በኢትዮጵያ የቱሪዝም ገበያ ልማት መለዮ ላይ ያተኮረ ኢትዮጵያን በፎቶ የማስተዋወቅ ውድድር ባለፈው ሳምንት የተጀመረ ሲሆን ውድድሩ ኦክቶበር 31 2018 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ ታውቋል፡፡
ተወዳዳሪ የፎቶግራፍ ባለሙያዎች፤ የሀገሪቱን የቱሪዝም ሀብቶች በፎቶ በማቅረብ ውበታቸውን አጉልቶ ማሳየት የሚጠበቅባቸው ሲሆን አላማውም የቱሪዝም መለዮ አርማውን በያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ልብ ውስጥ እንዲሰርፅ በማድረግ፣ የኢትዮጵያ የቱሪዝም መስህቦች አምባሳደር ማድረግ ነው ተብሏል። “Land of origins” ወይም በአማርኛው “ምድረ ቀደምት” በመባል የሚታወቀውን የቱሪዝም መለዮ የማስተዋወቅ ዘመቻ ባለፈው ሳምንት መጀመሩን የጠቆመው የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት፤ የዘመቻው አንዱ አካልም ኢትዮጵያን ምድረ ቀደምት ያሰኟትን በርካታ የተፈጥሮ፣ የባህልና የታሪክ ቅርሶች በተለያዩ አጋጣሚና ጊዜያት በተነሱ ፎቶዎች መግለፅ እንደሆነ አመልክቷል፡፡
የፎቶግራፍ ባለሙያዎች ለውድድር የሚያቀርቧቸው ምስሎች በተለያዩ ባለሙያዎች ተገምግመው በደረጃ የሚለዩ ሲሆን በውድድሩ ላሸነፉ ሶስት ተወዳዳሪዎችም ጠቀም ያሉ ሽልማቶች መዘጋጀታቸውን ድርጅቱ አስታውቋል፡፡
በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ ፍላጎት ያላቸው የፎቶግራፍ ባለሙያዎች፣ የኢትዮጵያን ምድረ ቀደምትነት ከሁሉ በበለጠ ይገልፅልናል የሚሏቸውን የፎቶ ምስሎች አዘጋጅተው photocompetition@ethiopia.travel ላይ ማቅረብ እንደሚችሉ የተገለጸ ሲሆን የፎቶው ይዘት ምን መምሰል እንዳለበትና ለውድድር የሚቀርቡት ፎቶዎች መጠን ምን ያህል እንደሆነ በድርጅቱ ድረ ገፅ www.ethiopia.travel ላይ ማግኘት እንደሚቻል ተጠቁሟል፡፡
Published in
ንግድና ኢኮኖሚ