Saturday, 12 October 2019 12:02

Mentorship -የጤና ባለሙያዎችን እውቀትና ክህሎት ለማዳበር

Written by  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
Rate this item
(0 votes)

 የእናቶችና ሕጸናትን ጤና ጥራቱን በጠበቀ መንገድ አገልግሎትን ለመስጠት እንዲቻል በስራው ላይ ለተሰማሩት የጤና ባለሙያዎችና ተቋማት የቴክኖሎጂ ድጋፍ ( የምክር አገልግሎት፤ክትትል የማድ ረግ፤ ሀሳብ ወይንም ልምድ ማካፈል) የመሳሰሉትን ማድረግ እንዲያስችል በኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ፕሮግራም ተዘርግቶአል፡፡ ይህንንም የተዘረጋውን ፕሮግራም የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ለሶስት ወራት ሲያስፈጽም መቆየቱንና በጊዜው የተደረ ሰበትን ደረጃ ለመወያየት ባለሙያዎቹ ከኦሮሚያ ምእራብ ዞን ለስብሰባ ተጠርተው እንደነበር እና የነበረውን የስራ አፈጻጸም ሁኔታ ባለፈው እትም አስነብበናችኋል፡፡ በዚህ እትም ደግሞ በዚያው በኦሮሚያ ምእራብ ሸዋ ዞን በጀልዱ ፤ጉደር እና ጌዴኦ ሆስፒታሎች ያለውን ገጽታ ዶ/ር ደረጀ ለማ እና ዶ/ር ቶሎሳ ( በአምቦ ሆስፒታል የማህጸንና ጽንስ ሕምና እስፔሻሊስቶች) በጥናት አስደግፈው ያቀረቡትን እውነታ ለንባብ ብለናል፡፡
የምእራብ ሸዋ ዞን በኦሮሚያ ካሉት 20/ አስተዳደራዊ ዞኖች አንዱ ነው፡፡ የምእራብ ሸዋ ዞን ከተማ አምቦ ሲሆን ከአዲስ አበባ 114 ኪሎ ሜትር ይርቃል፡፡ የምእራብ ሸዋ ዞን 23 ወረዳዎች ያሉት ሲሆን ህዝቡም 1‚028‚501 ወንዶች እና 1‚030‚175 ሴቶች ናቸው፡፡ ከዚህ ውስጥም 6‚10% ማለትም ወደ 242‚35 ያህሉ የከተማ ነዋሪ ነው፡፡
በምእራብ ሸዋ አራት የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች የሚገኙ ሲሆን እነርሱም በእንጪኒ ፤ጉደር ፤ጀልዱ እና ባኮ ይገኛሉ፡፡ በአምቦ ጌዴኦ እና ግንደበረት ደግሞ አጠቃላይ ሆስፒታሎች  እና በአምቦ ዩኒቨርስቲ አንድ ሪፈራል ሆስፒታል ይገኛል፡፡ በምእራብ ሸዋ ዞን 96 የህዝብ ጤና ተቋማት እና 77 የግል ክሊኒኮች እንዲሁም 526 የጤና ጣቢያዎች ይገኛሉ፡፡
ጉደር የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ወደ 325‚000 የሚደርሱ ታካሚዎች ያሉት ሲሆን ጀልዱ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ደግሞ ወደ 202‚716 ለሚሆኑ ሰዎች የህክምና አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ጌዶ ጠቅላላ ሆስፒታል ወደ አንድ ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎችን በህክምና የሚረዳ ሲሆን ይህ አጠቃላይ ሆስፒታል ወደ ሰባት የሚሆኑ ወረዳዎችን ያገለግላል፡፡
ከላይ የምትመለከቱት በስብሰባው ላይ ከማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ፤ከኦሮሚያ ክልል፤ ዞን፤ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የተወከሉ ባለሙያዎች ስብሰባውን ሲካፈሉ ነው፡፡
በምእራብ ሸዋ ዞን ከላይ በተጠቀሱት አካባቢዎች ባሉ የጤና ተቋማት (mentorship) የምክር አገልግሎት፤ የልምድ ልውውጥ እና ሌሎች የቴክኒክ ድጋፎች የመደረጋቸው አላማ እንደ ጥናት አቅራቢዎቹ ዶ/ር ደረጀ እና ዶ/ር ቶሎሳ ማብራሪያ፤
የእናቶችንና ጨቅላ ህጻናቶቻቸውን ሕመም.፤ ሞት እና የአካል ጉዳተኝነት ለመቀነስ እና የጤና አገልግሎቱን በተሻለ ብቃትና ደረጃ ለመስጠት፤
በተሟላ ደረጃ አስቀድሞ እራስን ከበሽታ የመከላከል እውቀትን እና ክህሎትን ማካፈል፤
ወደ ቀጣይ ማለትም አገልግሎቱ ካለበት ደረጃ እንዲሻሻል ለማድረግ ማገዝ፤
ጤና እንዲሻሻል ወይንም ወደነበረበት እንዲመለስ (ከሕመም መዳን) የሚያስችል የጤና አገል ግሎትን ሁሉም ባለድርሻ አካላት በሚሳተፉበት መንገድ ለህብረትሰቡ እውን ማድረግ ነው፡፡
ስለዚህም የmentorship አላማ ለእናቶችና ለህጻናቱ የሚሰጠው የጤና አገልግሎት እውቀትንና ክህሎትን ለሌሎች በማካፈል የእናቶችን ፤የጨቅላ እና የህጻናቱን ሞት ለመቀነስ እንዲሁም ጤናቸው በተሻለ መንገድ እንዲጠበቅ ለማድረግ ነው፡፡ ስለዚህም በኦሮሚያ በምእራብ ሸዋ ዞን በጉደር፤ ጀልዱ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎችና በጌዶ ጠቅላላ ሆስፒታል እ.ኤ.አ June - August 2019 በተፈጸመው አሰራር፤-
ጥራትን በማምጣት ደረጃ ተከታታይነት ያለው አሰራርን በጉደር፤ ጀልዱ እና ጌዶ ሆስፒታሎች እና አብረዋቸው የሚሰሩ የጤና ተቋማት በምን መንገድ ማሻሻል እንደሚቻል ማሳወቅ፤
በሶስቱ ሆስፒታሎች የምክር አገልግሎት፤ የልምድ ልውውጥ፤ ስልጠና እንዲሰጡ ለተመረጡ (mentees) ምክር ሰጪዎች ችሎታቸውን ማሳደግ፤
አገልግሎቱ በሚሰጥባቸው አካባቢዎች ያሉ የህክምና ተቋማት እርስ በእርሳቸው የሚደጋገፉበትንና ሀሳብ የሚካፈሉበትን፤ ልምድ የሚለዋወጡበትን እንዲሁም ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ የሙያ መሳሪያዎችን እንዲዋዋሱ ወይንም እንዲጠቀሙ የማድረግ ዘዴን እንዲያበረታቱና እና ስራ ላይ የሚያውሉበትን መንገድ፤ ዘዴ ማመላከት …ወዘተ ናቸው፡፡
የmentorship እቅድ ተይዞ ለሶስት ወራት ስራው በተሰራባቸው ሶስት ሆስፒታሎች አንዳንድ የታዩ ችግሮች መኖራቸው በጥናቱ ተጠቅሶአል፡፡
ከተጠቀሱት ችግሮች መካከል ደካማ መረጃ አያያዝ በስፋት የተጠቆመ ሲሆን የቤተሰብ እቅድ አገልግሎት ጋር በተያያዘ የስልጠና አለመኖር ተጠቁሞአል:: ሙያተኞች ተረኛ ሆነው ሲመደቡ እንዲሁም ለአልትራሳውንድ ስራ ሲፈለጉ የሙያተኞች አለመገኘት፤ የደም እጥረት የመሳ ሰሉትና የባለሙያዎች በስራ ላይ አለመቆየት እንደ ትልቅ ችግር በሶስቱም ሆስፒታሎች የተ ጠቀሱ ናቸው፡፡ ለምሳሌም በአንዳንድ ሆስፒታሎች ከከተማው ወደ ሆስፒታሉ የሚሄድ ትራንስ ፖርት እጥረት መኖሩ፤ለአገልግሎት የሚፈለጉ መሳሪያዎች አለመሟላት፤መሰረታዊ ለሆኑ የጤና አገልግሎት ስራዎች የስልጠና አለመኖር የመሳሰሉት ለእናቶችና ለጨቅላዎቻቸው እንዲ ሁም ለህጻናት ተገቢውን እና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት እንዳይቻል አድርጎታል፡፡ በጉደር ሆስፒታልም የሕክምና መገልገያ መሳሪያዎች ጥገና አለመኖር ስራውን በትክክል ለመስ ራት የማያስችል አስቸጋሪ ሁኔታ መኖሩ ተጠቁሞአል፡፡
እንደችግር ከተጠቀሱት መካከል የትራንስፖርት ችግር ማሳያ የሚሆን ምሳሌም በጥናት አቅራቢዎቹ እንደሚከተለው ተገልጾአል፡፡
‹‹…በኦሮሚያ በምእራብ ሸዋ ዞን ካሉት ሆስፒታሎች መካከል አንዱ ከከተማው ወጣ ባለ ሁኔታ የሚገኝ ነው:: ሰራተኞች ወደስራቸው በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ ከርቀቱ የተነሳ በእግራቸው ለመሄድ በተለይም ሴቶቹ ብዙ ጊዜ ይቸገራሉ፡፡ በስብሰባው ላይ ተሳታፊ የነበረ አንድ ባለሙያ እንደጠቁመው …16/እና ከዚያ በላይ የሆነ ኪሎሜትር እርቀት እንኩዋንስ ለሴቶቹ እኔም ብሆን አልሞክረውም …ነበር ያለው፡፡ ታዲያ አንዲት በአገሬው ተወዳጅ የሆነች ነርስ ወደስራዋ ለመ ሄድ በአካባቢው ያለውን መጉዋጉዋዣ ትጠቀማለች፡፡ አንድ ቀን ግን ጉዞዋ ወደስራ ቦታዋ ሳይ ሆን ወደሌላ ቦታ ይቀየራል፡፡ ይህች ባለሙያ ወደስራዋ እንዲያደርሳት የጠየቀችው መጉዋጉ ዋዣ አካሄዱን ለውጦ የግል ፍላጎቱን ሊያረካ ወደሚችልበት ቦታ አፋጥኖ ይወስዳታል፡፡ ያሰበውም አልቀረም:: ባለሙያዋን አስገድዶ ይደፍራታል፡፡ ይህች ባለሙያ ከዚያ በሁዋላ በደረሰባት አደጋ የተነሳ በዚያ አካባቢ መስራት ቀርቶ መታየት አልፈለገችም፡፡ ይህ ድርጊት ለሌሎችም ማስፈራሪያ በመሆኑ ሆስፒታሉ ባለሙያዎች እንዲቆዩና ስራቸውን በፍጥነት እያቋረጡ እንዳይሄዱ ለማድረግ አልቻለም፡፡ ተገልጋዩ ህዝብ በተለይም እናቶችና ሕጻናቶቻቸው በባለሙያዎች ተረጋግቶ ስራን አለመስራት ምክንያት የሚደርስባቸው የአገልግሎት እጥረት ምን ያህል እንደሚሆን መገመት ይቻላል፡፡ ይህንን ማስተካከል የማን ድርሻ ነው ሲባል ብዙ የሚመ ለ ከታቸው አካላት በመኖራቸው ልብ ሊሉ ይገባል ›› የሚል ማሳሰቢያ በጥናት አቅራቢዎቹ ቀርቦአል፡፡
ጉደር የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል በጥናት አድራጊዎቹ በሚዳሰስበት ወቅት የአካባቢው ፤የማዋለጃ ክፍሉ እና ማዋለጃው ንጽህና እና የተሟላ መሆን፤ የጨቅላዎች መቆያ እና መሳሪያዎቹ የተሟሉ መሆናቸው በጎ ነገር መሆኑ ተጠቁሞአል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የኦፕራ ሲዮን ክፍሉ ስፋትና ንጽህና እንዲሁም የተሟላ መሆን ለሌሎች ሆስፒታሎችም በምሳሌነት ሊጠ ቀስ የሚችል መሆኑ ተጠቁሞአል፡፡ አዋላጅ ነርሶቹ ከወሊድ አስቀድሞ ለእናቶች የሚ ሰጡት የተሟላ የምክር አገልግሎት እና ጥሩ የሆነ የመረጃ አያያዝ ይበል የሚያሰኝ መሆኑን ጥናቱን ያቀረቡት የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለሙያዎች የሆኑት ዶ/ር ደረጀ ለማ እና ዶ/ር ቶሎሳ ገልጸዋል፡፡   

Read 8070 times