Sunday, 03 February 2019 00:00

ሶማሊያ በሙስና ከአለም ቀዳሚዋ ሆናለች

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

ትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው አለማቀፍ ተቋም ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የ2018 የዓለም አገራት የሙስና ሁኔታ አመላካች ሪፖርት፤ ሶማሊያ በአመቱ እጅግ የከፋው ሙስና የተፈጸመባት አገር መሆኗን ያስታወቀ ሲሆን ኢትዮጵያ በሙስና ከ180 የአለማችን አገራት 140ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
በ180 የአለማችን አገራትና አካባቢዎች ላይ የሰራውን ጥናት መሰረት አድርጎ ተቋሙ ባለፈው ማክሰኞ ይፋ ባደረገው አለማቀፍ የሙስና ሪፖርት እንዳለው፤ ከሶማሊያ በመቀጠል የከፋ ሙስና የተፈጸመባት የአለማችን አገር ሶርያ ስትሆን ደቡብ ሱዳን በሶስተኛ ደረጃ ትከተላለች፡፡
በአመቱ ከአለማችን አገራት መካከል እጅግ አነስተኛው ሙስና የተፈጸመባት አገር ዴንማርክ ስትሆን፣ ፊንላንድ፣ ሲንጋፖር፣ ስዊድንና ስዊዘርላንድ በቅደም ተከተላቸው መሰረት በአነስተኛ የሙስና መጠን እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በአብዛኞቹ የአለማችን አገራት ሙስናን በመዋጋት ረገድ ውጤታማ አለመሆናቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ባለፉት ሰባት አመታት ሙስናን ለመቆጣጠር ባከናወኗቸው ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ የቻሉት የአለማችን አገራት 20 ብቻ መሆናቸውንና ከእነዚህ አገራት መካከልም አርጀንቲናና አይቬሪኮስት እንደሚገኙበት አመልክቷል፡፡
በአለማችን እጅግ ሙሰኛ መንግስታት ያሉበት አካባቢ ከሰሃራ በታች ያሉት የአፍሪካ አገራት ናቸው ያለው ሪፖርቱ፤ የከፋ ሙስና ካለባቸው 10 አገራት መካከል አምስቱ ከሰሃራ በታች የሚገኙ መሆናቸውንና በእነዚህ አገራት ሙስናን ለመዋጋት የሚደረገው ጥረትም ትርጉም ያለው ውጤት ሊያስመዘግብ አለመቻሉን ይገልጻል፡፡
ሲሼልስ፣ ቦትሱዋና፣ ኬፕ ቨርዴ፣ ሩዋንዳና ናሚቢያ እንደ ቅደም ተከተላቸው በአፍሪካ አህጉር አነስተኛ ሙስና የተፈጸመባቸው ቀዳሚዎቹ አምስት አገራት መሆናቸው ተነግሯል፡፡

Read 2498 times