የደራሲ ያለው አክሊሉ “ባለዝናር መነኮሳት” የተሰኘ መፅሐፍ ገበያ ላይ ዋለ፡፡ መፅሐፉ በዋናነት በኢትዮጵያ ፖለቲካ አካሄድ፣ ውድቀትና ተስፋ ላይ በማራኪ አቀራረብ የተፃፈ ፖለቲካዊ ልብ ወለድ ነው፡፡ “… ባለዝናር መነኮሳት” በልብ ሰቃይ የአተራረክ ክህሎት ሁለንተናዊ ጓዳ ጎድጓዳችንን ባማረ ቋንቋና ውብ አገላለፅ አብጠርጥሮ ያሳየናል፡፡
ርዕስ መዝዞ ይተነትንና መፍትሄ ሳያመላክት አያልፍም፣ ሲቋጭም ተንብዮ ነው፡፡ እንደዋዛ አቃልሎ ይጀምርና እንደ ሸክላ ድስት እየጋለ፣ ወደ ማታ እሳተ ነበልባሉን ያወርደዋል፡፡ አንድ በሳል ፖለቲካዊ ልቦለድ ፀሐፊ ተፈጥሯል ብዬ ለመናገር አላመነታም…” ብለዋል፡፡ ዶ/ር አጉማስ በርነህ በመፅሐፉ ጀርባ ላይ ባሰፈሩት ማስታወሻ፡፡ በ32 ክፍሎች የተደራጀውና በ375 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ፤ በ152 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ደራሲው ከዚህ ቀደም “ወሰብሳቤ” እና “አሻሮ መንጋ” የተሰኙ መፅሐፍትን ለንባብ ማብቃታቸው አይዘነጋም፡፡