Saturday, 02 February 2019 14:41

ዜና ዕረፍት የአፈ - ጉባዔ ዳዊት ዮሐንስና የሻምበል ለገሠ አስፋው የቀብር ሥነሥርዓት ተፈፀመ

Written by 
Rate this item
(0 votes)


    በ1987 የኢፌዴሪ ህገመንግስት ሲረቀቅ ወሳኝ ሚና የነበራቸው የመጀመሪያው የኢህአዴግ ዘመን መንግስት አፈጉባኤ ዳዊት ዮሐንስ የቀብር ስነሥርዓት ዛሬ ይፈፀማል፡፡
ሃገራቸውን በአፈ ጉባኤነትና አምባሳደርነት ያገለገሉት ዳዊት ዮሐንስ፤ የኢትዮጵያ የሽግግር መንግስት ሐምሌ 17 ቀን 1983 ዓ.ም ሲመሠረት በህግ ቋሚ ኮሚቴና በህገ መንግስት አርቃቂ ኮሚሽን ፀሐፊ ሆነው አገልግለዋል፡፡ ከ1987 እስከ 1998 ድረስም በሁለት ዙር የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አፈጉባኤ በመሆን ለአስር አመታት በም/ቤቱ ቆይተዋል፡፡ አምባሳደር ዳዊት ዮሐንስ የቀድሞ ብአዴን የማዕከላዊ ኮሚቴና አስፈፃሚ አባል በመሆንም ሀገሪቱን በከፍተኛ የስልጣን እርከን ከመሩ ባለስልጣናት መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡
በአዲስ አበባ የተወለዱት አምባሳደር ዳዊት ዮሐንስ፤ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጀመሪያ ድግሪያቸውን እንዲሁም ሁለተኛ ድግሪያቸውን ከአምስተርዳም ዩኒቨርስቲ በህግ አግኝተዋል፡፡  በ63 አመታቸው ከዚህ አለም በሞት የተለዩት አምባሳደር ዳዊት ዮሐንስ፤ ባለትዳርና የሶስት ልጆች አባት የነበሩ በህክምና ሲረዱ በቆዩበት አሜሪካን ሀገር ህይወታቸው ማለፉ ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል የደርግ ከፍተኛ ባለስልጣን የነበሩት ሻምበል ለገሠ አስፋው የቀብር ስነሥርዓት በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡
በ76 አመታቸው ከዚህ አለም በሞት የተለዩት ሻምበል ለገሠ አስፋው፤ በአለም ገና መስከረም 21 ቀን 1935 የተወለዱ ሲሆን፤ ሀገራቸውን በውትድርና በመንግስት አመራር አገልግለዋል፡፡ ሻምበል ለገሠ አስፋው የ4 ሴት ልጆችና የአንድ ወንድ ልጅ አባት ሲሆኑ አራት የልጅ ልጆችን አይተዋል፡፡

Read 1403 times