Saturday, 26 October 2019 12:39

በሀሳብ መንገድ ላይ

Written by  ተመስገን
Rate this item
(0 votes)

 “በእጅህ የያዝካት ወፍ እያለች ሰማይ ለሰማይ በምትበረው አትወራረድ”
                         
           “ሃሜት ቅዱሷን ነፍስህን ያረክሳል-+፣ ያወራኸው ውሸት ሲሆን ውስጣዊ ሰላምህ ክንፍ ያበቅላል” ይላል…አንድ ፀሐፊ፡፡ የምነግርህ እውነተኛ ታሪክ ነው፡-
በአንድ ቢሮ ውስጥ የሚሰሩ ሶስት ሰዎች ነበሩ፡፡ አንደኛው መስሪያ ቤቱን የተቀላቀለው በቅርብ ነው፡፡ “ከኛ በላይ ሃይማኖተኛ ላሳር ነው” የሚሉት ሁለቱ ሰዎች “ፋታ” ባገኙ ጊዜ ሁሉ ጐን ለጐን ተቀምጠው የሰው ስጋ ይቦጭቃሉ፡፡ ኩዳዴ ሲገባ ያለ አስር ስዓት እህል ውሃ የማይቀምሱት፣ ሰንበትና በዓላትን ሳያስተጓጉሉ የሚያስቀድሱት የነዚህ ሰዎች ነገር ሁሌም ሰውየውን እንዳስገረመው ነው፡፡ አንድ ቀን አጅሬው የመ/ቤቱ ክበብ ውስጥ የተጠበሰ ሥጋ ሲበላ ሁለቱ ሰዎች መጡ፡፡ ሰላምታ ተለዋውጠው መመገቡን ሲቀጥል..” “ምነው አጅሬ “እንብላ”ም አይባልም ‘ንዴ? ሲሉት ምን ብሎ እንደመለሰላቸው ታውቃለህ?...መጨረሻ ላይ ታነበዋለህ፡፡
***
ወዳጄ፡- የሆነውን ሆነ፣ ያልሆነውን አልሆነም ማለት መቻል ልንጠብቀው የሚገባ ሰብዓዊ ፀጋችን ነው፡፡ በባለቤትነት የያዝናቸው የራሳችን ጉዳዮች ሳያስጨንቁን፣ ለህሊና ጥያቄዎች መልስ መስጠት ሳንችል፣ ስለ “ሌላው እውነት” ሃላፊነት መሸከም የሚችል የሞራል ሰብዕና “አለኝ” ብሎ ማሰብ ራስን አለማወቅ ነው፡፡ ከራሳችን እየሸሸን ሌሎችን መወዳጀት፣ ውስጣችን ጨልሞ ለሌሎች ብርሃን መስጠት የ “ዕውነት” ሊሆን አይችልም፡፡
“የወንድምክን ዓይን ጉድፍ
ላውጣ ብለህ አትጣደፍ
መጀመሪያ ራስክን እየው
ያንተም ዓይን ጉድፍ አለው፡፡” …ይሉናል፡፡
ቅዱሳን መፃሕፍት፡፡ ዞሮ፣ ዞሮ ለራሱ ሰላም የሌለው ለሌላው ሰላም አይጨነቅም እንደ ማለት ነው፡፡
የሰላም ነገር ሲነሳ አንድ የጂብሰን አካዳሚ ተማሪ “Peace” በሚል ርዕስ በጃፓን ታይኩ የግጥም ስልት (5-4-5) ለሁለተኛ ጊዜ አንደኛ በመውጣት አሸንፎ ነበር፡፡ (የመጀመሪያውን ከዚህ ቀደም ጽፌዋለሁ) እንዲት ትላለች፡-
You can not be bought,
Never be stolen either,
Peace, how dear you are.
ወዳጄ፡- “በእጅህ የያዝካት ወፍ እያለች ሰማይ ለሰማይ በምትበረው አትወራረድ” ይላሉ፤ ሊቃውንት፡፡ ሰላምም እንዲሁ ነው:: በውስጥህ የገነባኸው ሰላም ከፈረሰ፣ መልሶ መገንባት እንደ መጀመሪያው “ቀላል” አይሆንም:: የሊቃውንት ነገር ካነሳን፣ ሰውየው ችግሩን ለማወያየት ከከተማው ራቅ ብለው ወደሚኖሩ አዋቂ ዘንድ ሄደ፡፡ እንዳገኛቸውም…
“መኖር አቃተኝ” አላቸው፡፡
“አይዞህ፣ ላንተ ያለው አይቀርም” አሉት፡፡
“ኧረ ብሶብኛል!”
“ሁሉም ነገር በህይወት መዝገብህ ላይ እንደተፃፈው ነው፡፡ በርታ!” ሲሉ መከሩት፡፡
“የምበላው እንኳ እየቸገረኝ ነው” ጠየቃቸው::
“እንኳን በአምሳሉ የፈጠረውን ቀርቶ ዕውር አሞራ የሚቀልብ አምላክ አለ፤ ተስፋ አትቁረጥ” ብለው አሰናበቱት፡፡
አላመናቸውም፡፡ ወደ ቤቱ ሲመለስ ረሃብና ጥሙ ፀናበት ደከመው፡፡ ከሩቅ ወደሚያየው ዋርካ ስር ለማረፍ ሄደ፡፡ ወደ ዋርካው ሲጠጋ የጥዓም ምግብና መጠጥ ሽታ ተቀበለው:: የአገልግል ምግብና የሽክና ጠጅ ከግንዱ ስር ተቀምጧል፡፡
እዚያ ምድረ በዳ ላይ ይኸንን ማየት የሚታመን አልሆነለትም፡፡
“እየቃዥሁ ነው ወይስ…” እያለ ማሰብ ከመጀመሩ ከሩቅ የሚመጣ ሰው ተመለከተ፡፡ ሰጋና ከዋርካው ላይ ወጥቶ አደፈጠ፡፡
እንግዳው ዝናር የታጠቀ፣ ብረት ያነገበ ነበር:: ከዛፉ ጥላ እንዳረፈም “እፎይ” ብሎ አገልግሉን መፍታት ጀመረ፡፡ “ባርክልኝ” ለማለት ወደ “አምላኩ” ቀና ሲል፣ ሰውየው ቅርንጫፎቹ መሃል ይቁለጨለጫል፡፡ ተደናግጦ ተስፈነጠረና መሳሪያውን አቀባብሎ ወደ ሰውየው ሲወድር፤
“የግዜር መንገደኛ ነኝ” እያለ መጮህ ጀመረ፤ ሰውየው፡፡
“በል ውረድ”…አለው፡፡
ወረደ፡፡
“ሌላው ነገር ቢያቅታችሁ በመርዝ መጣችሁብኝ?!” ሲል አፋጠጠበት፡፡
“ኧረ ጌታው እኔ ምንም የማውቀው ነገር የለም”
“ዝም በል! ስሞት፣ ስጣጥር ልታይ እንጂ ምን አስደበቀህ ታዲያ?”
ከዛፉ ጋር ጠፍሮ አሰረው፡፡ ባለ ብረቱ “ላንተ ጥይት አላባክንም፤ በቀመማችሁት መርዝ ትሞታለህ! እያለው ፍትፍቱን ባፍ ባፉ ያጐርሰው ገባ፡፡ ረሃብተኛው ሰው በገጠመው ነገር ይስቅ ጀመር፡፡
“እየሞትክ ትስቃለህ እንዴ?”
“አንዴ አድምጠኝ ጌታው” አለና ሁሉንም ነገር በዝርዝር ነገረው፡፡ ምግቡ ሰውየውን ምንም እንዳላደረገው የታዘበው ታጣቂም የሰማውን አምኖ፣ እየተገረመ ከሰውዬው ጋር መሳቅ፣ መብላትና መጠጣቱን ተያያዘው፡፡ የሸፈተበትን ምክንያት፣ ያካባቢው ሰው በየተራ እንደሚቀልበውም አጫወተው፡፡
ወዳጄ፡- ከተፃፈልህ እጅህ ታስሮ፣ መሳሪያ ተደቅኖብህ እንኳ የሚያጐርስህ አታጣም፡፡ ዐዋቂው “ላንተ የተባለ አይቀርም” ያሉት ነገር ሆነ፡፡
ሽፍታው ወዳጁ ተሰናብቶት ወደመጣበት እንደተመለሰ ከድካሙ ለመላቀቅ በጀርባው ተንጋለለ፡፡ ቅድም ከቅርንጫፎቹ ባንደኛው ላይ አፉን ከፍቶ የተቀመጠው አሞራ አሁንም ከቦታው አልተነቃነቀም፡፡ በቅርንጫፎቹ መሃል ዥው፣ ዥው፣ ከሚሉት ነፍሳት መሃል ብዙዎቹን ነፋስ እየገፈተረ ወደተከፈተው አፍ ይጥላቸው ነበር፡፡ በዚህ መሃል አምስትና ስድስት የሚሆኑ አሞሮች ነፋሱን እየቀዘፉ መጥተው በዋርካው እናት ማንዣበብ ጀመሩ፡፡ ብቸኛው አሞራም ተቀላቀላቸውና እንደ ሙሽራ አጅበውት በረሩ፡፡
ሰውየው ተንጠራርቶ ሲመለከት አሞሮቹ ትንሽ ኩሬ አጠገብ እንደደረሱ ወደ መሬት ዝቅ ሲሉ ተመለከተ፡፡ ብቸኛው አሞራ ውሃ እስኪጠጣ ሌሎቹ እያንዣበቡ ቆዩ፡፡ እንደጨረሰ በሄዱበት አኳኋን ወደ ዋርካው ተመለሱ፡፡ አሞራውም ከመሃላቸው ተነጥሎ እየተንደፋደፈ በአንደኛው ቅርንጫፍ ላይ አረፈ፡፡ ተመቻችቶ ተቀምጦ አፉን እንደከፈተ ጓደኞቹ ከነፉ፡፡ ለካስ አሞራው ዓይኖቹ የታወሩ ነበሩ፡፡ ሰውየውም “ዕውር አሞራ እሚቀልብ አምላክ አይጥልህም” ብለው አዋቂው የነገሩትን አስታወሰ፡፡
“አላህ ያውቃል፣ ነቢይ ያውቃል
ሰው በከንቱ ይጨነቃል…”ሲባል የዋዛ ይመስለው ነበር፡፡
ወዳጄ፡- ለሰው የሚያስፈልገው ዋናው ነገር “ጤና” ነው እንላለን፡፡ ጤና ካለ ሌላው ቀላል ነው ለማለት፡፡ ለአገር ደግሞ ዋናው ነገር ሰላም ነው፡፡ ሰላም ካለ አሁን በያዝነው የለውጥ መንገድ ችግሮችን እየፈታን ወደ ብልጽግና መጓዝ አያዳግትም፡፡ አለበለዚያ በተሸከምነው የኑሮ ቀንበር ላይ ድንጋይ መደረብ ይሆንና ማጣፊያው ያጥርብናል፡፡
ወዳጄ፡- የገሃነብ በር ሁሌም ክፍት ነው፡፡ እንደ አሞራው አፍ የሚውጠውን ይጠብቃል:: በውይይት የሚያልቁ ጉዳዮችን እያካበድን፣ በትንሽ በትልቁ እየተናተረክንና በስሜት እየተናወጥን ዜጐችን ለእሳት መማገድ ያሳዝናል:: በ2009 ዓ.ም መጨረሻ አካባቢ በዚሁ የሃሳብ መንገድ ላይ ከተጠቀሰ ጽሑፍ ጥቂት መስመሮች ላስታውሳችሁ፡- ሰውየው እሳት ዳር ቁጭ ብሎ መጽሐፍ ያነባል፡፡ ቀና ሲል የቁጫጭ መዓት እየተግተለተለ እሳቱ ውስጥ ይማገዳል፡፡ አዘነና በተናቸው፡፡ ትንሽ አንብቦ ቀና ሲል ቁጫጮቹ ተሰባስበው እንደገና እሳቱ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ሲደጋገምበት ሰለቸውና “የአገሬም ሰው እንዲሁ ነው!” ብሎ ተዋቸው… ይላል፡፡
***
ወደ ጨዋታችን ስንመለስ፤ ሃሜተኞቹ ሰውየውን፡-
“እንብላ አይባልም ወይ?” ሲሉት
“የከብት ስለሆነ ነው” ብሎ ነው የመለሰላቸው  “እናንተ ሰው ነው እምትበሉት” እንደማለት፡፡
ዴንዚል ዋሽንግተን፡- “የኔ ስኬት ውስጣዊ ሰላም ማግኘት ነው” ይለናል፡፡ አንተስ ወዳጄ ምን ትላለህ?
ሠላም!!   

Read 1398 times