Print this page
Saturday, 09 February 2019 12:27

ታሪክ እራሱን ቢደግምም እድል የሚሰጠን ለአንድ ጊዜ ብቻ ነው ከሙሼ ሰሙ

Written by 
Rate this item
(4 votes)

  የዛሬ 9 ወር በምርጫ ዶ/ር አብይ ጠቅላይ ሚኒስቴር ያደረገው የኢህአዴግ ጉባኤን ተከትሎ  የተዋቀረው አዲስ ካቢኔ በኃላፊነት ስራውን ከጀመረ 6 ወር አስቆጥሯል፡፡ ካቢኔው ከተዋቀረ በኃላ በወቅቱ መነሳት  የሚገባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም፣ ሂደቱን ገና በጥሬው መፈተሸ ገንቢ አለመሆኑ ግልጽ ነበር፡፡ ሂደቱን በጥሞና ተከታትሎ በስራ ዘመን ውስጥ ምርትና ግርዱን መለየት የተሻ አካሄድ ስለነበር  ሹመቱን በራሱ ፋይዳ (Merit) ብቻ መፈተሸ አስፈላጊ ሳይሆን ቀርቷል፡፡ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስቴር ዴኤታዎችና ሌሎችም ተሿሚዎች ኃላፊነታቸውን ከታረከቡ ጀምሮ ለስድስት ወር ቦታቸውን ፈትሸዋል፣ እቅዳቸውን አቅደዋል፣ እቅዳቸውን ተግባራዊ አድርገዋል፡፡ ቢያንስ የአጭር ጊዜ እቅዳቸውን። ሹመት ያዳብር መባባሉን ገታ አድርጎ ከጫጉላ ቤት ወጣ ተብሎ ጉድ ጉድ ተጀምሯል፡፡ ዝግጅት ማድረጉ፣ እሳት ማንደዱ፣ ድስ መጣዱ በእሳት መፈጀቱ፣ ጭስ ጭስ መሽተቱና ወጥ መቀመሻው ጌዜ ላይ ነን፡፡ በዚህ ልክም ከሹመቱ ጀምሮ ዛሬ እንደ ሃገር የደረስንበትን ጥረትና ውጤት መፈተሽ ይገባል፡፡    
ስልጣን ወይም ሹመት አንዱና ዋነኛ መገለጫው መንግስታዊና አስተዳደዊ ጉዳዮችን በተቀላጠፋና በጠራ መንገድ ጊዜ፣ ጉልበትና ሃብት ቆጣቢ በሆነ ስልት ማከናወንና ሕዝብን ማገልገል ነው፡፡ ስልጣንን በውክልና የሚሰጠውና ከሰጠው ስልጣን የሚመነጨውን አገልግሎት ተጠቃሚ የሆነው ሕዝብ የተሿሚውን ሙያዊ ችሎታ (ክህሎት)፣ ለሃገርና ሕዝብ ያለውን ታማኝነት፣ ፍትሐዊነት ተንተርሶ ምን ያህል ለቃል ኪዳናቸው ታማኝ እንደሆኑ መፈተሸ እንዲችል ግልጽነትና ተጠያቂት እውን ማድረግ ይገባል፡፡ ዜጎች ሹመኞችን ከሹመታቸው ጋር በተያያዘ በግላጭም ሆነ በድብቅ ሊተቻቸው፣ ሊመዝናቸውና ሊፈትሸው እንዲችል አስፈላጊውን ሁሉ መረጃ በቅርበት እንዲያገኘ ሁኔታዎች ማመቻቸት ይገባል፡፡ ለዚህ መሳካትም በእቅድ የተያዙና እየተተገበሩ ያሉ የተሿሚዎች የ6 ወር ግምገማዎች እንዲሁም በጀት ከአፈጻጸምና ከውጤት ጋር እየተቀናጁ የሚመዘኑባቸው ሰነዶችና ወይይቶች ሕዝብ እንዲያውቃቸው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
ዜጎች በመረጃ ላይ ተመስርተው በጎውን የማበረታታትና ጥፋቶች እንዲታረሙ የማድረግ  በዛው መጠን ደግሞ ግዴታቸወን በአግባቡ የመወጣት ልምድ እንዲያዳብሩ ማገዝ ሃገራቸችንን ሕዝባችንን ከብዙ ውጣ ውረድና ለፍቶ መና ከመሆን ያድነዋል፡፡ ግልጽነት በሌለበት ሁኔታ ሹመኞችን አግባብ ባለው መንገድ ለመውቀስም ሆነ ለማረም ወይም ለማበረታታት አይቻልም፡፡ መረጃም ሆነ ማስረጃ በሌለበት ሁኔታ መረጃ የሚሻ አዕምሮ ወቀሳ ትችትና ጣት መቀሰርንና አሉባላታን ቢያስቀድም የሚደንቅ አይሆንም፡፡  በቂ መረጃ በሌለበት ከእውነታው ይልቅ በጓሮ በር የሚገባ ሃሜትና አሉባልታ ባለስልጣናትን ለማብጠልጠለም ሆነ ለማስጠላት አገልግሎት ልይ ስለሚውል ከባለስልጣናቱ ስራና ሃገራዊ ፋይዳ ይልቅ ግለሰቦቹ መነጋገሪያ ርዕስ መሆናቸው አይቀሬ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በተራው ተስፋ መቁረጥ ያስከትላል፣ ተነሳሽነትና ቁርጠኝነትን ያመክናል። ግልጽነጽና ተጠያቂነት ለሃቀኛ ወቀሳና ትችት መተራረም በር ይከፍታል፣ ድብቅነትና የመረጃ ንፉግነት ግን ለአሉባልታና ለሃሜት ይጋልጣል፡፡ ቅድመ መረጃና ማስረጃ በቀረበበት ሁኔታ ዜጎች በገሃዱና እውነታ ላይ ተመርኩዘው ለመነጋገርም ለመተራረም እድል ሊፈጥር ይችላል፡፡ ግምገማ ወይም ምዘና ለጊዜያዊ ጭንቀት ሊዳርግ ቢችልም ግልጽነትና ተጠያቂነት እስካለ ድረስ ግን በመረጃ ላይ የተመሰረተ ግምገምም ሆነ ምዘና ሃገርና ሕዝብ ከጠቅላላ ውድቀታና ኪሳራ ሊታደግ እንደሚችል ግን ጥርጥር የለውም። ለዚህ ሲባል ዜጎች በራሳቸው ጉዳይ በተለይ ደግሞ መሰረታዊ ፍላጎቶቻቸውን ለማሟላትና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ሲባል በሚተገበሩ እቅዶች ላይ ንቁ ተሳተፊ የመሆኑ፣ የመከታተልና እርምት እንዲወሰድ የማድረግ አሰራር መለመዱ ጠቃሚ ነው፡፡  
እስከዛሬ ካልተሻገርናቸውና ልንሻገራቸው ከሚገቡ የዲሞክራሲያዊ  ስርዓት መገለጫዎች መካከል አንዱ ግልጽነት ነው፡፡ ይህንን አስመልክቶ በጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር አብይ በኩል መነሻ ግልጽነትን የማስፈን መርህ ተግባራዊ እንደሚሆን ተደጋግሞ የተነሳ ቢሆንም ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶለት ቀልጥፎ ወደ ተግባር አልተገባም፡፡ አሁንም ሳይውል ሳያድር ወደ ተግባር መገባቱ  ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ ጠቀሜታው የጎላነው፡፡
አንጻራዊ በሆነ ምልከታ በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ውስጥ የሚገኙ ሃገራት ልማታቸው፣ እድገታቸውና ሰላማቸው የተረጋገጠው ጠንካራና ብቁ መሪዎች ስነበሯቸው ብቻ አይደለም፡፡ ወሳኙ የነበረው ጉዳይ ሕዝብን ለማገልገል ስልጣን የተሰጣቸው ሹመኞችና ኃላፊዎች ስራቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ለማስቻል ሙያዊ ብቃት ከማላበስና ሁለንተናዊ ደጋፍ ከመስጠት ባሻገር ለገንቢ ትችት እራሳቸውን እንዲያዘጋጁና  ከመጋረጃ በስተጀርባ ከዘረጉት የህልም ዓለም ወጥተው በሰሩት ልክ ዜጎችን በገሃዱ ዓለም እንዲጋፈጡ በማድረግ  ጭምር ነው፡፡     
ማንኛውም ተሿሚ በዜጎች ስም ቃለ መሃል ፈጽሞ የስልጣን መንበር ላይ ሲቀመጥ ሙያዊ ክህሎቱ፣ አስተዳደራዊ ብቃቱ፣ ለሕዝብ ያለው ታማኝነት፣ ከወንጀልና ከግፍ እጁ የጸዱ መሆኑ ሊመረመርና ሊፈተሸ ይገባዋል። ላይ ላዩን ሲታይ ይህ ጉዳይ የሕዝብ የእለት ተዕለት ስራ ላይመስል ይችላል፤ ነገር ግን ሕዝብ የማይስማማበትን መሪ የመቃወም ወይም ታርሞ ብቁ እንዲሆን የማድረግ መሰረታዊ የሞራል ኃላፊነትና ግዴታ የሕዝብ መሆኑን አለማመን ደግሞ የአምባገነንነት ጉዞ ሀ.. ሁ ወይም የ እውር ድንር ጉዞ ነው፡፡ ተሿሚዎችም ሹመት የፈተዎች ሁሉ መጀመርያው እንጂ የፈተናዎች ሁሉ መጨረሻ አለመሆኑን በቅጡ መረዳት አለበቸው፡፡  በተለይ እንደ ሃገራችን ባሉ የድሃ ድሃ ሃገሮች፡፡
ማንኛውም ተሿሚ የቱንም ያህል እጅግ የላቀ የፓርቲ ድጋፍ ቢኖረው፣ የብሔሩን ወይም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ይሁንታና ተቀባይንት ቢቀዳጅ  በሕዝብ ፊት ዓይን የማይሞላና የሕዝብን ቀልብ የማይገዛ ከሆነ  ለራሱም፣ ለመረጠውም ሆነ አገለግለዋለሁ ለሚለው ሃገር፣ ማህበረሰብና ስርዓት ውድቀት ከመሆን አይድንም፡፡ ዜጎች ይሁንታ ያልሰጡት ሹመኛ የዜጎችን ሁለንተናዊ ድጋፍ ስለማያገኝ ስራው ጋሬጣ የበዛበት፣ ተቀባይነትና ውጤት የሌለው ይሆናል። ዜጎች ስንል እንግዲህ በስሩ የሚያስተዳድራቸው ሰራተኞች እንደሚያካትት ልንዘነጋ አይገባም፡፡
ከላይ ያስቀመጥኩት መሰረታዊ መነሻ ሃሳቤን እንደመንደርደርያ ወስደን ከዘጠኝ ወራት በፊት ወደ ተሰጡት ሹመቶች ስንመጣ፣ በርካታ አበረታች ጉዳዮች የታዩበትን ያህል ቀላል የማይባሉ ጥያቄዎችን ያስነሱና ያወዛገቡ እንደነበር አይረሳም፡፡ እኔም እንደ አንድ ዜጋ በመርህ ደረጃ በሹመት አስፈላጊነቱ ላይ እምነትና ጥርጥር ባይኖረኝም በርካታ በዓዕምሮዪ የሚጉላሉ ጉዳዮች ነበሩኝ፡፡
ከዚህ ሹመት ቀደም ሲል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ (ዶ/ር) ወደ ጠ/ሚኒስትርነቱ እንደመጡ የሰጡት ሹመት የተሟላ እውቅናና ድጋፍ ከፓርቲያቸው ሳያገኙ ስለነበር በርካታ ጥርጣሬዎችና ፈራ ተባዎች እንደነበሩበት በተከታታይ የተወሰዱት ሹም ሽረቶችና ሽግሽጎች ምስክር ናቸው፡፡ ይህ ደግሞ ወቅታዊ ችግርን ለመፍታታት ተብሎ በአጭር ጊዜ ውስጥና በቀለጠፈ ሁኔታ፣ “እንደተሰማው” በተለይ ጥቆማን  (Recommendation) ማዕከል አድረጎ የተከናወነ ስለነበር ጉድለቱ የሚጠበቅ ነው፡፡
ሊገመት እንደሚችለው ሹመቱ ያጠነጠነበት አጀንዳ በአንድ በኩል የተጀመረውን ለውጥ እንዳይቀጭ በማደረግ በሌላ በኩል ቀጣይነቱንም ማረጋገጥ ማዕከል በማድረግ ያለ በቂ ቅድመ ዥግጅት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ወሳኝ ቦታዎች ላይ የተቀመጡትን የቀድሞ ሹመኞችን እንደተጨባጭ ሁኔታው መገለል ያለባቸው በማግለል፣ መተካት ያለባቸው እንዲተኩና ሙሉ ለሙሉ መወገድ ያለባቸውንም እንዲወገዱ በማድረግ የተሰራ መሆኑን ግልጽ ነበር፡፡ ሹም ሽሩ አንጻራዊ በሆነ መልኩ ሁለገብ ሕዝበዊ ስምምነት ባያገኝም፣ በተለይ አፍረሽ ኃይሎች መወገዳቸው ቅድሚ የሚሰጠው አጀንዳ በመሆኑና እርምት የሚፈያስፈልጋቸው ጉዳዮችን ተረጋግቶ ማረም እስኪቻል ድረስ በትንፍሽ መውሰጃነትና በሽግግር መፍትሔነት ተቀባይነት አግኝቷል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ ሌላው ስምምነት የተቸረው ጉዳይ አበው እንደሚሉት በድሮ በሬ ያረሰ የለምና? አሁን የተካሂደው ሹም ሽሩ የተጀመረውን “ለውጥ ለማስቀጠል” ወይም አዲስ በመካሄድ ላይ ያለውን የአሰራር ለውጥ ለማስቀጠል “ጠቃሚ” የሆኑ ሰዎችን ወደ ስልጣን ማምጣት ስለሚያፈልግ፤ ይህንን ማድረጉ በራሱ በቂ ምክንያት መሆኑን ሃገራዊ ስምምነት ስላገኘ ነበር፡፡
በርካታ ሽም ሽሮችን እያስተናገድን ከዘጠኝ ወር በላይ አሳልፈናን፡፡ አሁን ሹም ሽሩ ቀጥሏል። በአስፈላጊነቱ ዙርያ ከሞላ ጎደል ይህንን ያህል ማለት ከቻልን፤ ዛሬ ላይ በምን ሁኔታ ላይ እንገኛለን ወደሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ልንዞር ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ከስድስት ወር ወዲህ የተካሄደው ሽም ሽር፤ ላለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት ትግል ሲካሄድበት የነበረውን ሹመት በብቃት ወይስ በብሔር አሊያም በቡድነኝነት ወይም በኮታ መሆን አለበት የሚለውን ውዝግብ  የሚያረካ መልስ ሳይሰጥ እንደተጠናቀቀ መገመት ይቻላል፡፡
አንድ የማይካድ ነገር አለ፡፡ ከዚህ በፊት ፍጹም ወደ አንድ ብሔር ወይም ፓርቲ ያጋደለውንና  ፍጹማ በሆነ መልኩ አድልዎ ይታይባቸው የነበሩ ከኢኮኖሚና ከፖለቲካ ውሳኔ ሰጭነት ጋር የተያያዘ ግንባር ቀደም  ቦታዎችና የደህንነት ሚና የነበራቸው የሹመት ቦታቸዎች በአንድ ብሔር ተይዘው የማይደፈሩ ይመስሉ እንደነበር አልቀጠሉም፡፡ የሹመት ቦታዎቹና ሹመኞች በአዳዲስ ሹመኞች ተተክተዋል፡፡ አንዳንዶቹም ወንበሮቹን ተጠቅመው ለሰሩት ግፍ፣ አድልዎና ለፈጠሩት ውድመት እንዲጠየቁ ወደ ፍትሕ ስርዓቱ ተላልፈዋል፡፡ ወደፊትም በተለይ ለአንድ ብሔር/ ብሔረሰብ ወይም ቡድን/ ፓርቲ በኮታነት የሚሰጥ ቦታ እንደማይኖር እንደ ሕዝብ ተስፋ እናደርጋለን፡፡   
ይህ እንግዲህ እስከዛሬ ኢትዮጵያን አድቅቆና ቀፍድዶ ከያዛት በእውቀት፣ በችሎታ፣ በታማኝነት፣ ሕዝብን በማገልገል፣ እራስን በማብቃት ከመመረጥ ይልቅ የፓርቲና የብሔር ማንነትን በማቀንቀን፣ በጥገኘነት፣ እንደፊውዳሉ ስርዓተ ማህበር ሹመት በደምና በአጥንት ይገኝ የነበረበትን አሰራር ወደ መቃብር የሚወስድ ጅምር ሊሆን ይችላል የሚል እምነት በስፋት እንድንሰንቅ የሚያደርግ ነው፡፡
የብሔር ማንንት ወይም ደምና አጥንት ቆጥሮ መሾምን፤ የፓርቲ አባልነትና ታማኝነት ብቸኛ መስፈርት አደርጎ ዜጎች አገራቸውን በብቃታቸውና በችሎታቸው ማገልገልን እንዳይችሉ መብትና ግዴታን የሚነፈጋቸው አሰራር  አጥፊነት ተረድቶ ከዚህ ስህትትና የጥፋት ጎዳና ፈጥኖ መማር አለመቻሉ ውጤቱ ዜር ድምር እንደሚሆን ጥርጠር አልነበረውም፡፡ የከፈልነውና እየከፍለን ያለውም ቁሳዊና የሞራል ኪሳራም የዚሁ መገለጫ ነው፡፡ ዛሬም ላይ ከሃገር በላይ ለፓርቲ መቆርቆርና ለቡድን ታማኝ መሆን፣ በእገሌ ወይም በእገሊት ስብስብ ውስጥ መቧደን ለሹመት መስፈርት ሆኖ መወሰዱ ለአገራችን ፈተና ሆኖ እንደሚቀጥል ምልክቶች አሉ፡፡ ከሰው መርጦ ለሹመት ከእንጨት መርጦ ለታቦት የሚባልበትን ኃላ ቀር ምዕራፉ ለምዕተ ዓመት ያክል ተዘግቶ የቆየ ቢሆንም በኢህአዴግ ዘመን እንደገና አገርሽቶ ላለፉት ሃሳ ሰባት ዓመታት ከብሔርና ከፓርቲ መርጦ ለስልጣን ወደ ሚባልበት ዘመን ተመልሰን ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ ከቡድንና ከቲፎዞ፣ በተለይ ከብሔር መርጦ ለሹመት እንዳያደናቅፈን ማስተዋል አለብን፡፡  
ሌላው መልካ ጅማሮ በርከት ያሉ እድሜያቸው በጎልማሳነት ውስጥ የሚገኙ ተሿሚዎች ወደ ከፍተኛ የስልጣን እርከን መምጣታቸው እሰየው የሚያሰኝ እመርታ መሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡ ነገር ግን  የስልጣን፣ የሃገርና የትውልድ ባለቤትነት ሽግግር ካረጁ አይበጁም ት ላይ ተመስርቶ መሆን የለበትም። ፈጥኖ መለወጥ አለመቻል፣ ተቸካይነት፣ ወደ ኃላ መጎተት አንድንዳ በእድሜያቸው በገፉ ሰዎች ዘንድ በመገለጫነት ሊወሰድ ይችል ይሆናል፣ በተቃራኒው ደግሞ ብስለት፣ አስተዋይነት፣ እርጋታ፣ የዳበረ ክህሎትና ልምድ የረጅም ጊዜ ተሳትፎ ውጤት መሆናቸው ላይ ግንዛቤ ተወስዶበት ይህንን ሃገራዊ እምቅ አቅም በአግባቡ ለመጠቀም እድል ሊሰጥ ይገባል፡፡  
በእድሜ የገፉትን አውራ ዜጎች ከፍተቶች መሞላት ተገቢ የመሆኑን ያህል ወደ ስልጣን የሚመጡት አዳዲስ ኃይሎችም ብቃትና አቅማቸው፤ ያለፈ ውጤታማም ሆነ ደካማ ተሞክሯቸው በሕዝብና በተግባር የተመሰከረላቸው መሆኑን ማረጋገጥደግሞ የዛን ያህል ወሳኝ ጉደይ ነው፡፡ ሽግግር ሁልጊዜም ፈታኝ ሂደት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ስልጣን የሚመጡት “ትኩስ ሃይሎች” ቀጣይ “የሽግግር ዘመናችንን” አስተማማኝ በሆነ መልኩ መወጣት የሚችሉና “ሽግግሩን” በተደላደለ መሰረት ላይ በማስቀመጥ ሂደቱ እንደ ወንዝ በማያቋርጥ ፍሰት ውስጥ የሚንኳለል መሆን ማረጋገጥ መቻል አለባቸው፡፡ ከዚህ አኳያ የተሿሚዎቹ ጎልማሳነት ጠቃሚ ቢሆንም በትውልድ መሐል ድልድይ በመሆን ሽግግርን የማቀባባልና ቀጣይነቱን የማረጋገጥ አቅማቸው ላይ ግን ጥርጠሬ አለ፡፡ አስተማማኝ መሰረት የዘረጉና ወደ ፊት መራመድ የሚችሉ ተሿማችን ማሽቷል ብንችልም፣ ከስድስት ወር በኃላ ዛሬም በእቅድ ውስጥ የሚዳክሩ፣ መያዢያን መጨበጫ የጠፋቸው፣ የሕዝብን ዓይን ለማየት ያለደፈሩ፣ ከስራና ከውጤት ይልቅ ብሔር፣ ደምና አጥንት ያጎናጽፋቸውን ካባ ከለላ አድርገው በባዶ ሜዳ የተኮፈሱ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ከስድስት ወሩ ግምገማ በኃላ  ፈጣን መልስ  የሚሹ ጉዳይ ናቸው፡፡    
ሹም ሽረቱ መልካም ከሆኑ ጎኖቹ መካከል አንዱ ግማሽ ያህሉ ተሿሚዎች አንስታይ ጾታ ያላቸው መሆናቸው ነው፡፡ ሴቶች በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ድል ያልተሳተፉበት፤ በጀግንንት ያልወደቁበት ዓውድ የለም፡፡ በወታደራዊ ተሳትፏቸውም ቢሆን አንቱ የሚባሉ ጀግኖችን ያፈሩና ከፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም አስተሳሰብ ከሚመነጭ ጥንካሬ በመነሳት በኢህአፓ፣ በመኤሶን፣ በደርግ/ኢሰፓ፣ በኢህአዴግና በኦነግ እንዲሁም በሌሎች ፓርቲዎች አርማና መፈክሮች ስር ተሰልፈው ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉ መሆናቸው ዛሬም ድረስ ከማናችንም አዕምሮ የተሰወረ ጉዳይ አይደለም፡፡ ይህም ሆኖ ግን፤ ከድል በኃላ ሴቶች በሰላማዊ የትግል ዘመን ስልጣንን ተረክበው መምራትናና ማስተዳደር ላይ ስር በሰደደ ደረጃ ተገድበው ነበር፡፡ ይህንን ሃገራዊ ፈተናና ማነቆ ከትብታቡ የፈታ እርምጃ መወሰዱ ለሁላችንም ኩራት ነው፡፡
በአዲሱ የካቢኔ ውስጥ የሴቶች ተዋጽኦ ከፍተኛ እመርታ አሳይቷል፡፡ ለዚህም  ዜጎች በነቂስ ወጥተን ሹመት ያዳብር በማለት ድጋፋችንን ቸረናል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ሴቶች በሹመት ተገቢውን ቦታ የማግኘታቸው ጉዳይ የረጅም ዘመን የትግላቸው ውጤት መሆኑን መቀበል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው። መታዘብ እንደሚቻለው ግን የደረስንበት ዘመንም ሆነ ወቅት ለውጡን የግድ የሚል መሆኑን ከመቀበል ይልቅ ከሂደቱ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚደረገው ቁፋሮ በተቃራኒው ሴቶችን አሁንም ጥገኝ የሚያደርገና ግንባር ቀደም ተጋድሏቸውን የሚኮስስ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ሰጭ ካለ ከላካይ  ውሎ አደሮ ወይም ዘግይቶም ቢሆን ሊመጣ እንደሚችል መገመት ያስፈልጋል፡፡ ይህንን አይነት ኃልዮሽ ጉዞ ለመፋታት ለውጡን ከፓርቲ ገድልነት አውጥቶ ተቋማዊ ቅርጽ መስጠት ተገቢ ነው። ቀጣይነቱ ሊረጋገጥ የሚችለው በዙህ መንገድ ብቻ ነው፡፡
በተቃራኒው ደግሞ በስልጣን መዋቅሩ ውስጥ የሴቶች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩ ብቻ የተባዕት ተጽእኖ የተንሰራፋበት ሃገር ወደ እኩልነት የሚደረገውን ጉዞ በራሱ ብቻ የተሟላ እንደሚያደርገው በማስላት ሚዲያዎች ከዚህ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት አበክረው መስራታቸውም ስህተት ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ኢህአዴግም ውሎ አድሮ በተለይ ደግሞ ምርጫን ተከትሎ ወደ እውነተኛ ባህሪው/ ገጽታው ሲመለስ ለምርጫ መወዳደርያ ሲል ሂደቱን የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ማሟያትና የሴቶችን ድምጽ ለማግኘት መጠቀሚያ ሊያደርገው ስለሚችል የሚዲያው ዘገባው በዚህ ጉዳይ ላይ ጥንቃቄ ሊያደረግ ይገባል፡፡
ሹመት ወይም የስልጣን መንበር በራሱ ጊዜ ሴቶችንም ሆነ ወንዶችን ሙሉና ብቁ አያደርጋቸውም፡፡ በተለይ ለረጅም ዘመን በጾታቸው ምክንያት ብቻ ሲገፉ የነበሩ ሴቶች ዛሬም ላይ ገና ከጾታ ትምክህት፣ ከባህልና ከሃይማኖት ተጽእኖ ካልተላቀቁ ሃይሎች ጋር ትግላቸው ተጀመረ እንጂ አልተጠናቀቀም። የወንድ የበላይትና ትምክህቱ፣ ሴቶች ማሳነሱና ማቃለሉ ፈተና ሆኖ መቀጠሉ አይቀሬ ነው፡፡ እነዚህ ሃይሎች በየዘርፉና ባገኙት እድል ተጠቅመው ፈተና ለመደቀን መፍጨርጨራቸውና ለማሰናከል መሞከራቸው የሚጠብቅ መሆኑን ተገንዝቦ የታሪክ አዙሪትን ከመስመር እንዳይወጣ በተግባር በመታገልና በውጤት ማቃናት ያስፈልጋል፡፡ በጥቅሉ ተቃዋሚዎች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፣ ልሂቃንና ጉምቱ ዜጎች ትኩረት ሊሰጡት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡     
ወደ መነሻ ግምገማዬ ስመለስ ዛሬስ ከስድስት በኃላ ተሿሚዎች ምን ይህል በተግባር ውጤትን አስመስክረዋል፡፡ ማህበረሰባዊ ተጽእኖው ተሻግራ ምን ያህል  ከተበተባቸው ድርጅታዊ አሰራር ማላቀቅና ሃገርን መስቀደም ችለዋል? ሃገራችን ከተደቀኑባትና በቀጠይ ከሚደቀኑባት ፈተናዎች ለመታደግ ምን ይህል አስተማማኝ መሰረት ጥለዋል? የስድስት ወር የሥራና ውጤት ግምገማው መልስ የሚሰጠን ጉዳይ ይሆናል። ተሿሚዎቹ እራስን በማብቃት እረገድ የተጣለባቸውን ኃላፊነትና አደራ በብቃት በመወጣት ለቀሪዎቹ የጾታ አጋሮቻቸው ምሳሌ ለመሆን ችለዋል ወይ? የሴት ተሿሚዎች ቁጥር የኮታ ወይም የችሮታ ሳይሆን የብቃትና የመቻል ወይም ሆኖ የመገኘት መሆኑን ለማረጋገጥ ማንኛውንም ፈተናና መሰናክል በማለፍ ሰርተውና አሰርተው በውጤት ለውጡን ለማረጋገጥ ምን ያህል ርቀት ሄደዋል? እንዚህ መሰረታዊ ትያቄዎች ናቸው፡፡
ሹመቱ የፈጠረውን እኩልነት በሙሉ ልብ መቀበል የሚችሉ በርካቶች የመኖራቸውን ያህል ታሪክ በነበረው መንገድ ሂደቱ እንዲቀጥል የሚፈልጉ፣  ከግራም ሆነ ከቀኝ  በርካታ ነባርና አዲዲስ ፈርጀ ብዙ ፈተናዎችና ችግሮችን በመቀፍቀፍና በመደቀን ሂደቱን ፈተና ላይ የሚጥሉ ኃላ ቀሮች ሊኖሩ እንደሚችሉ ከግምት ውስጥ ማስገባት ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ፍቱን መድህኒቱ ሁላችንም እንደዜጋ በአንድነት መንፈስ ተገቢውን ድጋፍ ለተሿሚዎች በተገቢውን ቦታና ጊዜ በመስጠት፣ ተሿሚዎቹ መተቸትም ማጠነከርም ይጠበቅብናል፡፡ ተሿሚዎቹ ደግሞ ወገባቸውን ጠበቅ በማድረግ ብቃትና ውጤት አጣምረው በማስመዝግብ የለውጥ ጅማሮውን ከሃዲዱ እንዳይወጣ ሰላማዊ መስዋእትነት እውን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
እርግጥ ነው አንድንድ የሚኒስቴር መስርያ ቤቶችና  መንግስታዊ ተቋማት ጓዳ ጎድጓዳቸው በርካታ ውስብስብ ችግር ቀፍድዶ የያዛቸው እንድሆኑ ይታወቃል፡፡ አንድንዶቹ ለብሔሮ ተሳትፎ ሲባ ብቃትና አቅ ሳይኖር አንድ ብሔር አባልት እየተፈራረቁ ስለ ነገሱበት እቅድ ሳኖራቸው፣ ስራ ሳያከወንባቸው ዛሬ ላይ የደረሱ ናቸው፡፡ በእግራቸው እንዲቆሙ ሰፊ ጥናት፣ ቅድመ ዝግጅና ሁለገብ እገዛና ድጋፍ ይጠያቃሉ። ለለውጥም በቂ ጊዜ ይፈልጋሉ። አንድንዶቹ መስርያ ቤቶች ደግሞ በሕግና በመርህ አስፈላጊ መስርያ ቤቶች መሆናቸው ቢታወቅም የፓርቲ ፓራሳታታሎችና የልማት ድርጅቶ አንድንድ የግል ተቋማትም በደባልነት ተመድበውባቸው ስራቸውን ስለሚሰሩባቸው መስርያ ቤቶቹ ለመኖር ሲሉ ይኖሩ እንደነበር ይታወቃሉ፡፡ እነዚህ መስርያ ቤቶችን ማጠናከር የሚቻለው መጀመርያ ደባሎቻቸውን በማፍሰረስ ነው፡፡ ቀጥሎ የደባሎቻቸውን ጥቅም የሚነካ ውሳኔ እንዳይመሰንን ሽባ አደርጎ ለማስቀመጥ ሲባል ከደባሎቻቸው እየተመረጡ የተሸሙትን በቦርድ አመራርነት በማሰናበት ስራቸውን በአግባቡና በበላይነት( Authority) እንዲሰሩ ማድረግ ያፈልጋል፡፡ እነዚህ ጉዳዮች ወስብስብ በሆነ በድብቅና በሚስጥር የተከናወኑ ተጋባሮች ስለሆኑ  መስርያ ቤቶቹን በቅጡ መፈተሸ የጥቅም ግጭት ያለባቸውን ቦታዎች ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡
ለውጥ የሚፈጥረው መነቃቃት በአግባቡ ካልተያዘ ለዜጎች መብት እንታገላለን የሚሉ ኃይሎች የሌሎችን መብት በሚጥስና ሰላምና መረጋጋትን በሚያውክ መልከ ሊጠቀሙበት ይችላሉ፡፡ ይህ ችግር ሃሳብን ከመግለጽ አልፎ በአንድ-አንድ አካባቢዎች የዜጎችን ሕይወት እስከመቅጠፍና ንብረት እስከማውደም እየደረሰ እንደሆነ እየሰማን ነው፡፡ የዜጎችን ሰላምና ደህንንት ማስጠበቅ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገበ ጉዳይ በመሆኑ መንግስትን ወክለው የተሾሙ ኃላፊዎች ሚናቸውን በአግባቡ መወጣት አለባቸው፡፡
ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የስርዓተ አልበኝነትና የጥፋት በር መክፈቻ መድረክ መሆን የለባቸውም፡፡ መብትም ቢሆን ብቻውን የሚከሰት ጉዳይ አይደለም በርካታ መገለጫዎች አሉት በተለይ ደግሞ ከግዴታ ጋር የሚመጣ ፓኪጅ መሆኑን መዘንጋት አይገባም፡፡ ሃሳባን በነጻነት መግለጽ ቃላቶች አምረውልኛል በሚል ወይም የሚደግፈኝና የሚወደኝ ስላሉ መናገር አለብኝ ከሚል ከንቱ ውዳሴ  የሚነሳ መሆን የለበትም፡፡ ሃሳበን በነጻነት መግለጽ ስርዓት፣ ቦታና ጊዜ አለው፡፡ ዜጎች ስጋት እስኪገባቸውና ደማቸው በከንቱ እስኪፈስ ድረስ ሹመኖች ኃላፊነታቸውንና ስራቸውን መዘንጋት የለባቸውም፡፡ የመንግስታዊ ኃላፊነትን በይሁንታ ሳይሆን በሕግ አግባብ የመፍታት አሰራና ባህል ተጠናክሮ መቀጠል አለበት፡፡
ከፊታችን ምርጫ ወቅት እየገሰገሰ ነው። ስጋቶችም ሆነ ተስፋዎች ተሰንቀዋል፡፡ ሃገራቸን ከፍተኛ የአመራር ብስለትና ችሎታን የሚጠይቅ ሁኔታ ላይ ትገኛለች፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚሰጧቸው አስተያየቶች ሕገ ወጥና አሉባልታን መሰረት ብቻ ያደረጉ እስካልሆኑ ድረስ የዴሞክራሲያዊ መብት መገለጫዎች በመሆናቸው መገደብ የሌለባቸውን ያህል ስርዓተ አልበኝትና ሕገ ወጥነት ገደብ ሊበጅለት ይገባል፡፡ በየክልሉና በስደተኛ  ሚዲያዎች ላይ የምንመለከተው ቁረጠው ፍለጠው መቆም አለበት፡፡ ሚዲያዎቹ ላይ የሚሰጡት አስተያየቶች መብት የመሆናቸውን ያህል የሌሎችን ጥቅም እየተጋፉ፣ አለመረጋጋትን እየሰበኩ የሚከናወኑ ከሆኑ መንግስት በሕገ ወጥነትና ሃሳብን በነጻነት መግለጽ መካከል ያለውን ልዩነት በቅጡ መዝኖ ችግሩን በሕግ አግብብ እንዲፈታ ማድረግ አለበት፡፡ በተለይ በየሚዲያው ላይ የመንግስት ሹመኞች ተሳትፎ መቀነስና አማራጭ ሃሳብ አለመቅረብ ብዙ ጉዳዮች ከመስመር እንዲወጡ በር እየከፈተ ነው፡፡ ሹመኞች በስፋት ወደ መድረክ እየቀረቡ ሚዛናዊ ዘገባ እንዲኖር የተጋነነው በልኩ እንዲዘገብ፣ ሃቁ እንዲወጣ ግዴታቸውን መወጣ አለባቸው፡፡
ዜጎችም ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ሲጠቀሙ ግዴታቸውን መርሳትና ከመስመር በመውጣት የሌሎችን መብት መንካት እየተለመደ መምጣቱ መንግስት የለም ወይ የሚስብል ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡
ዜጎች መብታቸውን ለመጠቀም የሚተጉትን ያህል የሌሎችን መብት ካላከበሩ ከአንደበታቸው የሚወጣውና ድርጊታቸውንና ሰለባ እንደሚደርጋው የሚጠበቅ ነው፡፡ ይህንን እድል በተደራጀ መልኩ ለመጠቀም አቅም ያለው  ኃይል አንድነታቸውን በመከፋፈልና በሃሰት ፕሮፓጋንዳ እርስ በርሳቸው በጥላቻ እንዲጋጩ በማድረግ ወደ ለግጭትና ለሕይወት መጥፋትና ለንብርት ውድመት ሊዳርጋቸው ይችላል፡፡ የዜጎችም ሆነ የፓርቲዎች ንቁ ተሳትፎ የሚለካው ለተሳትፎው ባባከኑት ጊዜና በዥጎደጎዱት ሃሳብ መጠን ሳይሆን መብትና ግዴታቸውን አውቀው የጨዋታው ሕግጋት ጠብቀው የሌለውን መብት ሳይነኩ በስርዓት ሃሳባቸውን ማካፈል በቻሉት መድረክ ልክ ብቻ መሆን አለበት፡፡ ለዚህም የመንገስት ሹመኞች ሚና በእጅግ ያስፈልጋል። ባለስልጣኖችን ከጫጉላ ቤታቸው መጥተው ገሃዱን ዓለም መቀላቀል አለባቸው፡፡
በፖለቲካዎ መስክ ሃገራችን ያለችበት ሁኔታ ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻል እያሳየ ነው፡፡ ከሞላ ጎደልም ቢሆን ከመፍረስና ከመበታተን የስጋት ደመና እየተላቀቅን ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቀላሉና በእድል የተገኘ ውጤት እንዳልሆነ ጠንቅቅን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ከተመክሮ እንደምንማረው በለወጥ ሂደት ውስጥ የሚገኝ ሕዝብ የደረሰበት በደልና ያሳለፈው መከራ ምሬት ወዴት ሊመራው እንደሚችል መገመት አዳጋች ነው፡፡ ከቀይ ሽብር ጋር በተያያዘ በደርግ ዘመን ስልጣንን የግል ሃብት በማድረግ ግለሰብዊ ቂም በቀልንና ጥላቻን ማዕከል አድርገው  ዜጎችን በመግደል፣ በማሰር፣ በማሰደድ ተጀምሮ የሰው ሃብትና ትዳርን በመመኘት ቤተሰብን እስከመበትንና ሰዎችን ደብዛ እስከማጥፍት የደረሰ ከፍተኛ የሆነ ሁሌም በጸጸት የሚወሳ ኢሰብአዊነት የተሞላበት ወንጀል ሲፈጸም ተመልክተናል፡፡ በሩዋንዳ በሰርቢያ… በሌሎችም ሃገሮች ከዚህ የከፋ ድርጊት ታዝበናል፡፡
ዛሬ ያለንበት ሁኔታ የተለየ ሊመስል ይችላል። የተለየ ከሆነ የተለየ ሊያደርገው የሚችለው መንግሰት ከነባለስልጣኖቹ ኃላፊነታቻን በብቃትና በኃላፊነት መንፈስ ሲወጡ ብቻ ነው። ኢኮኖሚያዊ ድቀት መዘዙ ብዙ ነው፡፡  
ዛሬ የምንገኝበት አንጻራዊ ሰላም ኢትዮጵያውያን ለውጥን በተሻለ መረጋጋት ለማስተናገድ የሚያስችል አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየገነባን እንደመጣን የሚያሳይ አመላካች ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ገና ወጥተን ያልጨረስነው ዳገት የለም ለማለት አይደለም። የለውጡ ጅማሮና አጋማሽ ላይ ሂደቱን ተከትሎ ቅጥ ባጣ መልኩ ዜጎች ሕይወታቸውን አልነጠቁም ንብረታቸውን አልተዘረፉም ማለት አይደለም። በዚህች ሁለት ዓመት ውስጥ ብሔሮችን ሳይለይ በዜጎች ህይወትና ንብረት ላይ እጅግ አሳዛኝና አሳፈሪ ድርጊቶችን መፈጸማቸው እሙን ነው፡፡  ይህ ውጥንቅጥ ኃላፊነትን በብቃት፣ በቁርጠኝነትና ወቅቱን ጠብቆ ያለመወጣት ችግር ማመላከቻ ነው።    በእርግጥ እንደነዚህ ዓይነት ጥቂቶች የሚያቀናብሩት ድርጊት ቁጥሩ ከመቶ ሚሊዮን የዘለቀውን ኢትዮጵያዊ የሚወክል ድርጊት ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም፡፡
ከዚህ አኳያ በመንግስትና በሕግ አስከባሪ አካላት መጠነ ሰፊ ድክመት ቢታይም ከነድክመቱም ቢሆን የተፈጸመው ጸያፍ ድርጊት በስፋት ተናፍሶ ደም ሳያቃባና ደም ሳይለውስ መቀጨት መቻሉ የዚሁ በጎ ገጽታ መለኪያ ነው፡፡ ከዚህ አልፎ ተርፎም ተጎጅዎችን ለመታደገ ሕዝባችን በነቂስ ወጥቶ እርዳታ ያደረገውንና አጋርነቱን በጨዋነት፤ ነገር ግን በቁጣ የገለጸውን ሕዝብ ስንመለከት ግጭቶችን ለመፍታት ከውጭ ገላጋይ ሳንጋብዝ ችግሮችን እርስ በርሳችን መፍታታት መቻላችን እጅግ ኩራት እንዲሰማን የሚያደርገ ተግባር መሆኑ ማስተዋል ያሻል፡፡ ለመገዛት ሳይሆን ለመስተዳደር የተመቸ ሕዝብ አለን ለዚህ ደግሞ ባለስልጣኖቻችን ሕዝባችንን ለማስተዳደርና እንጂ ለመግዛት ወጥነው ባይንቀሳቀሱ በጎ ነው፡፡
እርግጥ ነው፤ ስጋቶቻችን ገና በቅጡ አልተቀረፉም፣ በእንጥልጥል ያሉ ደም ሊያቃቡንና ሊከፋፍሉን ያቆቦቆቡ፣ እያሴሩና እያደቡ ያሉ ሃይሎችና አስተሳሰቦች ከነድርጊቶቻቸው ገና አንዳልተገቱ ግልጽ ነው። ለዚህ ደግሞ መጠነ ሰፊ ትግል ይጠብቀናል፡፡ በየጊዚው በየክልሎች ውስጥ የሚከሰቱ ከፍተኛ መፈናቀል፣ ስደትና የሕይወት መጥፍትን ያስከተሉ ብልጭ ድርግም የሚሉ ግጭቶችና ወደ ከተሞች ያለማቋረጥ እየሰረጉ የጦር መሳርያዎች በገፍ ለማስገባት የሚደረጉ ሙከራዎች የስጋቶቻችን ምንጭና የቀጣይ ፈተናዎቻችን መገለጫዎች ናቸው፡፡
በጥቅሉ ደምረንና ቀንሰን ስናጤነው ተስፋ ሰጭ ነገሮች በብዙ መልኩ ስር ለመስደደ እየታገሉ ይገኛሉ፡፡ ተስፋ ሰጭ ነገሮች እንዲጎለብቱ ለማድረግ ደግሞ የሁላችንንም እገዛ ድጋፍ ይሻሉ፡፡ ኃላፊነት የተሰጣቸው ሹመኞች ደግሞ በተለይ የሕግና የሞራል ግዴታ አለባቸው፡፡ ይህ ማለት ግን ድጋፍ ወይም ተቃውሞን በማራመድ ብቻ  የተሻለ ቀን ይመጣል ማለት እንዳልሆነ በጋራ መረዳት አለብን፡፡ “ለውጡ” እንዳይቀለበስ በአንድ በኩል በንቃት እየተጠባበቅን በተቃራኒው ደግሞ “ለውጡ” በምንፈልገው መንገድ አንድነታችን እያጠናከረልን  ልዩነቶቻችን ደግሞ አንጥሮ በማውጣት በዲሞክራሲያዊ አግባብ እርስ በእርስ ያለርህራሄ በሃሳብ እያታገለን የሃሳብ የበላይነት ገዢ የሚሆንባት አገር መገንባት አለብን፡፡
ለዚህ ደግሞ እራሳችንን ከጥላቻና ከአሉባልታ አላቀን ማህበራዊ ትስስር መድረኮች ከሚረጩት  የጥላቻ ስብከት ርቀን ከተረት ተረትና ከአፈ ታሪክ ይልቅ ዛሬ ያለው እውነታ ላይ ተመርኩዘን ፈር የሳተው ፈር እንዲይዝ ከሃዲድ የወጣው ወደ ሃዲዲ እንዲመለስ ድክመቶች እንዲታረሙና እንዳይደገሙ፣ ጥፋተኞች በሕግና በሕግ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ እንዲዳኙ በመጨረሻም ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የተከበሩባት፣ ፍትሐዊ የሃብት ክፍፍል የተረጋገጠባት፣ ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ እኩልነት የሰፈነባት ሃገር ለመገንባት ሁላችንም እጅ ለእጅ ተሳስረን እድሉን በኃላፊነት መንፈስ  ለመጠቀም  ያላሰለሰ ጥረት ማድረግን አለብን፡፡

Read 1563 times
Administrator

Latest from Administrator