Saturday, 11 August 2018 11:11

የግብር እና የታክስ ስርዓቱ ተሀድሶና የምህረት አዋጅ ያስፈልገዋል

Written by 
Rate this item
(2 votes)


     የኢትዮጵያ የግብር ስርአት ኋላ ቀር እንደመሆኑ መጠን ከቅርብ አስርተ አመታት ወዲህ የግብር ስርዐቱን ለማዘመን በተሻለ የግብር አሰባሰብና በዘመናዊ የካሽ ሬጅስተር ማሽን የታገዘ ቢሆንም፣ የውስጥ አደረጃጀቱ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ባለመሆኑ፣ የግብር ስርዓቱ የጥቂት ግለሰቦችን ካዝና ሲሞላ እንደነበር ያደባባይ ምስጢር ነው፡፡  
ይህንኑ የምዝበራ ክፍተት ለመሙላትም መካከለኛና አነስተኛ ግብር ከፋዮች ላይ ተመጣጣኝ ያልሆነ ግብርና ታክስ በመጫን፣ “ክፈል አልችልም” በሚል እሰጥ አገባ፣ በየፋይናንስ ቢሮዎች ቅሬታ ሰሚ ጉባኤና በየፍርድ ቤቱ የሚጉላላው ግብር ከፋይ ቁጥር ቀላል የሚባል አይደለም፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ስለ ግብር አሰባሰብ በቅርቡ በፓርላማ ባደረጉት ንግግር፤ በሀገራችን ያሉ ወደ ሶስት ሺ የሚጠጉ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ግብራቸውን ባግባቡ ቢከፍሉ በቂ በመሆኑ ታች ወርደን አነስተኛ ግብር ከፋዮችን ባላስጨነቅን ነበር ብለዋል፡፡ ይሁን እንጅ ሁሉም ግብር ከፋዮች በየደረጃቸው የሚፈለግባቸውን ግብር የመክፈል አገራዊ ግዴታ እንዳለባቸው እሙን ነው፡፡
ሆኖም ግብር ከፋዮች በየበጀት አመቱ በሂሳብ መዝገብ አቅርበው፣ ከከፈሉት ግብር ውጭ “ገቢ አነሰ” በማለትና ዘመናዊ የሂሳብ አያያዝ ዘዴን በሚጻረር “የዴስክ ኦዲት ግኝት” በተባለ የውስጥ አሰራር ተገቢ ላልሆነ የግብር ጫና ከመዳረጋቸውም በላይ በየበጀት ዓመቱ የሚቀርበው የሂሳብ መዝገብ፣ በወቅቱ ባለመመርመሩና ለብዙ አመት በመወዘፉ ምክንያት ወደፊት በተገኘው አጋጣሚ ሲመረመር የሚገኘው የልዩነት ግብር ከተጠራቀመ የባንክ ወለድና መቀጫ ክፍያ ጋር ተዳምሮ፣ ግብር ከፋዩን እንደሚጎዳው ይታወቃል፡፡
ስለሆነም አሁን አገራችን በሰነቀችው የይቅርታ፣ የምህረትና በፍቅር የመደመር ጉዞ መሰረት የታክስ ስርአቱም ለተወሳሰበውና ለተወዘፈው የውሳኔ አሰጣጥ ችግር የምህረት አዋጅ አድርጎ፣ በአዲስ መልክ የአሰራር ስርአቱን ሊያዘመን ይገባል እላለሁ፡፡
ዳኘ ከአዲስ አበባ ፒያሳ

Read 1661 times