Saturday, 13 October 2018 10:56

የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን ዛሬ ይዘጋል

Written by 
Rate this item
(0 votes)

 በክብር እንግድነት በተገኙት በምክትል ጠ/ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን መስከረም 30 ቀን 2011 በሚሊኒየም አዳራሽ በድምቀት የተከፈተው 9ኛው አዲስ ቢውልድ ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን ዛሬ ይዘጋል፡፡
በየትኛውም የአገር ዕድገት ኢኮኖሚ ላይ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ በጣም ከፍተኛ ነው ያሉት ም/ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሀገራችንን ለማዘመን ቁልፍ ከሆኑ ዘርፎች ከፍተኛ ካፒታል የሚጠይቅ፣ ከፍተኛ የሥራ ዕድል የሚፈጠርበትና ለሌሎች የልማት ፕሮግራሞች ስኬት መሰረት የሚሆነው ይኼው ዘርፍ ነው ሲሉ ገልፀዋል፡፡ ዘርፉ፤ በርካታ የሆኑ ገንቢዎች፣ አልሚዎች፣ የግንባታ ግብአት አቅራቢዎች፣ የሥራ ተቋራጮችና ሌሎችም የሚሳተፉበት ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ማዕከል እንደሆነ የጠቀሱት አቶ ደመቀ፤ ዘርፉን ለማዘመን በአገራዊ አቅም ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ማድረግ እጅግ በጣም ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡
ይህ ኤግዚቢሽን ለመንግሥት ከፍተኛ ተስፋ የሚያጭርና ተገቢ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው፣ በኮንስትራክሽን ግብአቶች አቅራቢዎችና አገልግሎት ሰጪዎች ላይ ያተኮረ መሆኑ ነው ያሉት ም/ጠ ሚኒስትሩ፣ የልምድ ልውውጥ መድረኮችን በማመቻቸት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ፣ የአገር ውስጥ የኮንስትራክሽን ግብአቶች፣ አምራቾችና የአገልግሎት ሰጪዎችን የበለጠ እንዲጠናከሩ ማድረግ ያስፈልጋል ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡
የቴክኖሎጂ ሽግግር የተሟላና ሙሉ የሚሆነው፣ ፋና ወጊዎችን በማበረታታት፣ ደረጃ በደረጃ በዓለም ላይ ተወዳዳሪ ማድረግ ሲቻል ነው፡፡ የአገር ውስጥ ግብአት አምራቾችና አቅራቢዎችን በጠንካራ የገበያ ትስስር፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በኢንጂነሪንግ ፋብሪኬሽን አቅምን በመገንባት፣ ከልዩ ልዩ ከፍተኛ የትምህርት፣ የቴክኒክና የሙያ፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ተቋማት ጋር በማገናኘት መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
መንግሥት የዜጎችን ፍላጎት በማስቀደም፣ ለወጣቱና ለመጪው ትውልድ የምትመች ኢትዮጵያን ገንብቶ ለማስረከብ፣ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ቀርፆ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ይገኛል ያሉት የኮንስትራክሽን ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፤ የኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ኢንዱስትሪውን ተወዳዳሪና ትርፋማ በማድረግ ሂደት ውስጥ የተደራጁ የሙያ ማኅበራትን በማበረታታት፣ የሙያ ሥነ ምግባርን በማስረፅ፣ መልካም ተሞክሮዎችን በማስፋት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር ለማሳለጥ፣ የግሉን ዘርፍ ጤናማ ፉክክር ለማዳበር ጥረት እያደረገ ነው ሲሉ ገልፀዋል፡፡
ከ80 በላይ በኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪዎች፣ የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂዎች አቅርቦት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ አምራቾች አቅራቢዎችና አልሚዎች የሚገኙበት ይህ ኤግዚቢሽን፤ በአገራችን የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ እንደ ማነቆ የተቀመጠውን የአገር ውስጥ የኮንስትራክሽን ግብአቶች ችግር፣ ወጪና ጊዜ ቆጣቢ የኮንስትራክሽን እጥረት ለመቅረፍና የተሻለ ኢንዱስትሪ ለመፍጠር፣ ብዙ የልምድ ልውውጥና የቴክኖሎጂ ሽግግር የገበያ ትስስር የሚደረግበት ነው ብለዋል- ሚኒስትሯ ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፡፡
ከ9ኛው የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን በተጨማሪ፣ 6ኛው አግሮፉድና ፓኬጂንግ እንዲሁም  የመጀመሪያው አዲ ፓወር ኤግዚቢሽኖችም ዛሬ ይዘጋሉ፡፡  

Read 2102 times