Monday, 18 November 2019 00:00

በናይጀሪያ የጥላቻ ንግግር በስቅላት ያስቀጣ መባሉ ተቃውሞ ገጥሞታል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

   የናይጀሪያ ምክር ቤት ግጭትና ሞት የሚያስከትሉ የጥላቻ ንግግሮችንና መልዕክቶችን እንዲሁም ሃሰተኛ መረጃዎችን ያሰራጩ የአገሪቱ ዜጎች በስቅላት እንዲቀጡ ለማድረግ ያቀረበው ረቂቅ ህግ ከመብት ተሟጋቾችና ፖለቲከኞች ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው ተዘግቧል፡፡
ረቂቅ ህጉ ባለፈው ማክሰኞ ለአገሪቱ የህግ መወሰኛ ምክር ቤት መቅረቡን ተከትሎ፣ በርካታ ናይጀሪያውያን ህገ መንግስቱን የሚጋፋ ነው በሚል ተቃውሟቸውን ማሰማታቸውን የዘገበው ኦል አፍሪካን ኒውስ፤ የምክር ቤቱ ምክትል ሊቀ መንበር ህጉ የናይጀሪያውያንን መብት የሚጋፋና ችግር የሚፈጥር ከሆነ እንደማይጸድቅ በመጠቆም፣ ዜጎች የምክር ቤቱን ውሳኔ በትዕግስት እንዲጠባበቁ ጥሪያቸውን ማቅረባቸውን አመልክቷል፡፡
ዜጎችን በስቅላት እስከ ማስቀጣት የሚደርሰው አዲሱ ህግ፤ ብሔርና ዘርን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶችን የሚፈጽሙ ዜጎች ከአምስት አመት ባላነሰ እስርና ከ10 ሚሊዮን የአገሪቱ ገንዘብ ባላነሰ እንዲቀጡ የሚደነግግ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፣ ግጭትና ሞት የሚያስከትሉ የጥላቻ ንግግሮችን በተመለከተ የማጣራትና ወንጀሉን የፈጸሙትን ተከታትሎ ለህግ የማቅረብ ስራ የሚያከናውን ገለልተኛ ብሔራዊ ኮሚሽን እንዲቋቋም የሚጠይቅ መሆኑንም አስታውቋል፡፡
ረቂቅ ህጉ ተቃዋሚዎችንና የመብት ተሟጋቾችን ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናትን ጭምር ማስቆጣቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ህጉ ተግባራዊ መደረግ የለበትም በሚል በግልጽ ከተቃወሙት ባለስልጣናት መካከልም የአገሪቱ የነዳጅ ሚኒስትር ዴኤታ ጌሚሶላ ሳራኪ እንደሚገኙበትም አስታውቋል፡፡
ባለፈው አመትም ለምክር ቤቱ ተመሳሳይ ረቂቅ ህግ ቀርቦ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ምክር ቤቱ ግን  ውድቅ አድርጎት እንደነበር አክሎ ገልጧል፡፡


Read 2797 times