Thursday, 25 June 2020 12:01

በ900 ሚ. ብር የተገነባው ሸገር ዳቦ ፋብሪካ ተመረቀ

Written by 
Rate this item
(3 votes)

በአዲስ አበባ ከተማ የተገነባውና በሰዓት 80 ሺህ ዳቦ የሚያመርተው ሸገር ዳቦ ፋብሪካ፤ በዛሬው ዕለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተመርቋል፡፡ በ900 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው ፋብሪካው፤ ከ3ሺ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል ተብሏል፡;

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በምረቃው ላይ ባደረጉት ንግግር፤#ፋብሪካው የዳቦ ፋብሪካ ብቻ ሳይሆን፤ በምግብ ራሳችንን የመቻል ፍላጎታችንን፣ ከድህነት የመውጣት ጥማትንና የብልፅግና ጎዳናን አመላካች ነው; ብለዋል።#በኢትዮጵያ በ10 ወራት ፋብሪካ ገንብቶ ማጠናቀቅ የሚታሰብ አልነበረም፤ በተለይም ለሚድሮክ; ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ሚድሮክ ከነበረበት ድክመት ተላቆ ፋብሪካውን በዚህ ፍጥነት ማጠናቀቅ መቻሉ ለሌሎችም ትምህርት የሚሆን ነው ሲሉ አድንቀዋል፡፡
 መንግስት በቀጣይ 2 ዓመታት ስንዴን ከውጭ ማስገባት የማቆም ፍላጎት እንዳለው በመግለጽም፤ ለዚህም የሙከራ ምርቶች መጀመራቸውን ጠቁመዋል፤ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ #ስንዴ ማምረት ብቻ ሳይሆን ምርቶቹን ወደ አግሮ ኢንዱስትሪ መቀየርም አስፈላጊ ነው; ብለዋል፡፡
መንግስት ላቀረበው ጥሪ ሼክ መሃመድ ሁሴን አሊ አላሙዲ ፈጣን ምላሽ መስጠታቸውን የገለጹት ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ፤  በእሳቸው አመራር የሸገር ዳቦ ፋብሪካም እውን እንዲሆን በማድረጋቸው ምስጋናቸውን አቅርበው፤ የኢትዮጵያ መንግስት ሁሌም ከጎናቸው እንደሚቆምም  አረጋግጠዋል።
 “አዲስ አበባን፣ ክልሎችን፣ ኢትዮጵያን ብሎም አፍሪካን እንለውጣለን” ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤“ኢትዮጵያ የጀመረችውን በሙሉ ታጠናቅቃለች፤ ይህንንም የምታደርገው በየአደባባዩ እየጮኸች ሳይሆን ሪቫን እየቆረጠች ነው” ብለዋል።የሸገር ዳቦ ፋብሪካ መገንባት የከተማውን ነዋሪዎች የኑሮ ጫና ይቀንሳል ያሉት ኢንጂነር ታከለ ኡማ በበኩላቸው፤ በቀጣይም የከተማዋ ነዋሪዎችን ጥያቄ የሚመልሱ ሥራዎችን በማቀድ ወደ ስራ መገባቱንም ተናግረዋል፡፡ የሚድሮክ ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አብነት ገብረ መስቀል ባደረጉት ንግግር፤ ሚድሮክ ኢትዮጵያ ለአዲስ አበባና
አካባቢዋ ነዋሪ ህዝብ በከፍተኛ ጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ ዳቦ አምርቶ ማቅረብ የሚያስችል የሸገር ዳቦ ፋብሪካን ገንብቶ ለፍሬ አብቅቷል ብለዋል። በ41 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈው ፋብሪካው፤ የዳቦና የዱቄት ፋብሪካ፣ የሻይ ቅጠል ማቀነባበሪያና 120 ሺህ ኩንታል ስንዴ ማከማቸት የሚያስችል 4 ጎተራ እንዳለው ለማወቅ ተችሏል፡፡ የዳቦ መጋገሪያ ፋብሪካው በሰዓት 80 ሺህ ዳቦ ፣ በቀን በሶስት ፈረቃም እስከ 2 ሚሊየን ዳቦ የሚያመርት መሆኑ
ታውቋል፡፡የሸገር ዳቦ ፋብሪካ ግንባታ በአጠቃላይ 900 ሚሊየን ብር መፍጀቱን ያስታወቁት አቶ አብነት፥ፋብሪካው ከምርት እስከ ማከፋፈል ሂደት 3 ሺ 400 ለሚደርሱ ዜጎች የስራ እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል፡፡

Read 5974 times Last modified on Thursday, 25 June 2020 12:07