Saturday, 28 December 2019 13:47

በሀሳብ መንገድ ላይ

Written by  ተመስገን
Rate this item
(2 votes)


             ሞትና ህይወት አንድ ነው
ዙርያ ገጠም - ክብ ዙረት
የበቀለው እየሞተ - የሞተው ሚበቅልበት፡፡
***
ፍርዴ “እውነት” ነው ሚዛኔ
በመጪው የምፃት ቀኔ
ለጽድቅም ይሁን ለኩነኔ
ፍትህ ብቻ ነው - ትርፍ ለኔ!
***
በረጋው ፍልስፍና ፈረስ
ወደ ህዋው ምገሰግስ
ከሰማየ ሰማያት ጫፍ
በፀሐይ መቅደስ ልነግሥ፡፡
***
ነፍስያ - ትንፈስ ወደዚያ
ወደ ፍጥረታት መዲና
ጋልቤ እንድደርስባት
በፀናው ልቤ ጐዳና
    አገሬ አሳቤ
    አገሬ ልቤ…ነውና!!
***
ከዲሴምበር ቀኖች አንደኛው ዓለም ዐቀፍ የፍልስፍና ቀን የተከበረበት ነበር፡፡ ከብዙዎቹ ሁለተኛው ዳግም ወደ ጠፈር የመጠቅንበት፡፡ ይኸው ዳግም ገናና አዲስ ዓመት!! “እንኳን አደረሰን!”
ሊቃውንቶቹ እንደሚሉት፤ ፍልስፍና ሃይማኖትና ሳይንስ በትክክል የሚገባቸው “የትም ፍጪው ዱቄቱን አምጪው” እንደሚባለው እውነትን መፈለግ፣ ዕውነትን ማወቅና ዕውነትን መኖር መቻል ነው፡፡ ሁሉም “አሁን” የምንኖራት የዚች ቅጽበት ሞተር ናቸው፡፡
ወዳጄ፡- ብዙ የተለያዩ የአስተሳሰብ ዘይቤዎች፣ አይዲዮሎጂዎችና ሌሎች ህዝቦችንና “ራሳችንን” ማዕከል ያደረጉ አመለካከቶች (World out looks) አሉ፣ ነበሩ፡፡ ፍልስፍናዊ የአስተሳሰብ ጥበብ ከሌሎቹ የሚለየው አንድም በምክንያታዊነት መሠረት ላይ መቆሙ፣ ባህሪና አኗኗርን “influence” ካላደረገ “ፉርሽ” መሆኑ፣ ሁለቱም “ነው” ለሚለው ድምዳሜ አራት ነጥብ አለ ማድረጉ ይመስለኛል፡፡ ሌሎቹን ዘጠና ዘጠኝ ምክንያቶች ለሊቃውንቶች እተዋለሁ፡፡
ቀደም ባሉ ዘመናት ለምሳሌ፡- “Long Live with the world out look of Marxist, Lenisnist Philosophy, which is the Scientific one” ተብሎ ተጽፎ አይተናል፡፡ ልክ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን ማርክሲዝም ራሱ እንደሚለው፤ ንድፈ ሃሳብ (Theory) በግብር ካልተለወጠ ወይም ካልተፈተነ ፋይዳ ቢስ ነው፡፡ ሊቃውንት “ያልተመረመረ ሃሳብ ከንቱ ነው” እንደሚሉት፡፡ ወዳጄ “ነው” ብለህ ለመደምደም አትቸኩል፡፡
በቀደም “EPRSSL” ወደ ጠፈር የመጠቀች ዕለት በኢትዮጵያ የሚኖሩት የቻይና አምባሳደር፤ ብዙ ሰዎች “መዳረሻ የለውም” ለማለት የሚጠቀሙበትን “Sky is the limit” በማለት ቀይረውታል፡፡ ድንቅ ሃሳብ ነው፡፡ ሰማይ በተለምዶ ወይም በቴሌስኮፕ ወደ ውጭ የምናየው፣ ህዋ፣ ጠፈር የምንለው ክስተት ሲሆን እምነት (Faith) ግን ወደ ውስጣችን የምንመለከትበት የስሜት መንኮራኩር ነው፡፡ የነፍስ ርቀት መለኪያ፡፡ ለነገሩ ሁለቱም መዳረሻ የላቸውም፡፡ ልዩነቱ እንደ ራስ መኖር፣ እንደ ሌላ ሰው መኖርና የሁለቱ ድልድይ ወይም ውሁድ መሆን ላይ ነው፡፡ ዕውነት የቃልና የሥጋ መዋደድ እንደሆነ ወይም “ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም” ተብሎ እንደተፃፈው ማለት ነው፡፡ ወዳጄ “ነው!” ለማለት አትቸኩል፡፡
እኔ እንደሚገባኝ፤ ዓለምን መረዳት ማለት ራስን ጨምሮ ሌሎች ሰዎች፣ ሌሎች ፍጥረታት፣ ከዋክብትና ፕላኔቶችን ባጠቃላይ “multivers” በምንለው ነገረ ህላዌ የተሰናሰለው ወይም የተቋጠረውን አካል ለማወቅ ለመረዳት፣ አንዱ ከሌላው ሊነጠል የማይችልበትን ህላዌ ሚስጢር፣ ለመግለጽ የአንዱ ህመም የሌላው የሚሆንበትን ምክንያት ለማስተዋል መሞከር ነው፡፡ ፍልስፍና አቋራጭና ምቹ መንገድ ነው፡፡
ወዳጄ፡- ሰው የማያስብ ወይም አእምሮ ቢስ ከሆነ ማሽን ይሆናል፡፡ ማሽን በሲስተም የተዋቀረ ነው፡፡ የነዳጅ፣ የዘይት፣ የአየር፣ የኤሌክትሪክ የኩሊንግና የመሳሰሉት ሲስተሞች ቅንብር ሲሆን የሚንቀሳቀሰው ግን በሰው አእምሮ ነው፡፡ ኦፕሬተሩ ከታመመ፣ አሰከረ ወይም ካበደ ማሽኑ ይቃጠላል፣ ይገለበጣል፣ ይጋጫል ወይም ገደል ይገባል፡፡
ሰውም ዳይጀስቲቭ ሲስተም፣ ስኬለተን ሲስተም ፣ ሰርኩላቶሪ፣ ብሪዚንግ፣ ነርቭና የመሳሰሉ ሲስተሞች አሉት፡፡ ይበላል፣ ይጠጣል ይንቀሳቀሳል፡፡ በትክክል ማሰብ ካልቻለ ግን “ሮቦት” ይሆናል፡፡ የግድ የሚመራው አእምሮ ያስፈልገዋል፡፡
ወዳጄ፡- ቁጥር ፖዘቲቭና ነጋቲቭ ከሌለው ቁጥር አይደለም፡፡ መደመር ከሌለ መቀነስ፣ መቀነስ ከሌለ መደመር የለም፡፡ እንደ ሞትና እንደ ህይወት አይነጣጠሉም፡፡ ብርሃን የሚኖረው ጨለማ ስላለ ነው፡፡ ከዋክብት እንዳለ ሁሉ ብላክ ሆል አለ፡፡ ወንድ ከሌለ ሴት፣ ሴት ከሌለ ወንድ የለም፡፡ ትውልድ የተቃራኒ ፆታዎች ፍሬ ነው፡፡ ወይራና ጥድ፣ ዋንዛና ቀረርቶ ሌሎችና ሌሎችም ፆታ አላቸው - እንደ ሰው፡፡ ግን ሁሉም ዛፎች ናቸው፡፡ አንዳቸው ካንዳቸው የሚለዩት በሚሰጡት ጥቅም ነው፡፡ የሰው ዋጋ የሚታወቀው በሚያፈልቀው ሃሳቡና በሚጠቅም ስራው ነው፡፡
ወዳጄ፡- ትልልቅ ሃሳቦች ስልጣኔን አግዝፈዋል፣ ሰውንና ሌሎችን ፍጥረታት አዛምደዋል፡፡ ትንንሽ ሃሳቦች ደግሞ ስልጣኔን ንደዋል፡፡ ህዝቦችን በጥላቻ ወሬ ከፋፍለዋል፡፡ “እኛ”፣ “እነሱ” እያሉ አዋግተዋል፡፡ እስኪ ይቺን በደንብ አንብብ፡፡ የፃፈልህ ታላቁ ዴቦን ነው፡፡
“Remember, it didn’t start with gas chamber It started with politicians dividing the people with
“us Vs THEM” It stated within tolerance and hate speech and when people stopped caring, become dsenticised  and turned a blind eye”
ክፉ ሃሳቦች የሚፈልቁት ከትንንሽ ጭንቅላት ነው፡፡ የኛው “አኖሌ”ም የዚህ ምሳሌ ነው፡፡
እንደነ ፕሌቶ፣ ቶማስ ሙር፣ ኤርቪንግ ዋላስና የመሳሰሉት ታላላቅ አሳቢዎች ደግሞ ሰለሞን አይላንድ፣ ዘ ስሪ ሳይረንስና የመሳሰሉትን፣ የሰው ልጅ በፍቅር፣ በመተጋገዝና በነፃነት የሚኖርባቸውን ምናባዊና ማህበራዊ ገነቶች ፈጥረው አሳይተውናል፡፡ የኛም አገር አውራ አምባ የዛ ምሳሌ ነው፡፡
ወዳጄ፡- ዘመኑ በጡንቻ ሳይሆን በሃሳብ ብልጫ፣ በመገፋፋት ሳይሆን በተመጋገዝ መኖር ብቻ እንደሚያዋጣ እያሳየን ነው፡፡ አንድ የድሮ ቀልድ ላስታውሳችሁ፡-
ሶስት ሱቆች በመደዳ ተከፈቱ፡፡ የመጀመሪያው ባለ ሱቅ በሩ ላይ “የትም የማይገኙ ዕቃዎች እዚህ አሉ” ብሎ ፃፈ አሉ፡፡ የመጨረሻ ደግሞ “የትም የማይደረግ ቅናሽ እናደርጋለን” በማለት ለጠፈ፡፡ አብዛኛዎቹ ሸማቾች የገዙት ግን ከመሃከለኛው ሱቅ ነበር፡፡ ምን ብሎ ቢጽፍ ይሆን?
***
ወዳጄ፡- ቅድም “EPRSSI” ንን በማምጠቃችን መደሰታችንን ጠቅሰን ነበር፡፡ ስለ ኮስሚክ ዓለም (Cosmic world) እና ስለ ጠፈር መንኮራኩሮች (Space vessel) ስናስብ ኒውተን፣ ጋሊሊዮ ኤሪንግተን፣ ሃውኪንግና ሌሎችን ሊቃውንት ማሰብ ግድ ነው፡፡ እነሱን ወደ ጐን እንተዋቸው፡፡ እኔን የሚገርመኝ፤ የነሱን ያህል መጪውን ጊዜ ከወዲሁ ማየት የቻሉ ፀሐፊዎች (Speculative writes) ህልም ዕውን ሲሆን ማየቴ ነው፡፡ ቬንዴታ (Vendeta) የተባለውን ታዋቂ ልብወለድ መጽሐፍ የፃፈችው ማሪያ ኮርሌ “The soul of Lilith” በተባለው መጽሐፏ ስለ  “The soul of Lilith” በተባለው መጽሐፏ ስለ Space observatory እና ስፔስ መንኮራኩር ከዓመታት ወዲያ ጽፋ ማንበቤን አስታውሳለሁ፡፡ ስታር ትሬክን ጨምሮ ሌሎችም አሉ፡፡
ወዳጄ፡- እንደ ማርቲን ሉተር ኪንግ ህልም፣ እንደ ሜሪ ኮሮሌ ቪዥን ይኑርህ፡፡ አይደለም ልጆችህ… ዓለም ያስታውስሃል፡፡ መጪው 2020 ይመችህ፡፡ ሃያ ሃያ ማለት “ናና” ማለት ነው፡፡
“ናና አንተዬ ናና፣ የሚለውን ዘፈን ሰምተሃል?...ናና እንደመር!!
ወደ ቀልዳችን ስንመለስ፤ የመሃለኛው ሱቅ ባለቤት በሩ ላይ የፃፈው “መግቢያው በዚህ ነው” የሚል ነበር፡፡
Happy New Year!
ሠላም !

Read 1526 times