Print this page
Sunday, 13 May 2018 00:00

ሲንጋፖር ለትራምፕና ኪም ታሪካዊ ስብሰባ ተመርጣለች ተባለ

Written by 
Rate this item
(1 Vote)

  77 በመቶ አሜሪካውያን ስብሰባውን ይደግፋሉ ተብሏል

    አይን እና ናጫ ሆነው የከረሙትና ከዛሬ ነገ ከቃላት ጦርነት ወደ ሚሳኤል ጦርነት ይገቡ ይሆን በሚል አለም በስጋት ተወጥሮ ሲከታተላቸው የነበሩት የአሜሪካው ዶናልድ ትራምፕና የሰሜን ኮርያው አቻቸው ኪም ጁንግ ኡን፣ ከሳምንታት በፊት ሁሉንም ፉርሽ አድርገው፣ ባልተጠበቀ ሁኔታ ሰላም በማውረድ፣በአይነስጋ ተገናኝተው በጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ ሊመክሩ  መቀጣጠራቸውን ያስታወሰው ሲኤንኤን፤ ለመሪዎቹ ታሪካዊ ስብሰባ የተመረጠቺው ሲንጋፖር መሆኗን ዘግቧል፡፡
ሰሜን ኮርያ አስራቸው የነበረቻቸውን ሶስት አሜሪካውያን፣ ባለፈው ረቡዕ መልቀቋን ተከትሎ የወጡ መረጃዎች፣ በስልጣን ላይ እያሉ በጋራ ስብሰባ ላይ በመታደም በሁለቱ አገራት ታሪክ የመጀመሪያዎቹ የሚሆኑት ትራምፕና ኪም ለሚያደርጉት ስብሰባ በተመረጠቺዋ ሲንጋፖር፣ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡
የተፈቱትን አሜሪካውያን እስረኞች ለማምጣት ወደ ፒንግያንግ አምርተው የነበሩት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማይክ ፖምፒዮ፣ ከሰሜን ኮርያው መሪ ጋር በቀጣዩ ስብሰባ ዙሪያ መምከራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ፖምፒዮ በበኩላቸው፤የመሪዎቹ ስብሰባ የሚከናወንበት ቦታና ጊዜ መወሰኑን ከመናገር ውጪ የትና መቼ የሚለውን በግልጽ አለመጠቆማቸውን ገልጧል፡፡
የሰሜን ኮርያው ኪም ባለፈው ረቡዕ በሰጡት መግለጫ፤”ከፕሬዚዳንት ትራምፕ ጋር የማደርገው ስብሰባ በኮርያ ልሳነ ምድር ሰላምን ለማስፈንና የተሻለ መጻይ ጊዜን ለመፍጠር የሚያስችል ታሪካዊ ክስተት ይሆናል” ብለዋል - በመንግስት መገኛኛ ብዙኃን፡፡
የአሜሪካ መንግስት ባለስልጣናት ከገለልተኛነቷና ከተሟላ የመሰረተ ልማት አውታሮቿ ጋር በተያያዘ ሲንጋፖርን ለስብሰባው ሳይመርጧት እንዳልቀሩም ዘገባው አመልክቷል፡፡ በተያያዘ ዜናም 77 በመቶ ያህል አሜሪካውያን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሰሜን ኮርያው አቻቸው ጋር ለመገናኘት መወሰናቸውን እንደሚደግፉና ትራምፕ በሰሜን ኮርያ ጉዳይ እየተከተሉት ያለውን አካሄድ የሚደግፉ ዜጎች ቁጥርም ከወራት በፊት ከነበረው ጭማሪ ማሳየቱን ሲኤንኤን በጥናቱ አረጋግጧል፡፡

Read 1875 times
Administrator

Latest from Administrator