Print this page
Saturday, 30 March 2019 13:06

ዕጣ የወጣባቸው የኮዬ ፈጬ የጋራ መኖሪያ ቤቶች በሚቀጥለው ሳምንት ለባለዕድለኞች ይተላለፋሉ

Written by  ሠላም ገረመው
Rate this item
(8 votes)


           “በድሃ ገንዘብ የተሠራ ነው፤ ቤቶቹን ባለዕድለኞች ከማስተለለፍ የሚያግደን ነገር የለም” - ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ
                                     
                በወሰን ይገባኛል ውዝግብ እጣ ለወጣላቸው ዕድለኞች ያልተላለፉት የኮዬ ፈጬ የጋራ መኖሪያ ቤቶች በሚቀጥለው ሣምንት ለባለዕድለኞች እንደሚተላለፉ ተገልጿል፡፡
ቤቶቹን ለማስተላለፍ አስቸጋሪ ሆኖ በቆየው የወሰን ይገባኛል ውዝግብ ጉዳይ የህግ ችግር አጥንቶ እንዲፈታ የተቋቋመው ኮሚቴ፤ ውሣኔውን ሰሞኑን ያሳውቃል ተብሎ የሚጠበቅ መሆኑን የገለፁት የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኢ/ር ሠናይት ዳምጤ፤ የኮሚቴውን ውሣኔ ተከትሎ ቤቶቹን በአንድ ሣምንት ጊዜ ውስጥ የማስተላለፍ ተግባር ይከናወናል ብለዋል፡፡
በም/ከንቲባ ኢ/ር ታከለ ኡማ የሚመራውና ከኮዬ ፈጬ ጋር ተያይዞ የተነሳውን የወሰን ጥያቄ ለመመለስና ዘላቂ መፍትሔ ለማስቀመጥ የተቋቋመው የአስተዳደር ወሰን አጣሪ ኮሚቴ ስራውን ባለመጨረሱ የቤት እጣ ከወጣ ጀምሮ መተላለፍ የነበረባቸው ቤቶች ለባለዕድለኞች ሳይተላለፉ መቆየታቸውን ኢ/ር ሰናይት ተናግረዋል፡፡
በቀጣይ የሚኖረውን እጣ አወጣጥ በተመለከተ የቤቱ ግንባታ 30% ከተጠናቀቀ በኋላ ዕጣውን በማውጣት ያላለቁ ግንባታዎች እንደሚሠሩ የገለፁት ኃላፊዋ፤ ይህ የሚደረገው ባለ ዕድሎች ቤታቸውን ተከታትለው የማየትና የመቆጣጠር ሃላፊነት እንዲኖራቸው ታስቦ ነው ብለዋል፡፡
መመሪያው የሚፈቅደው 80 በመቶ የሚሆነው ተጠናቆ ከተሰራ በኋላ ቢሆንም 30 በመቶ ላይ ሳለ እጣ አውጥቶ 80% ሲደርስ ግን ለባለዕድለኞቹ እንደሚያስተላልፉ ተናግረዋል፡፡  
አያይዘውም ቀደም ሲል ከባንክ ጋር ውል የመፈፀም ስራ ይከናወን እንደነበር ገልፀው፤ አሁን ግን በቤቶችና ልማት አስተዳደር የባንክ ሒሳብ ገቢ በማድረግ ውል ለመፈፀም የሚያስችል አሠራር ተዘርግቶ መጠናቀቁን ኃላፊዋ ገልፀዋል፡፡
ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ትላንት በሰጡት መግለጫ፤ ዕጣው ለባለ ዕድሎች እንዲተላለፍ ታስቦ የተሠራ በመሆኑና የተሰራውም በድሃው ገንዘብ በመሆኑ ከመተላለፍ መስተጓጐል እንደማይገባው ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም የአስተዳደር ወሰን ማጣራቱ ከግለሰቦች የዕጣ አወጣጥ ጋር እንደማይገናኝ ተናግረዋል፡፡

Read 13563 times Last modified on Saturday, 30 March 2019 13:17