Saturday, 21 December 2019 12:07

የኢራን አብያተ ክርስትያናት

Written by 
Rate this item
(0 votes)


              የሃሳብና የሃይማኖት ነፃነት በኢራን ጥልቅ መሰረት ያለው ነው፤ እንዲያውም ከኢራናውያን ባህል ጋር የተሾመነ ነው ማለት ይቻላል፡፡ እስልምና በዚህች አገር ላይ ዋነኛ ሃይማኖት ከመሆኑ በፊትም ሆነ በኋላ አናሳ የሃይማኖት ቡድኖች በነፃነት ኖረዋል፤ አብላጫው ሕዝብ በሚከተለው ሃይማኖት ገደቦች አልተጣሉባቸውም፡፡
የታሪክ ልሂቃን እንደሚሉት፤ መለኮታዊ (ቅዱስ) ሃይማኖቶች በዚህች ምድር ላይ ሁልጊዜም የሚገባቸውን አክብሮት ሰጥተዋል፡፡ ከቅድመ እስልምና ዘመን አንስቶ ክርስትያኖችም በነፃነት ሲኖሩ ቆይተዋል፡፡ ለዚህ ሃቅ፤ የኢራን ክርስትያኖች ታሪክ ምስክር ነው፡፡ በኢራን ጥቂት ታዋቂ፣ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያናት ይገኛሉ፤ ለምሳሌ፡- በኦሩሚህ የሚገኘው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን፣ በአይስፋሃን የቫንክ ቤተ ክርስትያንና በማኩ የቅዱስ ታዴዩስ ቤተ ክርስትያን፡፡  በኢራን በጥንታዊነቷ የምትታወቀው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን፤ በዓለም ላይ ከሚገኙ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያናት አንዱ ተደርጋም ትቆጠራለች፡፡
የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን በዓለም ሁለተኛዋ እጅግ ታዋቂ ቤተ ክርስትያን እንደሆነች ይነገራል - የኢየሱስ ክርስቶስ የትውልድ ሥፍራ በሆነችው ፍልስጤም ከምትገኘው የቤተልሄም ቤተ ክርስትያን በመቀጠል፡፡ በኢራን ካሉ ሌሎች ታዋቂ ቤተ ክርስትያናት ውስጥ በጆልፋ፣ አይስፋሃን የሚገኘው የቫንክ ቤተ ክርስትያን አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስትያኑ የተወሰኑ የኢራናውያን የሕንጻ ጥበብ ማራኪ ገጽታዎችን ያንጸባርቃል፡፡ በቤተ ክርስትያኑ ውስጥ ያሉት ስዕሎች፤ ማንም የኢራን ባለ ክህሎት ሰዓሊያን የሥነ ጥበብ ጣዕምና ምርጫ ይገልጻሉ። በቫንካ ቤተ ክርስትያን ግድግዳዎች ላይ ማንም ሰው፣ የጊዜ ሽግግር ሂደትን ማስተዋል ይችላል፡፡  
የቤተ ክርስትያን ሙዚየም ግድግዳዎቹ ከዕፁብ ድንቅ ሕንጻው ጋር ተዳምሮ፤ የሳፋቪሮ ዘመን ደማቅ የኢራናውያን ኪነ ህንጻን ወካይ ሆኖ ቆሟል፡፡
በጊዜ ባቡር ተንሻተን ወደ ኋላ ስንመለስ፣ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ6ኛውና በ9ኛው ክፍለ ዘመን ባሉት ጊዜያት፣ የቅዱስ ታዴዩስ ቤተ ክርስትያን በምዕራባዊ አዛርባይጃን ግዛት ውስጥ ነበር የሚገኘው፡፡
ይህ ቤተ ክርስትያን በኢየሱስ ክርስቶስ ሃዋርያ በቅዱስ ታዴዩስ እንደተገነባ ይነገራል፡፡ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ክርስትያኖች በየዓመቱ ወደ ቤተ ክርስትያኑ ሃይማኖታዊ ጉዞ ያደርጋሉ፡፡ በምዕራባዊ አዛርባይጃንና በአይስፋሃን ግዛቶች ውስጥ የሚገኙ ታዋቂ ቤተ ክርስትያናትን የተመለከተ አጭር ዘገባ (ሃተታ) አሰናድተናል፡፡
የምዕራባዊ አዛርባይጃን መዲና በሆነችውና በሰሜን ምዕራባዊ ኢራን፣ ከኦሩሚህ ሃይቅ አቅራቢያ (ከቱርክ ድንበር እምብዛም ሳይርቅ) በምትገኘው ኦሩሚህ እንጀምራለን። በመላው የታሪክ ሂደት፣ አዛርባይጃን፣ የኢራናውያን የእስልምና ሥልጣኔ ምንጭ እንዲሁም የተለያዩ የአርኪዮሎጂና ታሪካዊ መስህቦች ምድር በመሆን አገልግሏል፡፡
የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን
በኦሩሚህ የምትገኘው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን፤ በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉት እጅግ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያናት እንደ አንዱ ተደርጋ ትቆጠራለች፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ምድርን ጥሎ በሄደ አጭር ጊዜ ውስጥ አንስቶ ቤተ ክርስትያኒቱ በዚህ ከተማ እንደነበረች ይነገራል። በአሲሪያን ቋንቋ፤ ቤተ ክርስትያኒቱ ‹‹ማርት ማርያም›› ወይም ‹‹Holy Virgin›› (ቅድስት ድንግል) ተብላ ትጠራለች፡፡
አንዳንድ የታሪክ ምሁራን፤ ይህቺን ቤተ ክርስትያን ከፍልስጤሙ የቤተልሄም ቤተ ክርስትያን ቀጥሎ ሁለተኛዋ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያን እንደሆነች ያምናሉ። አራት ማዕዘን ቅርጽ ያለው የቤተ ክርስትያኑ ሕንጻ ፈርጣማና ቀላል ነው፡፡ የቤተ ክርስትያኑ ወፍራም መሰረት በድንጋይና በሲሚንቶ የተገነባ ነው፡፡ የቤተ ክርስትያኗ ውስጣዊ ክፍል የማምለኪያ አዳራሽ፣ የመስዋዕት ማቅረቢያ፣ ጥቂት ክፍሎችና መግቢያ ታዛዎችን ያካትታል፡፡ እንደ ቀድሞው ጊዜ፣ የተለያዩ ወፍ ዘራሽ ዕፅዋት የቤተ ክርስትያኑን ውስጣዊ ክፍል አስጊጠውታል። በቤተ ክርስትያኑ ውስጥ ሃውልቶች ወይም የቅዱሳን ስዕሎች አይታዩም፤ የምስራቃዊ ቤተ ክርስትያን የመጀመሪያ አባላት በእነዚህ ነገሮች ጥቅም አያምኑም ነበር፡፡
ቤተ ክርስትያኑን ከክርስቶስ ልደት በፊት በ642 ዓመተ ዓለም የጎበኘችው አንዲት የቻይና ልዕልት፤ ለዳግም ግንባታው አስተዋጽኦ አድርጋለች፡፡ ከዚያም በቤተ ክርስትያኑ ግድግዳ ላይ በተለበጠ ድንጋይ ላይ ስሟ ተቀርፆላታል፡፡ ዝነኛው ጣልያናዊ ተጓዥ ማርኮ ፖሎ፤ ቤተ ክርስትያኗን በጉዞ ማስታወሻው ላይ የገለፃት ሌላው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስትያን ጎብኚ ነው፡፡ እ.ኤ.አ በ1903 ዓ.ም ታዋቂው አሜሪካዊ ኦርዬንታሊስት ፕሮፌሰር አብራሃም ጃክሰን፤ ቤተ ክርስትያኗን የጎበኘ ሲሆን ፎቶግራፍም አንስቷል፡፡
አፕሪል 15,1918 ማርፖሎስዊስ፣ የምስራቃዊ ቤተ ክርስትያን መሪ ተደርገው የተሾሙበት ሥነ ሥርዓት የተካሄደው በዚህችው ቤተ ክርስትያን ነበር - በርካታ ቁጥር ያላቸው አንጋፋ የአሲርያን የሥነ መለኮት ሊቃውንትና ምሁራን በታደሙበት። በጣም ታዋቂ የነበሩ ግለሰቦች በቤተ ክርስትያኗ ታዛ በኩል ተቀብረዋል፤ ለምሳ የጋቪላን ግዛት ሊቀጳጳስ የነበሩትና በ1874 ያረፉት ማርዩሃና ይጠቀሳሉ፡፡  
የቫንክ ቤተ ክርስትያን በአይስፋሃን
በጆልፋ፣ አይስፋሃን የሚገኘው ቫንክ፤ በኢራን ሁለተኛው እጅግ ታዋቂ ቤተ ክርስትያን ነው፡፡ ከ400 ዓመት በፊት፤ አይስፋሃን በአንድ ወቅት የሳፋቪድ ሥርወ - መንግስት መቀመጫ ነበር፡፡ ከተማው የኢማም ክሆሜይኒ አደባባይን (በቀድሞ አጠራሩ ናቅሽ - ኢ -ጃሃን አደባባይ) በዓለም እጅግ ውብ ከሆኑ የታሪካዊ ሕንጻዎች ስብስብ ጋር አካትቶ ይዟል፡፡ የኢማም ክሆሜይኒ አደባባይና በዙሪያው ያሉ ሕንጻዎች፤ በኪነ - ሕንጻ ውበትና ጥበብ ረገድ አቻ እንደሌላቸው የሚታወቅ ሲሆን የዓለም ትልቁ ባህላዊ ቅርስ ተደርገው ይቆጠራሉ፡፡ ይሁን እንጂ የቫንክ ቤተ ክርስትያን፣ ከጥበባዊና ኪነ ሕንጻ እሴት አንጻር፣ በአይስፋሃን ከሚገኙ ሌሎች ታሪካዊ  ሕንጻዎች ጋር የላቀ ሥፍራ ተቀዳጅቷል፡፡ የዛያንዴህሩድ ወንዝ በከተማው መሃል ላይ በናቅሽ - ኢ -ጃሃን አደባባይ ያሉትን ታሪካዊ ሕንጻዎች፣ የቫንክ ቤተ ክርስትያን ከሚገኝበት የጆልፋ ግዛት ይለያቸዋል፡፡
ታሪካዊው የSi- o - se ፖል ወይም 33- Arched ድልድይና ሌሎች ጥቂት ጥንታዊ ድልድዮች ሁለቱን የከተማዋን ክፍሎች በአንድ ላይ ያገናኟቸዋል፡፡ በጆልፋ ግዛት በርካታ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያናት አሉ፡፡ ከሁሉም ግን እጅግ ታዋቂው የቫንክ ቤተ ክርስትያን ነው፡፡ ቤተ ክርስትያኑ በዕድሜ ጠገብ ዛፎች የተከበበ ሲሆን ቅጥሩ ጡብ የተነጠፈበት ነው፡፡ ቤተ ክርስትያኑ በትክክል መቼ እንደቆመ አይታወቅም፡፡ ሆኖም በኢስፋሃን ከሚገኙ ጥንታዊ ቤተ ክርስትያናት አንዱ እንደሆነ ማስረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ቤተ ክርስትያኑ እ.ኤ.አ በ1905 ዓ.ም ዳግም ግንባታ ተደርጎለታል፡፡ አንዳንድ የታሪክ ምሁራን፤ አሁን የቫንክ ቤተ ክርስትያን በቆመበት ሥፍራ ላይ በአንድ ወቅት የአናሂታ ቤተ መቅደስ ቆሞ እንደነበር ያምናሉ፡፡ ክርስትያኖች ቤተ ክርስትያኑን  ‹‹Amenapregij›› ብለው የሰየሙት ሲሆን ትርጉሙም ‹‹አዳኝ›› ማለት ነው፡፡
ሻህ አባስ - ኢ - ሳፋቪ፤ በጆልፋ ነዋሪ ከነበሩ አርመናውያን በተገኘ ልገሳ ቤተ ክርስትያኑ ዳግም ግንባታ እንዲደረግለት ፈቀዱ፡፡ ቤተ ክርስትያኑን የተገነባበት ድንጋይ፣ በአርመንያዊ ሬቫን ከሚገኝ ሌላ ቤተ ክርስትያን ወደ ኢስፋሃን እንደተጓጓዘ ይነገራል፡። በቤተ ክርስትያኑ ላይ ከተቀረፁ ጽሁፎች የቀብር፣ የቤተ ክርስትያኑ መስራች ‹‹Khajeh Avedicp›› እንደሆነ ይገልጻል። በቫንክ ቤተ ክርስትያን በርካታ የተቀረፁ ጽሁፎች ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ጽሁፎች የተቀረፁትና የተለበጡት በተለያዩ ታሪካዊ ወቅቶች በነበሩ ታላላቅ ሰዎች ትዕዛዝ ነበር፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስን የቀብር ሥነ ሥርዓት የሚያሳይ እንደሆነ የሚነገርለት ስዕል ሊጎበኝ የሚገባው ነው። የቀብር ሥነ ሥርዓቱ በኢራን ሰዓሊያን ውብ ተደርጎ ተገልጿል፡፡ ሌላው መጎብኘት ያለበት ደግሞ የቤተ ክርስትያኑ ሙዚየም ነው፡፡ ሙዚየሙ በርካታ ታሪካዊ ሰነዶችንና ቁሶችን ይዟል፡፡ በሙዚየሙ ውስጥ የተቀመጡት አብዛኞቹ ቁሶች ለቤተ ክርስትያኑ በስጦታነት የተበረከቱት ወደ አውሮፓ ይጓዙ በነበሩ ክርስትያንና አርመናውያን ነጋዴዎች ነው፡፡
በአርመንኛ ቋንቋ የተጻፉ ማኑስክሪፕቶች እንዲሁም የሳፋቪዳ ነገስታት ትዕዛዞችና ደብዳቤዎች በሙዚየሙ ውስጥ ተቀምጠዋል፡፡ በቫንክ ቤተ ክርስትያን ማተሚያ ቤትም ይገኛል፡፡ ማተሚያ ቤቱ የተቋቋመው መነኩሴና የቤተ ክርስትያን መሪ በነበሩት ‹‹Khachatour Gesatatski›› የተባሉ ግለሰብ ነው፡፡ ከቤተ ክርስትያኑ አጠገብ ቤተ መጻሕፍትም ይገኛል፡፡
የቅዱስ ታዴዩስ ቤተ ክርስትያን
በኢራን ሊጎበኙ ከሚገባቸው ሌሎች ቤተ ክርስትያናት መካከል በካራ - ዝያ - ኢድ - ዲን የሚገኘው የቅዱስ ታዴዩስ ቤተ ክርስትያን አንዱ ነው፤ በምዕራብ አዛርባይጃን፣ በማኩና በበዛርጋን ግንባር መካከል የቆመው ቤተ ክርስትያን፡፡ የታሪክ ልሂቃን፤ ቤተ ክርስትያኑ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ6ኛውና 9ኛው ክ/ዘመን በነበሩት ጊዜያት ተገንብቷል ብለው ያምናሉ፡፡
ቤተ ክርስትያኑ ከክ.ል.በፊት በ1319 በተከሰተ የመሬት መንቀጥቀጥ ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበታል፡፡ ሌሎች የታሪክ አጥኚዎች፤ የቅዱስ ታዴዩስ ቤተ ክርስትያን፤ ከክርስቶስ ሃዋርያት በአንዱ እንደተገነባ ይናገራሉ፡፡ አንዳንድ መረጃዎች እንደሚመሰክሩት፤ ከክ.ል.በፊት በ40 ዓ.ዓ ታዲዩስ ክርስትናን ለመስበክ ወደ አካባቢው ተጉዞ ነበር፡፡ ያን ጊዜ ታዲያ ታዴዩስግና ሳንዶክህት (የንጉሱ ሴት ልጅ) በንጉሱ ተሰውተዋል ይባላል፡፡
የሳንዶክህት መቃብርም በዚሁ ቤተ ክርስትያን ይገኛል፡፡ በየዓመቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ክርስትያን የሃይማኖት ተጓዦች፤ የታዴዩስና ሳንዶክህትን ቤተ ክርስትያንና የመቃብር ሥፍራ ለመጎብኘት ወደ ካራ - ዝያ - ኢድ - ዲን ይተማሉ፡፡        

Read 1457 times