Monday, 20 August 2018 00:00

በህንድ የደረሰ የከፋ የጎርፍ አደጋ 44 ሰዎችን ገድሏል

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

 በቱርክ በመሬት መንቀጥቀጥ 30 ሺህ ዜጎች ሊሞቱ እንደሚችሉ ተነግሯል

    በህንድ ለቀናት የዘነበው ሃይለኛ ዝናብ ያስከተለውና ባለፉት የአገሪቱ 100 አመታት ታሪክ እጅግ የከፋው እንደሆነ የተነገረለት የጎርፍ አደጋ፤ 44 ሰዎችን ለሞት  መዳረጉ ተነግሯል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በደቡባዊ ህንድ በምትገኘው ኬራላ ግዛት የተከሰተው የጎርፍ አደጋ፣ በአስር ሺህ የሚቆጠሩ ነዋሪዎችን ከመኖሪያ ቤታቸው ማፈናቀሉን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ ከ50 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎች በመጠለያ ካምፖች ውስጥ እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኙም አመልክቷል፡፡
የጎርፍ አደጋው በተለይ ህጻናትንና ሴቶችን ክፉኛ ማጥቃቱን የጠቆመው ዘገባው፤ የትራንስፖርት አገልግሎቶችን ማቋረጡንና በርካታ ቤቶችን፣ የመሰረተ ልማት አውታሮችንና ሰብሎችን ማውደሙን ጠቅሶ፣ በአደጋው ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታና ህክምና ለመስጠት ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝም አክሎ ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የቱርክ የአደጋ ቁጥጥር ኤጀንሲ፣ በኢስታንቡል አካባቢ ይከሰታል ተብሎ የሚጠበቀው ከፍተኛ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ በከተማዋ የሚኖሩ 30 ሺህ ዜጎችን ለሞት ሊዳርግ እንደሚችል ባወጣው መግለጫ ማስጠንቀቁን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ ኤጀንሲው ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ እንዳለው፤ በኢስታንቡል በሬክተር ስኬል 7.5 የሚገመት የመሬት መንቀጥቀጥ ሊከሰት እንደሚችል ያስጠነቀቀ ሲሆን፣ ነዋሪዎች ተገቢውን ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የመሬት መንቀጥቀጡ 50 ሺህ በሚሆኑ ሰዎች ላይ ከፍተኛ የመቁሰል አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል ያስጠነቀቀው ኤጀንሲው፤ 49 ሺህ ያህል ህንጻዎችንም ሊያፈራርስና 2.4 ሚሊዮን ዜጎችን ቤት አልባ ሊያደርግ እንደሚችልም አስታውቋል፡፡

Read 2407 times