በሪል እስቴት ግንባታ ላይ የተሠማራው “ፍሊንትስቶን ሆምስ”፣ በአማራ ክልል ደሴ ከተማ ከ29 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባውን የልህቀት የአዳሪ ት/ቤት ለክልሉ ትምህርት ቢሮ አስረከበ፡፡
የልህቀት ት/ቤቱ በ2010 ዓ.ም የ8ኛ ክፍል ብሄራዊ ፈተና ወስደው ከፍተኛ ውጤት ያመጡ 100 ተማሪዎችን በ2011 የትምህርት ዘመን ተቀብሎ ለማስተማር መዘጋጀቱ ታውቋል፡፡ በ5.5 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈው የልህቀት የአዳሪ ት/ቤቱ፣ ባለ አንድ ወለል 13 ህንፃዎች ያሉት ሲሆን ግንባታው የተጀመረው በ2005 ዓ.ም ነበር፡፡
በ2002 ዓ.ም የአማራ አቀፍ ልማት ማህበር ት/ቤቶችን ለማስገንባት ባካሄደው የእርዳታ ማሰባሰብ ፕሮግራም ላይ፣ የ”ፍሊንትስቶን ሆምስ” ባለቤት ኢ/ር ፀደቀ ይሁኔ፣ በ10 ሚሊዮን ብር የአዳሪ ት/ቤት ገንብተው ለማስረከብ ቃል ገብተው የነበረ ሲሆን ት/ቤቱም በቃሉ መሠረት የተፈፀመ ነው ተብሏል፡፡
በ10 ሚሊዮን ብር ሊገነባ ታቅዶ የነበረው የአዳሪ ት/ቤቱ፤ በየጊዜው የግንባታ ቁሣቁስ ዋጋ መናርን ተከትሎ ከ29 ሚሊዮን ብር በላይ እንደፈጀ ከኩባንያው የተገኘ መረጃ ይጠቁማል፡፡