Saturday, 09 February 2019 12:10

ፌስቡክ 15ኛ አመቱን በስኬት አክብሯል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  የተጠቃሚዎቹ ቁጥር ከ2.32 ቢሊዮን በላይ ደርሷል ከ35 ሺህ በላይ ቋሚ ሰራተኞች አሉት

     እ.ኤ.አ በ2004 በሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ማደሪያ ክፍል ውስጥ በማርክ ዙከርበርግ የተጠነሰሰውና በተማሪዎች መካከል ትስስር ለመፍጠር ታስቦ እንደዋዛ የተጀመረው የአለማችን ቁጥር አንድ ማህበራዊ ድረ-ገጽ የሆነው ፌስቡክ የተመሰረተበትን 15ኛ አመት ባለፈው ሰኞ ያከበረ ሲሆን፣ የተጠቃሚዎቹ ቁጥር ከ2.32 ቢሊዮን በላይ መድረሱን አስታውቋል፡፡
በ2004 ላይ በሰባት ሰራተኞች ብቻ ስራ የጀመረውና በስኬት ጎዳና ተጉዞ ከአለማችን ቀዳሚ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች አንዱ ለመሆን የበቃው ፌስቡክ በአሁኑ ወቅት ከ35 ሺህ በላይ ቋሚ ሰራተኞች እንዳሉትም ኩባንያው አስታውቋል፡፡
በየቀኑ የሚጠቀሙት ደንበኞች ቁጥር 1.5 ቢሊዮን የደረሰለት ፌስቡክ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2018 ብቻ 55 ቢሊዮን ዶላር ገቢ እና 22 ቢሊዮን ዶላር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን የዘገበው ሲኤንኤን፣ ያም ሆኖ ስኬቱ በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ያለፈ እንደነበር አስታውሷል፡፡
የ34 አመቱ ማርክ ዙከርበርግ የሚመራው ፌስቡክ ዋትሳፕንና ኢንስታግራምን በድምሩ 20 ቢሊዮን ዶላር በመግዛት የራሱ ካደረገ በኋላ የተጠቃሚዎቹ ቁጥር በተለየ ሁኔታ እንደጨመረም አመልክቷል፡፡
የሁለት ልጆች አባትና የሆነውና 119 ሚሊዮን የፌስቡክ ተከታዮች ያሉት የኩባንያው መስራች ማርክ ዙከርበርግ ከአለማችን ስመጥር ቢሊየነሮች አንዱ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ አጠቃላይ የተጣራ ሃብቱ 62.4 ቢሊዮን ዶላር መድረሱንም ገልጧል፡፡

Read 1281 times