Monday, 20 May 2019 00:00

የሜክሲኮ ሲቲ ነዋሪዎች አየር በመበከሉ ከቤት እንዳይወጡ ተነግሯቸዋል

Written by 
Rate this item
(2 votes)


                 በሜክሲኮ ሲቲ የአየር ብክለት በከፍተኛ ሁኔታ መስፋፋቱንና ለጤና አስጊ መሆኑን ተከትሎ፣ የከተማዋ ነዋሪዎች ከቤታቸው እንዳይወጡ ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ብሉምበርግ ዘግቧል::
የሜክሲኮ ርዕሰ መዲና አየር በዚህ ሳምንት በከፍተኛ ሁኔታ መበከሉ ያሳሰበው የአገሪቱ መንግስት፣ የከተማዋ ነዋሪዎች ከቤታቸው እንዳይወጡና መስኮቶቻቸውን እንዲዘጉ፣ ብስክሌተኞችና እግረኞች ደግሞ ፊታቸውን በጭንብል በመከለል ሳንባቸውን ከመመረዝ እንዲከላከሉ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል፡፡
ከአለማችን ታላላቅ ከተሞች አንዷ እንደሆነች የሚነገርላት ሜክሲኮ ሲቲ፣ በአየር ብክለት በከፍተኛ ሁኔታ ከተጎዱ የአለማችን ከተሞች አንዷ መሆኗን የጠቆመው ዘገባው፤ ለአየር ብክለቱ በምክንያትነት ከሚጠቀሱ ጉዳዮች መካከል ብዛት ካላቸው ተሽከርካሪዎች የሚወጣው በካይ ጭስ አንዱ እንደሆነም አመልክቷል፡፡
ከሰሞኑ የከተማዋ የሙቀት መጠን በመጨመሩና ዝናብ ባለመዝነቡ የደን ቃጠሎዎች በተደጋጋሚ መከሰታቸውንና ይህም  የአየር ብክለት ችግሩን በከፍተኛ ሁኔታ እንዳባባሰው የጠቆመው ዘገባው፤ የከተማዋ አየር ለጤና እጅግ አደገኛ በመሆኑ ነዋሪዎች ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱንም አክሎ ገልጧል፡፡

Read 1111 times