Saturday, 09 May 2020 12:26

ከመስከረም 30 በኋላ በትግራይ ክልል የህወኃት የተናጠል ስልጣን ያበቃል

Written by  አለማየሁ አንበሴ
Rate this item
(2 votes)

 ከመስከረም 30 ቀን 2013 በኋላ በትግራይ ክልል የህወኃት ስልጣን እንደሚያበቃና “የጠባቂ መንግሥት” (Care taker Government) ሊቋቋም እንደሚችል የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ መሪ አቶ ነብዩ ስሁል ሚካኤል ገለፁ፡፡
የፓርቲው መሪ ትናንት በፌስቡክ ገጻቸው ባሰራጩት መረጃ፣ “ከመስከረም 30 በፊት በትግራይ የህወኃት የተናጠል ስልጣን ያበቃል” ብለዋል፡፡
የህወሃት የተናጠል ሥልጣን ማብቃቱን ተከትሎም ኢትዮጵያን የማስተዳደር ስልጣን የተሰጠው ብልጽግና ፓርቲ፣ በጠባቂ መንግሥትነት ትግራይን ያስተዳድራል ያሉት አቶ ነብዩ፤ የህወኃት እጣ ፈንታን በተመለከተም ከ50 በመቶ ያልበለጠ ከ25 በመቶ ያላነሰ የክልሉን ስልጣን እንዲጋሩ ሊፈቅድላቸው ይችላል ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ “ሕገ መንግሥታዊ ቀውስ ተፈጥሯል” የሚል መከራከሪያ የሚያነሱት ፖለቲከኛው አቶ ልደቱ አያሌው “ከመስከረም 30 በኋላ ገዥው ብልጽግና ፓርቲ በሕገ መንግሥት የተሰጠው ስልጣን ስለሚያበቃ የሽግግር መንግሥት ሊቋቋም ይገባል ሲሉ ከሰሞኑ አበክረው ሞግተዋል - አብዛኞቹ ተቃዋሚዎች ግን ሃሳባቸውን አልተቀበሉትም፡፡
የብልፅግና ፓርቲ መሪና የኢፌዲሪ ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ በበኩላቸው፤ ፓርላማው ያፀደቀው የሕገ መንግሥት ትርጉም የማሰጠት መፍትሄ ተግባራዊ እንደሚሆን ጠቁመው፤ ከዚህ ውጭ ባለፈ የሽግግር መንግሥት መመስረትና በክልል ደረጃ ምርጫ ማድረግ የሚሉ ኢ-ህገመንግስታዊ ሀሳቦች ተቀባይነት እንደማይኖራቸው አስታውቀዋል፡፡ ከሕገ መንግሥቱ ማዕቀፍ ውጪ ለመንቀሳቀስ በሚሞክሩ ወገኖች ላይ መንግሥታቸው ሕገ መንግስቱን ከጥቃት የመከላከል እርምጃ እንደሚወስድ ማስጠንቀቃቸው ይታወቃል::

Read 13342 times