኪጅ” የተባለ አልበም ባለፈው ስድስት ወር 912ሺ ቅጂ በመቸብቸብ ሁለተኛ ደረጃ ሲይዝ “አፕ ኦል ናይት” የተባለው አልበም በ899ሺ ቅጂ እንዲሁም የሟቿ ዊትኒ ሃውስተን “ግሬተስት ሂትስ” አልበም 818ሺ ቅጂ በመሸጥ ተከታታይ ደረጃ ወስደዋል፡፡