Sunday, 06 January 2019 00:00

“የኔ የምለው ሰው”

Written by  ከቃል ኪዳን
Rate this item
(11 votes)

 ምን እንደጎደለኝ እያሰብኩ ነው፡፡ የቤቴ አስቤዛ ስላለቀ ድርጊቴ፤ ማጀቱ በጎደለ ቤት ውስጥ ቁጭ ብሎ ስለጎደለ ነገር ማሰብ ይመስላል፡፡ ግን ውጪ እየበላሁ ነው፡፡ ሆዴ ከሞላ ደግሞ የማጀቴ ጉድለት፤ ጉድለቴ ሊሆን አይችልም፡፡
ግና እደጅ አንድ ምግብ የምበላበት ገንዘብ የሁለት፣ የሦስት ቀን አስቤዛዬን እንደሚችል እያወቅሁ ለምን አስቤዛ ለማድረግ ሰነፍኩ? ለምን ማብሰል አስጠላኝ? ከቀናት በፊት ከጫማዬ እኩል ንጹሕ እንዲሆኑ የምፈልጋቸው ማብሰያ ድስቶቼ፤ ቀለሙ የረገፈ ኮርኒስ መስለው እያየሁ እንዴት ጨከንኩ? እንዲህ እንድሆን ያደረገኝ ይሄ ጉድለቴ ይሆን እንዴ?
‹‹የሆነ ጉድለት ይሰማኛል፡፡ ምን እንደጎደለኝ ባስብም፤ ጎዶሎ እውቀቴ ትክክለኛ ጉድለቴን ሊገልጥልኝ አልቻለም፡፡ ምን የጎደለኝ ይመስልሀል?›› አልኩት እንደ መርዶ ነጋሪ፣ በጠዋት እቤቴ መጥቶ የነበረውን ጎዶሎ ጓደኛዬን፡፡
ቁመቴ አጭር ነው፡፡ ነገር ግን ከዚህ ጎዶሎ ጓደኛዬ፣ በታኮ ጫማ ከፍታ ልክ እረዝማለሁ፡፡ ይሄን ያህል መበላለጥ ይዘን ሁለታችንም አጭር ተብለን ልንጠራ አይገባም፡፡ ለዛም ይመስለኛል ጫማዎች ታኮና ‹ፍላት› ከሚል ተቀጥላ ጋር የሚጠሩት፡፡ የታኮ አናሽ ‹ፍላት› ከተባለ፤ የአጭር አናሽ ደግሞ ጎዶሎ መባል አለበት፡፡
‹‹ቆይ አንተ እራስህን ብታገኘው ትወደዋለህ? ማለቴ እራስህን ጓደኛ ለማድረግ ትፈቅዳለህ?›› በሀሳብ ነጉዶ ሄዶ የነበረው ጎዶሎው ጓደኛዬ ከሀሳቡ ሲመለስ፣ ጥያቄዬን በጥያቄ መለሰልኝ፡፡
‹‹መልስልኝ እንጂ?›› አፋጠጠኝ፡፡
መልሴን ለመስማት ከመቸኮሉ የተነሳ በእጁ የያዘውን መጽሐፍ ሁለቴ ተር፣ ተር አድርጎ ከደነው። የመጽሐፉ ትልቅነት ከጎዶሎ ቁመቱ ጋር አልሄድ አለኝ፡፡ ለጎዶሎዎች የሚሆን ጎዶሎ መጽሐፍ ለምን አይዘጋጅላቸውም? ከአንገት የምትንጠለጠል የቡዳ መድኃኒት የምታክል!፡፡
‹‹አንተ ብትሆን ምን ታደርግ ነበር?›› ስል መልሼ ጠየቅሁት - ከበደኛ!
የከበደኝ ጥያቄው ይሁን መልሱ አልገባኝም። ጎዶሎ ጥያቄ መሆን አለበት፡፡ ጎዶሎው ጓደኛዬ በምላሼ ተናዶ፤ ልክ በእጁ እንደያዘው መጽሐፍ፤ መዝጊያዬን ሁለት ጊዜ ተር፣ ተር አድርጎ ሲያበቃ ወርውሮ ዘግቶት ሄደ፡፡
ቆይ ምን እንድመልስለት ነበር የጠበቀው? ‹አንተ ታኮቢሱን ጎዶሎ፣ ጓደኛዬ ያደረግኩ፣ እራሴን እንዴት ጓደኛ ማድረግ ያቅተኛል?› እንድለዉ ነው? ደግሞ እሱ ጥያቄዬን በጥያቄ ከመለሰ፤ እኔስ የሱን ጎዶሎ ጥያቄ ይዤ ለምን ልጨነቅ? እሱ ለእኔ ጥያቄ፤ ታኮ ሆኖ፤ ከፍ አድርጎ ከእኔ እኩል ያደርገው ዘንድ ሌላ ጥያቄ ከሰጠኝ፤ እኔ ለእሱ ጥያቄ፣ ታኮዬን ሰብሮ፣ ዝቅ አድርጎ፣ ከእሱ እኩል ያደርገኝ ዘንድ ለጥያቄው፤ ሌላ ጥያቄ ብመልስ ለምን ሊቀበለኝ አልወደደም? ወይስ ለአንድ መንገድ በደርሶ መልስ የተለያየ ክፍያ እንደሚጠይቁ ታክሲዎች፤ ከጎዶሎ ወደ አጭርና ከአጭር ወደ ጎዶሎ የሚወረወሩ ጥያቄ-መልሶች መመሳሰል የለባቸውም?
ሁሉም የራሱን ጥያቄ ተሸክሞ የሚዞር ከሆነ፣ ሰው ለራሱ ጥያቄ እራሱ መልስ መፈለግ ሳይኖርበት አይቀርም፡፡ እኔም ያለ ማንም እርዳታ ጥያቄዬን ለመመለስ በሀሳብ ላይ፣ ታች አልኩ፡፡ መልስ ግን የለም። ምናልባት የማጀቴ መሙላት ጉድለቴን ከሞላው ብዬ አስቤዛ ልገዛ ወጣሁኝ፡፡ ቀድሜ ግን ድስቶቼንና መመገቢያዎቼን አጣጠብኩ፡፡
ባለመደብሩ ጠፍቼ በመምጣቴም ሆነ ሁለት መቶ ብር የሚያወጣ አስቤዛ በአንድ ጊዜ በመግዛቴ ምንም አዲስ ነገር የተሰማው አልመሰለኝም፡፡ የእኔ መጥፋትም ሆነ አለመጥፋት ጉድለቱን አይሞላውም ማለት ነዉ? ወይስ እሱ ጉድለት የለውም?
ቤቴ ስመለስ የገዛሁትን አስቤዛ በቀላሉ ይታየኝ ዘንድ ግልጽ ቦታ ላይ አስቀመጥኩ፡፡ በርግጥ አሎሎ ለሚያካክሉ ዓይኖቼ፤ የጠባቧ ቤቴ ሁሉም ጥጎች ግልጽ ቦታዎች ናቸው፡፡ ሁለት መቶ ብሬን በአስቤዛ መልክ ከጠረጴዛዬ ላይ ደርድሬ፤ በትላልቅ ዓይኖቼ አፍጥጬ ለግማሽ ሰዓት ያህል ተመለከትኩት፡፡ ምንም አዲስ  ነገር የለም፡፡
የማጀቴ መሙላቱ እኔን አልሞላ ቢለኝ፤ ምናልባት ማጀቴ መሙላት ያለብትን ያህል አልሞላ ይሆን ብዬ እንደገና ወደ መደብር ተመልሼ በተረፈችኝ መቶ ብር ሌላ አስቤዛ ጨመርኩበት፡፡ ባለመደብሩ አንድ ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሁለት ጊዜ ተመላልሼ አንድ ዓይነት ነገር ብገዛውም፤ አሁንም መጉደልም ሆነ መሙላት አይታይበትም፡፡ ይሄ ሽንቁር! ቢያንስ በሆዱ ‹ቅድም የገዛኸው አስቤዛ አልበቅቶህ ነው?› ብሎ አይገላምጠኝም? የባለመደብሩ ንቀት እያናደደኝ፣ ወደ ቤቴ ተመልሼ አዲሱን አስቤዛ ከቀድሞው አስቤዛ ጎን አኖርኩና፣ ወደ ኋላ አፈግፍጌ አፈጠጥኩባቸው - ምንም ለውጥ የለም፡፡ ቦታ እየቀያየርኩ ብሞክርም፤ ምንም መሙላት ሊሰማኝ አልቻለም፡፡
‹‹ውበት በአፍ ይገባል!›› ሲል ራዲዮኔ ለፈፈ፡፡
‹‹ሙላትስ?›› ስል ጠየቅሁት፡፡
ያልጠየቅሁትን፤ ቀድሞ የጀመረውን መዘባረቅ ያዘ፡፡ ራዲዮኑን ከወራት በፊት አውጥቼ ሰብሬው በቅርብ ነው ያሠራሁት፡፡ ተቀይሞኝ ይሆን የጠየቅሁትን የማይመልሰው? ወይስ ከሥብራቱ በኋላ ያልተጠየቀውን የሚያዘባርቀው የራሱ ጉድለት አመጣ?
‹ሙላት› በአፍ መግባቱን ለምን እራሴ አላረጋግጥም በሚል ተነሳሁና ቶሎ ለማረጋገጥ፤ ቶሎ ይደርሳሉ ያልኳቸውን ምግቦች ማበሳሰል ጀመርኩ። ሁለቱንም የምድጃዬን ላንቃዎች ከፍቼ አንዱ ላይ ከኩባያ የምትተልቅ ትንሽዬ ድስት፤ በሌላው መጥበሻ ጣድኩ፡፡ አንድ አይነት ምግብ መብላት አልወድም፡፡
አስቤዛው አዲስ ነገር ካመጣ በሚል ጎንበስ ቀና እያልኩ እያየሁት፤ ምግቦቹን አብስዬ ጨረስኩ፡፡ በድስት የጣድኩት ምግብ ሲበስል፤ ሚስቴ ረስታዉ በሄደችው ሻሽ ይዤ ካወረድኩት በኋላ ክዳኑን ከፍቼ፣ እንደ ቡና ጭስ፤ እያዟዟርኩ በእንፋሎቱ ቤቴን አጠንኩት፡፡ ያበሰልኩትን አቀራርቤ አስቤዛው ላይ እንዳፈጠጥኩ፣ የምቆርሰዉን እንኳን ሳላይ ምሳዬን በላሁ፡፡ ከሆዴ በቀር ሌላ የሞላ የለም፡፡ ከላዩ ላይ ተቀንሶ የተሠራለት ጎዶሎ አስቤዛ ላይ አፍጥጦ ሙላትን መፈለግ ከባድ ነው፡፡
እጄን ታጥቤ፤ ሚስቴ ረስታው በሄደችው መከረኛ ሻሽ አደራረቅሁ፡፡ ሻሹን አንድ ቀን እራሴን አሞኝ አናቴ ላይ ከማሰሬ ውጪ፤ ይኸው ድስት ሳወርድበት፤ ምድጃ ስጠራርግበትና የረጠበን ሳደርቅበት ይኖራል፡፡ ለእሷ ይሄ ሲያንሳት ነው እንደውም፡፡ ንዝንዟን ሳስታውስ እንደውም እሳት ውስጥ ጨምሬው ላንጨረጭረው ይቃጣኛል፡፡
አሁንም አለች ወይስ የለችም ለማለት ያህል፤ የሚስቴ አሻራ የቀረበትን የመጨረሻ ሻሽ አንስቼ አፍንጫዬ ላይ አኖርኩት፡፡ የሻሹ አካል እሷን፣ እሷን፤ ድስት፣ ድስት፤ ምድጃ፣ ምድጃ፤ ጣት፣ ጣት ይላል፡፡ ይሄ ሻሽ የነካውን ነገር ሁሉ ጠረኑን አትሞ ያስቀራል እንዴ? ከአፍንጫ ውጪ ሌላ ማሽተት የሚችል አካል ቢኖሮ ኖሮ ደግሞ አሁን ላይ የኔን አፍንጫ፣ የኔን አፍንጫ ማለቱ አይቀርም ነበር ማለት ነው፡፡
ሻሹን ከአፍንጫዬ ላይ አንስቼ ትኩር ብዬ አየሁት። ቆይ ሁሉን የሚያትም ከሆነ፣ እንዴት የሚስቴን ንዝንዝ ሳያትም ቀረ? ካልነካ በስተቀር ባየ፣ በሰማ አያትምም ማለት ነው? እሷስ ንዝንዟን ካልቀዳችበት እንዴት እረስታው ሄደች? ወይስ ሌላ ምን ድግምት አስደግማበት ነው? እሷን የጎዳሁ መስሎኝ የጋለውን ድስት በሻሿ ይዤ ካወረድኩ በኋላ ይሆን እንዴ ማብሰል ያስጠላኝ? እንደዛ በፍጹም ሊሆን አይችልም። አድብቼ፣ በድንገት እኮ ነው ወደ እናቷ የሰደድኳት፡፡
ሚስቴን ጠልቼ ብፈታትም፤ አፍቅሬ ነበር ያገባዋት፡፡ ‹ሰውነቷ› የሚለው የሙሉቀን መለሰ ዘፈን ለእሷ የተዘፈነ ነበር የሚመስለኝ፡፡ አንዳንዴ ሙሉቀን በአካል የሚያውቃት ስለሚመስለኝና ስለምቀና ሙዚቃው ሲመጣ እዘጋዋለሁ፡፡ ከሁለት ዓመት በኋላ ሚስቴ ሰውነቷ ሳያንሳት፤ ሳታገባ ሠላሳ እንዳለፋት ሴት ንዝንዟ ባሰ፡፡ ሚስቴ መነዛነዝ ከመጀመርዋ ከወራት በፊት፤ አንድ ጠዋት አባቴ መጥቶ፤
‹‹ልጆቼ፤ ሁለት ዓመት ታለፋችሁ፣ ፍቅራችሁ እያለቀና እየተሰለቻቻችሁ ስለምትመጡ ውለዱ፡፡›› ሲል መከረን፡፡ እኛ ግን ሀብት ንብረት ካላፈራን ብለን እንቆይ አለን፡፡ ሁለት ዓመት ሲያልፍ ሚስቴ ንዝንዝ ጀመረች፡፡ የሙሉቀን ‹ሰውነቷ› እንኳን በሆነ አስማት ተገልብጦ፤ ‹ንዝንዟ› እያለ ይሰማኝ ጀመር። አንድ ቀን ዘፈኑ ሲመጣ ሬዲዮኑን ሰብሬ እሷንም፤
‹‹በቃኝ ሂጂልኝ!›› አልኳት፡፡
‹‹ከሠፈሬ የት ልሂድልህ? ደግሞ ይሄን ቤት፣ ቤቴ ነው ብለህ ውጪ ልትል ነው እንዴ? አባትህ የሰው መተላለፍያ የነበረውን መንገድ አጥረው፣ ቤቱን እንደሠሩት የማላውቅ መሰለህ? እኛ ህጻን እያለን ወደ ትምህርት ቤት የምንሄድበትን መተላለፍያ እኮ ነው አጥረው ቤት ያደረጉት፡፡›› አለችኝ፡፡
ከዓመታት በፊት ጎዶሎው ጓደኛዬ፣ ነዝናዛዋን ሚስቴን ላገባት መወሰኔን ስነግረው፣ ሰፈር ውስጥ መርመጥመጥ እንደማይበጀኝና ገመናዬን ከምታውቅ ሴት ጋር ትዳር መመስረት እንደሌለብኝ ተቆጥቶ ነግሮኝ ነበር፡፡ ይኸው ያለው ደረሰ፡፡ ሚስቴ በተጣላን በሠልስቱ ነጠላዋን አንጋዳ ለብሳ ቀበሌ ስትሄድ አየኋት። እንዳትከሰኝ አልደበደብኳት፤ ፍቺ እንዳትል በህግ አላገባዋት ብዬ ችላ አልኳት፡፡ እሷ ግን የቀበሌ ደንብ ማስከበር ይዛ መጥታ፣ “አባቱ መንገዱን አጥረው እኛ በየት በኩል እንለፍ!” ብላ ቀኑን ሙሉ ስትረብሽ ዋለች፡፡
ሚስቴ እንዲህ ባደረገች በነጋታው፣ ጎዶሎው ጓደኛዬ፣ የጎደለ የላስቲክ ውሃ ይዞ ቤቴ መጣ፡፡ ያለው በመድረሱ ትንንሽ ዓይኖቹን፣ በትልልቅ ዓይኖቼ ማየት ፈራሁ፡፡ ፈራ ተባ እያልኩኝ፤
‹‹ትዝ ይልሃል ሚስት ፍለጋ ሰፈር ውስጥ አትርመጥመጥ ያለከኝ?›› አልኩት፡፡
 ዝም አለኝ፡፡
‹‹የዛኔ ‹እንዴት ከሠፈርህ ልጅ ጋር ትርመጠመጣለህ?› ስትለኝ ውጤቱ ባይታየኝ፤ በልቤ ‹ይሄ ጫኝና አውራጅ! ሰፈር ውስጥ አዲስ ተከራይ በመጣ ቁጥር፣ ከጓደኞቹ ጋር ከሰፈራችን የመጣን ጭነት፣ ከእኛ ውጪ ማንም አያወርድም እያለ እየተጣላ፣ እኔ የሰፈሬን ቆንጆ ለሌላ አሳልፌ እንድሰጥ ነው እንዴ የሚፈልገው?› ብዬ ረግሜህ ነበር፡፡›› ጓደኛዬ በቁጣ ተመለከተኝ፡፡
‹‹አንተ ግን የሆዴን እርግማን ሳታይ ‹ከአብሮ አደግህ አትሰደድ ሲባል አልሰማህም? ትዳር ከላጤነት ስደት ነው፡፡ ትዳራዊ ስደትህን ከአብሮ አደግህ ጋር ካደረግህ ነገ ቀን ሲጎድል፤ በቀይ ሽብር እንደተከሰሱት ገመናህን አጋልጣ ትሰጥሀለች አልከኝ፡፡› እኔ ግን ተገብዤ እንደገና በሆዴ ‹ቆይ ይሄ ጎዶሎ ምን አባቱ ነው የሚለኝ?› ብዬ ሰደብኩህ።›› ጎዶሎው ጓደኛዬ ፊቱ፣ ለግዙፍ ሰው የሚበቃን መቅላት፣ በንዴት ቀላ። ደግነቱ የፈለገ ቢናደድብኝ፣ ቤቱ ገብቶ የዕለት ውሎ መመዝገቢያው ላይ ንዴቱን ከማስፈር በዘለለ ምንም ሊያደርግ አይችልም፡፡
‹‹ምኗን አይተህ ነው? የድሮውን እንዴት እረሳኸው?” አልከኝ፡፡ ‹‹ሰውነቷ!›› አልኩ፡፡ “ይሁና” ብለህ እዝን ብለህ ወጣህ፡፡ ዛሬ ሲደርስብኝ ግን ይኸው እውነቱን ፊቴ ቆሞ አየሁት፡፡
‹‹አዎ እኔም ዛሬ እውነቱ ተገለጠልኝ፡፡ እኔም አመጣጤ ለሱው ነበር፡፡›› አለኝ ጎዶሎው፡፡
‹‹ማለት?›› ምን ሊለኝ ነው በሚል መገረም ውስጥ ሰጥሜ ጠየቅሁት፡፡
ከብዙ ፈራ ተባ ማለት በኋላ፣ የሠፈራችንን አንዲት ጎዶሎ ሊያገባ፣ በርበሬ ማስቀንጠስ መጀመሩን ነገረኝ፡፡
‹‹የጫኝና አውራጅ አመልህ አለቅ ብሎህ ነው ወይስ ምን ተገኘ?›› አልኩት በንዴት፡፡
‹‹ሰውነቷ!›› አለኝ፡፡ አሽሙር መሆኑ ነው፡፡
‹‹እሺ አንተም ጎዶሎ፣ እሷም ጎዶሎ - ጎዶሎ ልትወልዱ?›› አሽሙሩን፣ በአሽሙር ለመመለስ እየሞከርኩ፡፡
‹‹ሳንወልድ ብንፋታስ?›› አለኝ፡፡ ሌላ አሽሙር!
 አጭር ሰው ተንኮለኛ ከተባለ፣ ጎዶሎ ምን ሊባል ይሆን? የራሱ ጉዳይ! እንደኔ ቀምሶ ይየው ብዬ ተውኩት፡፡
ሚስቴን ያበረርኳት ጊዜ ዕቃዋን እየሸከፈች፣ ለወራት የሚበቃ ንዝንዝ አሻረችኝ፡፡ ወጉ አይቅርብኝ ብላ እንጂ ሶስት አራት ቤት አልፋ እናቷ ቤት ለመግባት ዕቃ መሸከፍ አያስፈልጋትም ነበር፡፡ ዕቃዎቿን ሸክፋ ስትጨርስ፣ ዓይኖቿ ሟሙተው የሚፈሱ እስኪመስሉኝ አለቀሰች፡፡ አልቅሳ ስታበቃ አልጋችንን ከሸፈነው መጋረጃችን ውጪ ያለው የቤቱ ክፍል እንኳን የማያቃቸውን ገበናዎቼን እያነሳች ሞለጨቺኝና ወጥታ ሄደች፡፡
በመሄዷ ቀለለኝ፡፡ እቤት አለመኖሯን ሳስብ፣ ዓመቱን ሙሉ ለዩኒቨርስቲ መግቢያ ፈተና ሲዘጋጅ ከርሞ ፈተናውን እንደጨረሰ ተማሪ ተደሰትኩ። ደስታዬ ግን እንደጠበቅሁት ፍጹም አልነበረም፡፡ ፈተናውን መጨረሱ በራሱ እረፍት አይደለም ለካ? ከሌላኛው ቀን በኋላ ውጤቱ ያሳስባል፡፡ እንደውም ፈተናውን ከመጨረሱ፤ ውጤቱን ማወቁ ዘለግ ያለ ደስታ ሊሰጥ ይችላል፡፡
ሚስቴን ከአጠገቧ ተኝቼ፣ ስነቃ፣ ከእነ ንዝንዟ ተሰውራ እንዳገኛት የሚማለድ አዲስ ጸሎት በምሽቱ የሠርክ ጸሎቴ ላይ ጨምሬ ነበር፡፡ ብዙ ጊዜ የተዘጋ በሬን ከፍቼ ስገባ፣ በሩን እሷ ልትገባ ስትመጣ እንዲሰወራት፤ አስተዛዝኜ ነግሬው ነበር፡፡ ‹ቆይ የነዘነዘችህ ሌላ ሴት በር የለችም?› እያልኩ ቁስሉን ለመንካት እሞክራለሁ። ቁስል እንደሌለው ደረቱን ነፍቶ ዝም ይላል፡፡ ‹ታዲያ ቀለም ቀቢው ‹በስትኮ› ሊደፍነው ያልቻለው ቋርህ ከየት መጣ?› በሩ በዝምታው ይጸናል፡፡ ተናድጄ ወርውሬ እዘጋዋለሁ። ከበሩ በላይ ያለው ግድግዳ እየተፈረፈረ ወለሉ ላይ ይወርዳል፡፡ በሩ የዛኔ ‹አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል› ይልና በበርኛ ይሥቃል። አፈሩን ጠርጌ አውጥቼ ፊት ለፊቱ ቆሜ በንዴት አፈጥበታለሁ። ንዴቴን ሲያይ ይበልጥ ይንከተከታል። ወዲያው በሚያውቀው አንድ ቀልድ፤ እንደ ቅዱሳን ሥዕል፣ በነጭ መጋረጃ ወደተሸፈነው መስኮቱ ዞሮ፤
‹‹ኖክ! ኖክ! ኖክ!›› ይላል
‹‹ሁ ሂዝ ዜር?›› መስኮቱ ድምጹ ብቻ ነው የሚሰማው።
‹‹በሩን እጎዳለሁ ብዬ፤ ወርውሬ ዘግቼ፣ የግድግዳ ፍራሽ የተረፈኝ….›› በሩ በሣቅ እንደታጀበ ይጠይቃል። መስኮቴ ይሄኔ በሣቅ ይንክተከታል፡፡ ቆይ መልሱ ሣቅ ነው እንዴ?  በሩና መስኮቱ እስኪሰነጠቁ ወይ ስንጥቃቸው እስኪሰፋ አብረው ይስቃሉ፡፡ ሁለቱንም በተራ በተራ እመለከታቸዋለሁ፡፡ የበሩ ሣቅ ያስጠላኛል። መስኮቱ ድምጹ ብቻ ስለሚሰማ ያን ያህል የሚያናድድ አልነበረም።
አንድ ቀን እንደ ብርድ ልብስ የወፈረ መጋረጃ ገዝቼ በሩንም፤ እግረ መንገዴን የተፈረፈረው ግድግዳንም ሸፈንኩት፡፡ በሩ አኮረፈ፡፡ ወደ ጆሮው ጠጋ ብዬ፤
‹‹ይኸውልህ አደብ ካልገዛህ ገና ነቅዬ አውጥቼ እወረውርሃለሁ፡፡ በየመንገዱ የሚሸጡት ንቃይ በርና መስኮቶች ከየት የመጡ መሰለህ? እንዳንተ የሚያስቸግሩት ናቸው፡፡››
መስኮቱ ይሄን ሲሰማ ከመሸማቀቁ የተነሳ፤ የሆነ አካሉ ቋ ብሎ ሲሰበር ተሰማኝ፡፡ እሱም ላይ በዛቻ ጣቴን አወዛውዤበት ተቀመጥኩኝ፡፡
ጉድለቴ ምን እንደሆነ ማወቅ ብፈልግም፤ ‹ምንድን ነው ጉድለቴ?› ብዬ ከመጨነቄ ውጪ እራሴን ‹ምንድነው ግን ጉድለትህ?› ብዬ መጠየቅ እፈራለሁ። ምናልባት ውስጤ ከራሴ እንኳን ሸሽጌ የደበቅሁት ነገር ሳይኖር አይቀርም፡፡ ወይ ደግሞ ድንገት በሽታዬ መድኃኒት የሌለው እንዳይሆን እሰጋለሁ፡፡ መድኃኒት ከሌለው፣ በሽታውን ማወቁ በምን እንደሚሞቱ ከማወቅ በዘለለ ምንድን ነው ጥቅሙ? ችግሩ ለመሙላትም ሆነ እየጎደሉ ለማለቅ አንድ ሰው ጉድለቱን ማወቅ አለበት፡፡
ቆይ፣ ቆይ ሚስቴ መሄዷ ይሆን እንዴ ያጎደለኝ? እሱ ያጎድላል እንዴ? እሷ በመሄዷ ምንድን ነው የቀረብኝ? እንደውም ከንዝንዟ ተገላገልኩ እንጂ!  ግን ይሄን እንዴት ማረጋገጥ እችላለሁ? የማጀቴ ጉድለት ካጎደለኝ ብዬ ለማረጋገጥ አስቤዛዬን ከገዛሁ፤ እሷ እንዳጎደለች ለማወቅ እሷን ማናገር አለብኝ ማለት ነው፡፡
ወደ እሷ ጋር የምደውልበት ምክንያት ሳፈላልግ ጸሐይ አዘቀዘቀች፡፡ ዝም ብዬ ብደውልላት ናፍቅያት ሊመስላት ይችላል፡፡ ነይና ሻሽሽን ውሰጂ ልበላት እንዴ? ሻሿን እስካሁን ከእጄ ላይ እንደጠመጠምኩት ነው። ያለችውን ትበል ብዬ ደወልኩ፡፡ ወንድ ልጅ አነሳው። እየተንተባተብኩ እንዳለች ጠየቅሁት። ሳይንተባተብ እንደሌለችና ስትመጣ መልዕክት ሊነግርልኝ እንደሚችል ነገረኝ፡፡ እኔ ቅሌታሙና ወራዳው፣ መልሼ እንደምደውል ነግሬው፣ ስልኩን ዘጋሁት፡፡
ከተለያየን ስንት ጊዜ ሆኖ ነው፣ ስልኳን የምትሰጠው ፍቅረኛ ያበጀችው? እሷ እያለች ገዝቼው የነበረው አምስት ሊትር ዘይት እንኳን ገና አላለቀም። ደግሞ ድምጹን የማውቀዉ መሰለኝ። የሰፈራችንን ልጅ ፍቅረኛ አድርጋ፤ ተርመጥምጣ እንዳይሆን ብቻ። ለነገሩ እራሴ እስካባረርኳት ድረስ የፈለገችውን አማርጣ ጓደኛ ማድረግ ትችላለች። ሳበራት እስከሌላ ሠፈር ድረስ ማብረርና ከዛው ፍቅረኛ እንድትይዝ ማድረግ ነበረብኝ፡፡ ቆይ ከማን ጋር ሆና ነው? ውጪ እየበሉ ደጅ እያመሹ መምጣት ከመረጃ እንድርቅ አድርጎኛል፡፡ ጎዶሎው ጓደኛዬም አፍላ ፍቅር ላይ ሆኖ ለኔ የሚነግረው ቀርቶ እሱም የሚሰማው አጥቷል፡፡
ቆይ ማነው በእኔ እግር ለመተካት ሲያደባ የነበረው? ማነው እንደወረወርኳት የቀለባት? በርግጥ በዛ ሰውነቷ ይሰያት የነበረው ጎረምሳ ብዙ ነበር። ለነገሩ ማንም የራሱ ያድርጋት!፡፡ የሚገርመው የእሷ ባለመጠባበቂያ መሆን ነው። አዘናግቼ፣ ቀን ጠብቄ ነበር እኮ ያባረርኳት!  ሳትፈልግ፣ በእልህ ነው የገባችበት እንዳልል፣ እኔ እንዳውቅና እንድቀና ብላ እንኳን በበሬ ይዛው አልፋ አታውቅም፡፡ ንቃኝ ነው እንዳልል፣ ንዝንዟ የቅናት ውጤት ነበር፡፡ ወይ እሱ አፍሮ፤ የድብቅ ይሁን ብሎ አስማምቷት ይሆናል፡፡ ታዲያ ስልኳን ለምን አነሳው?
ስብሰከሰክ ቆየሁ፡፡ አውጥቼ ብጥላትም፤ እንዲህ በአንዴ አንስቶ ከጉያው የሚሽጣት ይኖራል ብዬ አልጠበቅሁም ነበር፡፡ ሰው እንዴት ሰው የጣለውን እያየ፤ ‹ለምን ጣላት?› የሚለውን እራሱን ሳይጠይቅ ያነሳል? ከበሮ በሰው እጅ ሲያዩት ያምር፤ ሲይዙት ያደናግር ሲባል ያልሰማ መሆን አለበት፡፡ ነገ ንዝንዟ አውጥቶ እንዲወረውራት ሲያደርገው፤ የኔ ችግር ምን እንደነበር ይገባዋል፡፡ ንዝንዟ ሲያነስረው፣ ያን የምወደውን ሰውነቷንና ‹ሰውነቷ› እያለ የሚያላዝነውን ሬዲዮን አውጥቼ ለምን እንደሠበርኩ ይገባዋል፡፡
አመሻሽ ላይ ደወለችልኝ፡፡ ቁጥሯ እንጂ ደዋይዋ እሷ ባትሆን ብዬ ማንሳቱን ፈርቼ ቆየሁ፡፡ ደግሞ ቁጥሯን ‹ላቭ› ብዬ ‹ሴቭ› እንዳደረግሁት ነው፡፡ እንዴት እስካሁን አላጠፋሁትም? እረስቻት ነው ወይስ እረፍት ላይ ስለነበርኩ? ወደ መዘጋቱ ሲደርስ እንደ ምንም ጉልበት አሰባስቤ ስልኩን አነሳሁት፡፡ ለምን አርፌ እንደማልቀመጥና እንደምጨቀጭቃት ጠየቀችኝ። ከዛ ፍቅር እንዳለብኝና ልረሳት እንዳልቻልኩ፣ በኔ ቦታ ሆና መለሰች፡፡ ካሁን በኋላ ብረሳት እንደሚሻላትና የራሴን ህይወት ብጀምር እንደሚበጀኝ መከረችኝ። በመጨረሻም ይሄን ቁጥር ለታናሽ ወንድሟ እንደሰጠችውና አዲስ ቁጥር እንደያዘች፤ ወንድሟን ከአሁን በኋላ እየደወልኩ እንዳላስቸግረው አስጠነቀቀችኝ፡፡
ቅድም ስደውል ያነሳው ታናሽ ወንድሟ እንደሆነ ድምጹ መጣልኝ፡፡ በንዝንዘ ምክንያት የፈታኋት ሚስቴ፤ ተንቀልቅዬ በመደወሌ ትነዘንዘኝ ጀመር። ለደቂቃዎች በጥሞና ስሰማት ከቆየሁ በኋላ፣ ቀን አስቤዛዎቹ ላይ እንዳደረግሁት፤ የምትለውን መስማት ትቼ ስልክ በያዘው ጆሮዬ አፍጥጬባት፣ ጉድለቴ እሷ እንደሆነች መመዘን ጀምርኩ፡፡ ለደቂቃዎች በጆሮዬ ባፈጥባትም ምንም የሞላ ነገር ሳጣ፤ ስልኩን ጆሮዋ ላይ ዘግቼ ተቀመጥኩ፡፡
ስልኩን ጆሮዋ ላይ ከዘጋሁ በኋላ በአስር ደቂቃ ውስጥ አስር ጊዜ ደጋግማ ደወለች፡፡ እንዳላየ ዝም አልኳት። የጽሑፍ መልዕክት ላከች፡፡ ሳላነብ አጠፋሁት። ሌላ የጽሑፍ መልዕክት ለመጻፍ በሹል ጥፍሯ የስልኳን ‹ስክሪን›፣ በእልህ ስትጠቀጥቀው ይሰማኛል፡፡ ጥፍሮቿ የሚነጥሩበት የእስክሪኑ ሜዳ የሚያወጣቸው የተለያዩ ድምጾች፣ እየጻፈች ያለችው ስድብና እርግማን እንደሆነ ነገረኝ፡፡ ስልኬን አጥፍቼ ትውት!
ይህቺን አለብላቢት ከሰውነቷ በተጨማሪ ምኗን ነበር የወደድኩት? ድጋሚ ሰውነቷን? ከእሱ በተጨማሪ አጠገቤ በመሆኗ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ከእሷ ጋር ማውራቱና መሣሣቁም ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ከእነ ባለቤትዎ ብለው በሚጠይቁ ግብዣዎች ላይ አብራኝ ስትገኝም ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ሲከፋኝና ስደሰት፣ ስሜቴን የምትጋራልኝ የኔ ሰው መሆኗን ሳስብም ደስ ይለኝ ነበር፡፡ ምናልባት በእሷ ደስተኛ የነበርኩ ባይሆንም፣ በነበረው የፍቅር ግንኙነት ደስተኛ ነበርኩ ማለት ነው። ያ ነው እንዴ የጎደለኝ? ይሄን ጥያቄ ስጠይቅ አንጀቴ መልሱን እንደደረስኩበት በመርገብገብ አሳወቀኝ፡፡ በዚያች ቅጽበት ትንሽ ቀለል ሲለኝ ተሰማኝ፡፡ አዎ እሷ ሳትሆን “የኔ የምለው ሰው” ነው የጎደለኝ - ዩሬካ!
ድንገት የቤቴ መዝጊያ በኃይል ተንኳኳ፡፡ መዝጊያዬ ያወጣው ድምጽ ቅድም የፈታኋት ሚስቴ፣ ጥፍሮቿ የሞባይሏን ስክሪን ሲቀጠቅጡ፣ ስክሪኑ ካወጣቸው ድምጾች ጋር ተመሳሳይነት ነበረው። ቀጭንና ወፍራም ቢሆኑም ቅሉ፡፡ እንደገና በኃይል በሬን አንገጫገጨችው። ሲያሾፍብኝ የነበረው በር እንዲህ በመደብደቡ ደስ ቢለኝም፣ ከዛሬ ምሽት ጀምሮ ለሳምንት ያህል የሰፈሩ የቡና ወሬ ማዳመቅያ እንደምሆን አልጠፋኝም፡፡

Read 2998 times